Thursday, May 29, 2014

ማቋረጥ

                                      

                   . ልቦለድ ቢጤ

መምህር ተሻለ አዲስ አበባ ውስጥ አለ በሚባለው ትምህርት ቤት ውስጥ የአማርኛ መምህር ነው ። ለሁለት ሰዓታት የነበረውን እረፍት ከጓደኞቹ ጋር ቼዝ ሲጫወት ቆይቶ ፔሬዱ ሲደርስ ወደሚያስተምርበት ክፍል እየተጣደፈ ሲጓዝ ነበር ድንገት ከኌላው በዳይሬክተሩ አቶ ዘሩ የተጠራው
<< የት ክፍል እየገባህ ነው ? >>
<< ስድስተኛ ቢ ነኝ - ምነው ፈለጉኝ እንዴ ? >>
<< እንግዶቹ ቤተመጻህፍቱንና ላቦራቶሪ ክፍሉን ጎብኝተው ጨርሰዋል >>
<< እንዴ እስካሁን ከዚህ ግቢ አልወጡም ? >> አለ ተሻለ በግርምት
<< አዎ አኔ ቢሮ ብዙ ስለቆዩ ነው ። ሪፖርቴን ጣፋጭ በሆነ መልኩ አቅርቤያለሁ ። ምቀኞች ደካማ ነው እያሉ የሚያሰወሩትን የትምህርት ጥራት መገምገም ስለፈለጉ ተግባራዊውን ነገርም ማየት ፈልገዋል ። ዛሬ ርዕሰ ጉዳይህ ምንድነው ? >> ዳይሬክተሩ እየተጣደፉ ነው የሚያወሩት ።
<< ቃላት ፣ የቃላት እርባታና የቃላት አረዳድ የሚል ነው ። በተጨማሪም ... >>
<< ኡ ? ... ምነው ተሻለ ? ምንድነው ዲሪቶ አደረከው እኮ ? >>
<< ተማሪዎች አንድን ተመሳሳይ ቃል እንዴት እንደሚተረጉሙትና በምሳሌም እንዴት እንደሚያስደግፉት የሚታይበት በመሆኑ የአረዳድ ማዕዘናቸውን የሚያሰፉበት ነው >>
<< ጥሩ ... ጥሩ ... ዘዴው ምንድነው ? ማለቴ የምታስተምርበት ? >> አሉ ግራና ቀኝ እየተገላመጡ
<< ተማሪዎች ቃሉን ከሶስት ቀናት በፊት ስለወሰዱ ያዩበትን መንገድ ሰምተን ወደ አጠቃላዩ ትምህርት ነው የምንደረደረው >>
<< አደራ እንግዲህ ? ... >> ዳይሬክተሩ ሀሳባቸውን ሳይቋጩ እንግዶቹን ወዳዩበት አቅጣጫ በሩጫ ተፈተለኩ ።
ሃላፊ ሆኖ የመርበትበትና ሃላፊ ሆኖ የመኮፈስ መንታ ገጽታዎች ሽንት ቤት ገብቶ አሜባን ማማጥና ከግልግል በኌላ ፈገግ ብሎ ቀበቶን ከማሰር ጋር እንዴት እንደተመሳሰለበት አላወቀም - ግን ያለቦታው ይህን ምሳሌ ነበር ሲያነጻጽር የነበረው ። ወደመሬት ወድቄ እምቦጭ እላለሁ የሚል የሚመስለውን ቦርጭ በአንድ እጅ ፣ ወዲህና ወዲያ የሚወራጨውን ካራቫት በሌላ እጃቸው ይዘው በዚህን ያህል ፍጥነት መሮጣቸውም በአስገራሚ መልኩ ፈገግታ ጭሮበታል ።
ለመምህር ተሻለ የማስተማር ስልት መሰረት የሆነው ቢቢሲ የተባለው መገናኛ ብዙሃን ነው ። ይህ ጣቢያ በቀጣዩ ሳምንታት የሚያቀርባቸውን አንኳር ጉዳዮች አስቀድሞ ነው የሚያስተዋውቀው ። ተማሪዎችም ቀጣዩን ምዕራፍ አስቀድመው ካወቁ መደናገርን አስወግደው ተሳታፊና እንደ ካራ ስል ይሆናሉ የሚል እምነት አለው ። ይህ ስልት ከፍተኛ ባለስልጣን ፣ ሀብታሞችና ታዋቂ ሰዎች ልጆቻቸውን በሚያስተምሩበት በዚህ ትምህርት ቤት በሁሉም መምህራን እንደ ቋሚ አሰራር ተግባራዊ እንዲሆን በተለያዩ ግዜያት በተካሄዱ ስብሰባዎች ላይ እስከመናገር ደርሷል ። የማስተማሪያ መንገድንና የፈተና አወጣጥ ዘዴን ደብቅ እያደረግን የትምህርት ጥራትን ከፍ ለማድረግ መሞከር ከንቱ ምኞት ነው የሚል ሀሳብም አለው ።
የስድስተኛ ቢ በር ድንገት ተበርግዶ በርካታ የሀገሪቱ ባለስልጣናት ተግተልትለው ወደ ውስጥ ሲገቡ ተማሪዎቹ እንግዶቹን ቆመው ተቀበሏቸው ። እንግዶቹ ክፍት በተደረገው አንደኛው ጠርዝ ከተቀመጡ በኌላ መምህር ተሻለ ሞቅ ያለ ሰላምታ አቅርቦ ማስተማሩን ቀጠለ ።
<< እሺ ተማሪዎች ሁላችሁም እንደምታውቁት የዛሬው ክፍለ ግዜ የቃላት አረዳድ ላይ የተመሰረተ ነው ። እስኪ ዋነኛ ቃሉን የሚያስታውሰኝ ማነው ? >>
<< አቋረጠ >> አለ በላይ የተባለው የክፍሉ አለቃ ተሽቀዳድሞ ፤ እንደስሙ ሁሌም የበላይ መሆን አለብኝ ብሎ ስለሚያስብ ለብዙ ነገሮች ደንታ የለውም ።
<< ልክ ነው አቋረጠ ሲረባ ማቋረጥ ፣ ያቋርጣል ፣ አቋራጭ ፣ ያቆራርጣል ወዘተ እያለ ይቀጥላል ። ለመሆኑ አቋረጠ ምንድነው ? እንዴት ተረዳችሁት የሚል ነበር የቤት ስራው ? >>
<< እሺ መስፍን >> አለ መምህር ተሻለ እጅ ካወጡት ውስጥ ለአንደኛው እድል እየሰጠ
<< አቋረጠ ማለት የቀለበት መንገድ አጥርን ዘለለ ማለት ነው ። ሰዎች ብረቱን የሚያቋርጡት በቅርበት መሸጋገሪያ ድልድይ ስለማይሰራላቸው ነው ። ሆኖም ብዙ ሰዎች ቶሎ እንደርሳለን ብለው ሲዘሉ በመኪና አደጋ እስከመቼውም ሳይደርሱ ቀርተዋል ። የመኪና አደጋ አሰከፊ ነው >> አለ ተማሪው የሀዘን ገጽታ እያሳየ ።
<< የማን ልጅ ነህ መስፍን ? >> አሉ አንደኛው ሚኒስትር በፈገግታ
<< የኢንጂነር ፈቃዱ >> ባለስልጣናቱ በአግርሞት ሳቅ አውካኩ
<< በመንፈስ ደግሞ የሳጅን አሰፋ ... >> አሉ ጥግ ላይ የተቀመጡት የፖሊስ ኮሚሽነሩ ፤ ቤቱ እንደገና በሳቅ ተንጫጫ ።
<< እሺ አያሌው ? >> ሳቁ እየሰከነ ሲመጣ መምህር ተሻለ ሁለተኛውን ተጠያቂ ጋበዘ
<< ማቋረጥ ማለት የቀበሮ ማቋረጥ ነው ። ሰዎች ለውጊያ ሲሄዱ ቀበሮ መንገዱን ካቋረጠቻቸው ይሸነፋሉ ። አጼ ቴዎድሮስም ሆኑ አጼ ሚኒሊክ በዚህ እንደሚያምኑ አያቴ አጫውተውኛል >> አለና ቁጭ አለ ። መምህር ተሻለ ፊት ላይ መደናገጥ ቢታይም ባለስልጣናቱ ከመሳቅ የገደባቸው ነገር አልነበረም ።
<< አያሌው አያትህ ማናቸው ? >> አሉ አሁንም አንደኛው ሚኒስትር እንደዘበት
<< ቀኛዝማች ነቅአጥበብ ....  >>
ወደ መሃል ቁጭ ያለ አንድ ባለስልጣን የተማሪውን ሀሳብ አቋርጦ << እነ ፊታውራሪና ቀኛዝማች አሁንም ሄደው ሄደው አላለቁም እንዴ ? >> ከማለቱ ቤቱ በእንባ ቀረሽ ሳቅ ተበጠበጠ ። መምህር ተሻለ የውሸት ፈገግታ እየታየበት ቀጣዩን ተማሪ ጋበዘ
<< ማቋረጥ ማለት የማራቶን ሩጫን ማቆም ማለት ነው ። ሩጫውን የሚያቆሙት ወንዶች ናቸው ። ወንዶች ሩጫውን የሚያቋርጡት በሴት ሰዓት ላለመግባት ነው ። የአባቴ ስም አሰልጣኝ ቶሎሳ ይባላል >>
የስድስተኛ ቢ ክፍል ኮርኒስ በሳቅ ወላፈን የእሳት ጢስ የፈጠረ መሰለ ። ሳቁን ያባባሰው ተማሪው አይቀርልኝም ብሎ ከወዲሁ  የአባቱን ስም ማስተዋወቁ ነበር ።
<< ማነህ ስምህ ? >> አሉ አንደኛው ሚኒስትር ወደተናጋሪው ተማሪ እየተመለከቱ
<< ዘላለም >>
<< ዘላለም  እኔ እንኳን የአባትህ ስም ቱርቦ ቱሞ ይሆናል ብዬ ጠብቄ ነበር >> አሉ ቀድመው እየሳቁ
<< እንዴ አያውቁም እንዴ ? እሱ እኮ ሞቷል - በጣም ጎበዝ አትሌት ነበር ። የሞተውም ተማሪ መስፍን እንዳለው በመኪና አደጋ ነው ። በመኪና አደጋ ላይ ብዙ መሰራት አለበት >> አለ ተማሪው ፈርጠም ብሎ
<< በእውነት የተማሪዎችህ የአመላለስ ስርዓት ጥሩ ነው ። በተለይ ጥሩ ነው ያልኩት በጣም ግልጽ ከመሆናቸው አንጻር ነው ። ይህ ባህሪ ነው እያደገ መውጣት ያለበት ። አንድን ጉዳይ የሚያዩበት መንገድም እንደሀገራችን ብሄር ብሄረሰቦች የሰፋና የሚያምር ነው ። የመሰላቸውን የመናገር ነጻነትም እንዳላቸው መረዳት ይቻላል ... >> አሉ አንደኛው ሚኒስትር ስሜታቸውን መቆጣጠር እያቃታቸው ።
ተማሪዎች እንደ ማዕበል በሚንጠው የሳቅ ጎርፍ ሳይናጡ እጃቸውን ለተሳትፎ በጉጉት ከማውጣት አልተቆጠቡም ። በምስጋናው የተነቃቃው መምህር ተሻለ ለመጀመሪያ ግዜ የሴት እጅ በማየቱ ተሳትፎውን ለማሰባጠር የመናገር እድሉን ትእግስት ለተባለች ተማሪ ሰጣት
<< አቋረጠ ማለት ንግግር አቋረጠ ማለት ነው ። ንግግር የሚያቋርጠው ደግሞ አበበ ገላው የተባለ ሰው ነው ። አበበ ገላው የጠላውንም ሆነ የወደደውን ሰው ንግግር ያቋርጣል ። አበበ ያቋረጠው ሰው የሀገር ውስጥ ስሪት ከሆነ ሰውየው ይሞታል ። ለምሳሌ ያህል ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ። አበበ ያቋረጠው ሰው የውጭ ሀገር ስሪት ከሆነ ሰውየው አይሞትም ። ለምሳሌ ያህል ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ >>
በሳቅ ሲታመስ የነበረው ክፍል በሚያስደነግጥ ጸጥታ ተወጣጠረ ። የባለስልጣናቱ ግንባር እንደ በረሃ መሬት እየተሰነጣጠቀ አስፈሪ የቦይ ምስል ሲፈጥር በግልጽ ይታያል  ። በግልባጭ በመምህር ተሻለና ዳይሬክተሩ ጆሮ ግንድ ስር መነሻውን አናት ያደረገ የላብ ጎርፍ ወደታችኛው የሰውነት ክፍሎች ደለል እየጠራረገ በፍጥነት ያሽቆለቁል ነበር ።
<< ምን እየተካሄደ ነው አቶ ዘሩ ?! ትምህርታዊ ኩዴታ እያደረጋችሁ ነው ! >> ተቀዳሚው ሚኒስትር ከወንበራቸው ተነስተው  ጸጥታውን በረጋገዱት
<< በእውነት አይን ያወጣና የተቀነባበረ የሽብር ተግባር ይመስላል ! >> ቃለ አቀባዩ እንደ ነብር ገሰሉ
<< በጣም ይቅርታ እጠይቃለሁ ። ምሳሌዎቹ በዚህ መልኩ ይቀርባሉ ብዬ አልጠበኩም ። የትምህርት ማቋረጥ ፣ የጽንስ ማቋረጥ ፣ የመንገድ መቋረጥ ፣ የወንዝ ማቋረጥ የሚኖራቸውን ተጽዕኖ አጉልቶ በማውጣት ... >>
<< ዝም በል አንተ ! ራስህ አቋርጥ ! ... ንግግርህን አቋርጥ ! ... >> የፖሊስ ኮሚሽነሩ ሌባ ጣታቸውን ቀስረው እየተንቀጠቀጡ የመምህር ተሻለን ቀልብ ገፈፉት ። ተክዘው የቆዩት አንደኛው ሚኒስትር ጣልቃ ገብተው <<  ያሳዝናል ! በተለይ ከዚህ ትምህርት ቤት ይህን የመሰለ ተራ አሉባልታ መስማት ያሳፍራል ... ትዕግስት ለመሆኑ የማን ልጅ ነሽ ? >> ሲሉ ለስለስ ባለ ድምጽ ጠየቋት
<< የአበበ >> አለች ልጅቱ ፈራ ተባ እያለች
<< የአበበ ? >> አንደኛው ሚኒስትር አንዴ ልጅቱን ሌላ ግዜ ባለስልጣናቱን እያፈራረቁ ተመለከቱ
<< የቱ አበበ ?! >> አሉ በመገረምም በመኮሳተርም
<< የአበበ ገላው እኮ አይደለም ! የጄኔራል አበበ ... >> የክፍሉ አለቃ በላይ ነበር ጣልቃ ገብቶ የመለሰላት ፤ ትዕግስት ጭንቅላቷን  አወዛወዘች
አንደኛው ሚኒስትር ተጨማሪ አስተያየት ሳይሰጡ ከክፍሉ ሲወጡ ባለስልጣናቱም እየተጣደፉ አጀቧቸው ። ፖሊስ ኮሚሽነሩና አንድ የደህንነት ባለስልጣን የአቶ ዘሩንና የመምህር ተሻለን ክንድ እንደ ምርኩዝ ተጠቅመው ተከተሉ ። የክፍሉ አለቃ በላይ እየሮጠ በሩን ከፍቶ የእንግዶቹን መራቅ ካረጋገጠ በኌላ ጥቁር ሰሌዳው ላይ << ማቋረጥ >> ሲል በትልቁ ጻፈ ። የክፍሉን ግራና ቀኝ ካሰተዋለ በኌላ
<< ቃሉ ማቋረጥ ቢሆንም እኛ እንቀጥላለን - ተጨማሪ ሃሳብ ያለው አለ  ? >> ሲል እጁን ኪሱ ከቶ ጠየቀ ። ዘላለም እጁን አወጣ
<< እሺ ዘላለም >>
<< ማቋረጥ ማለት የመምህር ተሻለን ትምህርት ማቋረጥ ነው >>
<< ትስማማላችሁ ? >>
<< በጣም ! በጣም ! ሰሌዳው ላይ ጻፈው ! ጻፈው ! >> ሲሉ ተንጫጫቡት ። በላይ የተነገረውን ጹሁፍ በትልቁ ጻፈው ። ቀጥሎ እጅ ያወጣችው ትዕግስት ነበረች
<< እሺ ትዕግስት ተጨማሪ ነው ? >>
<< ዋናው ጥያቄ የስድስተኛ ቢ የእውቀት ጉዞ ለምን በድንገት ተቋረጠ የሚለው ይመስለኛል ? >> ስትል ጥያቄ አዘል አስተያየት ወረወረች ። አለቃው የትዕግስትን ጥያቄ አሁንም ሰሌዳው ላይ አሰፈረው ።
<< እውነት የስድስተኛ ቢ የእውቀት ግጥሚያ ለምን ተቋረጠ ? >> ሲል የክፍሉ አለቃ እየንተጎራደደ ጠየቀ ። አያሌው እጅ በማውጣቱ እንዲናገር ተፈቀደለት ።
<< የእውቀቱ ጉዞ የተቋረጠው  ብዙ ቀበሮዎች ክፍላችንን ስላቋረጡት ነው ! ይህን አያቴ የነገሩኝ ሳይሆን አይኔ የተመለከተው ነው >> ሲል የክፍሉ ተማሪዎች በመልስ አሰጣጡ በሳቅ መንፈራፈር ጀመሩ ። አሳሳቃቸው የባለስልጣናቱን የሳቅ ከፍታ በልጦ መገኘትን ያለመ ይመስል ነበር ።
<< ምንድነው እንዲህ የሚያደርጋችሁ ... ?! >> የሚለው ደንገተኛ ድምጽ ከወደ በሩ ብቅ ብሎ የሳቁን ወላፈን በአንድ ግዜ ጤዛ አለበሰው ።
የነገር ሽታን የሚያነፈንፈው የደህንነቱ ሰው ኮሚሽነሩን አስከትሎ ወደ ክፍል ገባ ። ከዚያም የስድስተኛ ቢን ተማሪዎች ትምህርት ከጥቁር ሰሌዳው ላይ በቅደም ተከተል በጥንቃቄ ማንበብ ጀመረ ።
< ቀበሮዎች > የሚለው ቃል ጋ ሲደርስ ግን ሳቁን መቆጣጠር አልቻለም ። የስድስተኛ ቢ ክፍል ተማሪዎች በባለስልጣኑ ድራማዊ ተግባር  ተገርመው ሳቁን ሊያጅቡት ቢገባም በፍጹም አልሳቁም ። በሚከብድ ጸጥታ የአሳሳቁን አይነት እየመረመሩና ቃሉን በነገር እያራቡ ነበር ። ከልቡ ሳቀ ... ከአንገት በላይ ሳቀ... እንደ ማሽላ ሳቀ...
ሳቀ ...
ይሳቅ ...
ስቆ...
አሳሳቆ ...

Monday, May 12, 2014

የተመጣጣኝ ርምጃ ልኩ የት ድረስ ነው ?




ፖሊስ ረብሻንና ብጥብጥን ለማረጋጋት መጀመሪያ መጠቀም ያለበት ህይወት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሊያደርሱ በማይችሉ ነገሮች ነው ። ምክንያቱም ሰው የመኖር ፣ ከግርፋትና ሰብዓዊነት ከጎደለው አያያዝ የመጠበቅ መብት አለውና ። ለዚያም ነው ቆመጥ ፣ ውሃ ፣ አስለቃሽ ጋዝ ፣ የፕላስቲክ ጥይትና የመሳሰሉት በመጀመሪያ ረድፍ የግድ መታየት የሚኖርባቸው ።
በርግጥ እነዚህ ድርጊቶች በራሳቸው ጉዳት ሊያመጡ ስለሚችሉ ተግባራዊ ሲደረጉም ጥንቃቄና ሰብዓዊነት የተላበሰ መርህን ይፈልጋሉ ። ለምሳሌ ያህል ፖሊስ ዱላ ሲጠቀም በፍጹም ጭንቅላት ፣ አንገት ፣ አከርካሪ አጥንት ፣ ልብና ኩላሊት ላይ ማነጣጠር የለበትም ። የፕላስቲክ ጥይትም ቢሆን ከደረት በታች ባሉ የሰውነት ክፍሎች ላይ ነው ተግባራዊ መሆን ያለበት ። አስለቃሽ ጋዝም መጠኑና ደረጃው ከፍ እንዳይል ጥንቃቄ ይፈልጋል ።
የሀገራችን እውነታዎች ግን ለዚህ መርህ ጀርባቸውን የሰጡ መሆኑ ይታያል ። ፌዴራል ፖሊስ በአንድ ምት ጭጭ የሚያደርገውን ዱላውን በቀጥታ የሚሰነዝረው ለጭንቅላት ነው ። አጋጣሚ ሆኖ በሁለት ምክንያቶች ኢላማዎች ግባቸውን ይስታሉ ። አንዱ እንደ አይን ሁሉ የጭንቅላት አምላክ አትርፎህ ዱላው ጀርባህን እንደ ሙሴ ዘመን ባህር ይሰነጥቀዋል ። ሁለተኛው ራስህን ለመከላከል ወደላይ የሰነዘርከው እጅህ ተሰብሮም ቢሆን አንጎልህን ከመፈጥፈጥ ይታደገዋል ። በጣም የሚያሳቅቀው ግን አንዱ ፖሊስ መምታት ሲጀምር ሌላውም ሰልፍ ጠብቆ የጭካኔውን ደርሻ ማዋጣቱ ነው ። በሰብዓዊ ስሜት ተገፋፍቶ < እረ ይበቃዋል ? > ብሎ የሚከላከል አለመገኘቱ ሌላኛው አሳዛኝ ክስተት ነው ። ሰው ሬሳ እስኪሆን ድረስ እንደ እባብ መቀጥቀጥ ምን የሚባል ትምህርት እንደሆነ ግልጽ አይደለም ። ሰብዓዊው ህግ ብዙ ደም ለፈሰሰው የመጀመሪያ እርዳታ እንዲያገኝ ምቹ ሁኔታ መፈጠር እንዳለበት ሁሉ ያዛል ። በመሰረቱ እንደዚህ አይነት ክስተቶች የመሰረታዊ መብት ጥያቄዎች ግብግብ እንጂ ድንበር የመቁረስ ወይም ሀገር የማስገበር ጦርነት አይደለም ። በለየለት የሁለት ሀገር ጦርነት ላይ እንኳን የተማረከ ወታደር በቁጥጥር ስር ይውላል እንጂ ሰብዓዊና ሞራላዊ ህግን በመተላለፍ አይጨፈጨፍም ። ጀግኖች የሚቀጡህም ሆነ ጠማማ ካለብህ የሚያስተካክሉህ በማስተማር ነው ።
ለህይወት አስጊ የሆነው ተኩስ በአስገዳጅ ሁኔታ ተፈጻሚ ሊሆን የሚችለው በተለያዩ አጥጋቢ ምክንያቶች ነው ። ፖሊሱ ሁሉንም ስልቶች ውጤት አጥቶበት በተለይም ሁከቱ በህይወቱ ላይ አደጋ የሚያስከትልበት ከሆነ ራሱን ለመከላከል ፣ ሁከቱ የሌሎች ሰዎችን ህይወት ሊያጠፋ የሚችል ከሆነ ተመጣጣኝ ርምጃ ሊወስድ ይችላል ። ከረብሻና ተቃውሞ ዉጪም አንድ ወንጀለኛ ካመለጠ ሌሎችን ይጎዳል ተብሎ የሚታሰብ ከሆነ መሳሪያ ጥቅም ላይ ሊውል ይችላል ።
ይህ ማለት ግን ከላይ የተቀመጡትን ምክንያቶች ሰበብ በማድረግ ፖሊስ ወይም የተደራጀው ሃይል ፍጹም ሊተካ የማይችለውን የሰው ልጅ ህይወት ይቀጥፋል ማለት አይደለም ። በተመድ ለፖሊስ የተዘጋጁ ደረጃቸውን የጠበቁ የስልጠና ማንዋሎች እንደሚያስረዱት እያንዳንዱ ፖሊስ ወደ ስራ ከመግባቱ በፊት በስልጠና ወቅት ራስን ስለመከላከል ፣ ስለ ሰብዓዊ አያያዝ ፣ ስለመጀመሪያ ርዳታ ፣ ስለተሰበሰበ ህዝብ ባህሪ ፣ ስለግጭት አፈታት ፣ ስለውጥረት አስተዳደር ወዘተ በቂ ትምህርት የሚያገኝ ቢሆን በችግር ግዜ አንድና አንድ ወደሆነው ግድያ ወይም የፈሪ ዱላ በፍጥነት አያመራም ። በስልጠና የበለጸገ እንዲሁም የሃላፊነቱ ሚና ከህዝባዊነት የመነጨ መሆኑን የሚገነዘብ ፖሊስ ቢያንስ በመጨረሻው ሰዓት ሲተኩስ እንኳ ወንጀለኛን ለመቆጣጠር እንጂ ነፍስን ለማቋረጥ አያልምም ። ጭንቅላት መምታት ነጥብ የሚያሰጠው በስልጠና ወቅት የተኩስ ሰሌዳ ላይ እንጂ የራስህ ቤተሰብና ወገንህ ተቸግሮ ተቃውሞ በሚያሰማበት ወይም ሁከት በሚፈጥርበት አንድ ቀን አይደለም ። ዞሮ ዞሮ ህዝብ ጠላት ሆኖ ስለማያውቅና ሊሆንም ስለማይችል እግሩን መምታትም ሲበዛበት ነው ።
አዲስ አበባንና በዙሪያዋ የሚገኙ የኦሮሚያ ከተሞችን በማካተት የተዘጋጀውን የጋራ ማስተር ፕላን በመቃወም በየቦታው የተቀሰቀሰው ቁጣ የብዙ ሰላማዊ ዜጎችን ህይወት በልቷል ። መንግስት የሟቾቹን ቁጥር 11 ቢልም ተቃዋሚ ድርጅቶች እስከ 45 ያደርሱታል - የውጭ መገናኛ ብዙሃን ደግሞ አስከ ሰላሳ ። የቁጥር ዝቅታና ከፍታ የሚመነጨው ኌላ የሚቀርበውን ዓለማቀፍ ስሞታና ክስ ታሳቢ ከማድረግ አንጻር ነው ። አነስተኛ ሰው ከሞተ ተመጣጣኝ ርምጃ ነው የወሰድኩት በማለት ቁጣን ለማርገብ ይቻላል ። የኢትዮጽያ መንግስት በዛ ያሉ መብት ጠያቂዎችን በአደባባይ የመግደል ልምድ ከግዜ ወደ ግዜ እያደበረ የመጣ ይመስላል ።
በምርጫ 97 ማግስት በተቀሰቀሰ ቀውስ የሰው ልጅ ክብር ህይወት በጥይት ሲረግፍ አቶ መለስ ዜናዊ ተመጣጣኝ ርምጃ ነው የወሰድነው በማለት መጠነኛ አሃዝ በመጥቀስ መግለጫ ሰጥተው ነበር ። ሆኖም ጉዳዩን እንዲያጣራ የተሰየመውና በአቶ ፍሬህይወት ሳሙኤል የሚመራው ቡድን << መንግስት ያልተመጣጠነ/ ከመጠን ያለፈ /  ርምጃ ወስዷል >> የሚል ያልተጠበቀ ሪፖርት አቀረበ ። በሪፖርቱ መሰረት 193 ሰዎች በጥይት ሲሞቱ 763 ያህል ቆስለው ነበር ። ሪፖርቱ ጓዳ የነበረን ራቁት ገላ ድንገት ለአደባባይ ያጋለጠ አውሎ ንፋስ ነበር ።
ተቃውሞ የሚበርደው ሰዎች ሲሞቱ ነው የሚለው ፍልስፍና ያልተለወጠ መሆኑም የዛሬው እውነታ እያሳበቀ ነው ።  በ1997 ግርግር አንዳንድ የአዲስ አበባና ፌዴራል ፖሊስ አባላት አጋዚ የተባለው ልዩ ጦር እንጂ እኛ ሰላማዊ ህዝብን አልገደለንም እያሉ ራሳቸውን ነጻ ሲያወጡ ነበር ። መጸጸቱ በራሱ ጥሩ ይመስለኛል - ግን ይህ አይነቱ ደመ ንጹህነት መሰዎዕትነት ለሚከፈልለው ሲቪል ማህበረሰብ ትርጉም አልባ ነው ። መደበኛው ፖሊስ የመግደል አማራጭን በመርህ ደረጀ የማይቀበል ከሆነ የገዳዩንም ጣልቃ ገብነት ማለዘብ የሚከብደው አይሆንም ። ምናልባት መቋቋም የማይችለው የአስገዳዩን ቀጭን ትዕዛዝ ከሆነ አላውቅም ። ዞሮ ዞሮ በኛ ሀገር ፖሊሲያዊም እንበለው አጋዚያዊ ቀመር የተመጣጣኝ ርምጃ ልኩ የት ድረስ ነው ? ስንት ሰው ሲሞትና ስንት ሰው ሲቆስል ? ይህ ወለል ካልታወቀ እንዴት ነው < የወሰድኩት ርምጃ ተመጣጣኝ ነው > ማለት የሚደፈረው ? ግድያን ለማስቀረት መጣሩ ነው የሚሻለው ወይስ እየገደሉ በቁጥር ጅዋጅዌ መጫወት ?
የዛሬ የገደላ ዜና በሁላችንም የባንክ ደብተር ውስጥ የሚቀመጥ የቁጠባ ቦንድ ነው ። ይህን ኖት ነገ እያወጣን ስንመዝረው ውስጣችንን የሚሞላው ፍርሃት አፋችንን የሚሞላው ደም ነው ።
 እናም ነገ ያስፈራል ።
ውሃ ጠማኝ ፣ ደመወዝ አነሰኝ ፣ መሬቴን በህገወጥ መንገድ ተቀማሁ ፣ አስተዳደሩ ገለማኝ ብሎ ለተቃውሞ አደባባይ የሚወጣ ሰው ባልጠበቀው መልኩ ስሙ አሸብር ፣ ነውጤ ፣ ነፍጤ ተብሎ ቢቀየር እስር ቤት ሊያደርሰው ይችላል ።
ያስፈራል ።
የተቃውሞ ሰልፍ ድንገት ተደናቅፎ ግርግር ከፈጠረ ወይም ነፍሰጡሩ ተቃውሞ ድንገት ሜዳ ላይ ብሶታዊ ልጅ ቢገላገል ሊያስገድል ይችላል ።
በ2001 በወጣው የጸረ ሽብርተኝነት አዋጅ አንቀጽ 21 << ናሙናዎችን የመስጠት ግዴታ >> ላይ ተጠርጣሪው ለምርመራ ፍቃደኛ ካልሆነ ፖሊስ አስፈላጊ የሆነ ተመጣጣኝ ሃይል ተጠቅሞ ከተጠርጣሪው ናሙና ሊወስድ ይችላል ይላል ። ተመጣጣኝ ሃይል  እዚህም ጋ አለች ።  እንግዲህ ሰውየው መረጃ አልሰጥም ብሎ ግግም ካለ ፖሊስ ገድሎትም ቢሆን ናሙና ይወስዳል ማለት ነው ? -  አያስቅም - ያስፈራል ።

           

Tuesday, May 6, 2014

እናትነት






ፍቅር - ቋንቋ - ቀንዲል ውበት

የልብ - የአንጀት - ጠሊቅ እውነት

እናትነት...                                                                                               

የደም ውህድ - ክፋይ ስጋ

የምጥ ስርፀት - የአጥንት ዋጋ ።


/ ለእናቴ የብርጓል ዘውዴ /                                                                                                                                       

 

Sunday, April 27, 2014

የደነበረው


የደነበረ በሬን የሚያረጋጋው ሁለተኛ አካል የለም ። በሬው መረጋጋት የሚችለው የራሱ የድንጋጤና የፍርሃት ድልቂያ በራሱ ግዜ እየሳሳ ሄዶ ጸጥ ማለት ሲጀምር ነው ።
እንደእኔ እምነት ኢህአዴግ ከደነበረው መንፈስ ገና አልተላቀቀም ። ድርጅቱ ገመድ በጥሶ መሮጥ የጀመረው በ1997 « እንከን የለሽ » ምርጫ ወቅት ነበር ። ዘጠኝ የእፎይታ አመታት በማለፉ ረጅም ቢሆንም እስካሁን እንከን የለሽ መረጋጋት አልፈጠረለትም ። ምክንያቱም ጉዳቱ ከስሜታዊ ቁስል ወደ ስነልቦና ጉዳት ሳይታወቅ ያደገ / Trauma / በመሆኑ ተመሳሳይ ግዜያትን ጠብቆ ሊገነፍል ስለሚችል ።
ያኔ በስንት ደምና አጥንት ያመጣነው ድል ድንገት ከከተማ በበቀለ እንጉዳይ / ድርጅት / እንዴት ይነጠቃል ? በሚል የአጥቢያ ድል አለቆቻችን ሳይቀሩ ቢሮ ዘግተው እዬዬ ብለዋል ። የቅንጅት ጉዳይ ያው በሚታወቀው መልኩ ከተዘጋ በኃላ በሬው እየፎገረ ማባረር የጀመረው « ሀሳብ » ን ነበር - ሀሳብን በነጻ የመግለጽ መብትን ። በዚህም በርካታ የህትመት ውጤቶች ከገበያው ድራሻቸው ጠፋ ። በሬው ይህን ርምጃ የወሰደው በግራና ቀኝ ጆሮው ላይ መርፌ እየወጉ ከሚያስፈረጥጡት አካላት አንደኛው መሆናቸውን በመረዳቱ ነው ።
ከዚያ ወዲህም ከዴሞክራሲ መብቶች አንዱ የሆነው ሀሳብን በነጻ የመግለጽ መብት ከአደገኛ ቀጠና ውስጥ መውጣት አልቻለም ። አንዴ ፈንጂ ወረዳ ስለሆንክ ግራና ቀኝህን ተመልከት ሲባል ሌላ ግዜ ቀይ መስመሩን አትጠጋ ወይም አትርገጥ ሲባል እየተሳቀቀ ቆይቷል ። በርግጥ የሀገራችን ህገ መንግስት ለዚህ መብት መበልጸግና መፋፋት በጽሁፍ ደረጃ ድጋፍ ይሰጣል ። ጋዜጠኛው አንዳንዴ ይህን እያሰበ የተወሰነ ርቀት ሲጔዝ ቢታይም ድንገት ከሩቅ የሚተኮስ ድሽቃ ከአፈር ይቀላቅለዋል ። ብእረኞቹ በሚደርስባቸው ተጽዕኖ ሲያማርሩና ሲያቃስቱ ፣ ከታፈረውና ከተከበረው ውክቢያ ጋር ፖሊስ ጣቢያና ፍርድ ቤት ሲመላለሱ ፣ መፈክር ይሁን ቁጣ ባለየ መልኩ ሲገሰልባቸው ፣ አንዳንዴም ሲታሰሩ ማየት ብርቅ አልሆነም ።
በመሰረቱ ኦትዮጽያ የሰብዓዊ መብቶች ድንጋጌን የህጔ አካል አድርጋ ተቀብላለች ። ይህም ግዙፍ ክሬዲት ሆኖ በየስብሰባው ምስጋና መወድስ ተዘርፎለታል ። አንዳንድ ነጭ ጥናት አቅራቢዎች < ኢትዬጽያን ተመልከቱ የህገ መንግስቷ አብዛኛው ገላ በሰብዓዊ መብት መልካም መዓዛ የታወደ ነው ፣ የኢትዬጽያን መንገድ ተከተሉ በስብዕና ፍቅር ትሰክራላችሁና > በማለት ምስክርነት ሲያቀርቡ ... እሰይ አበጀሽ የኛ ሎጋ አበጀሽ የኛ ልጅ .... እያልን ማስታወሻችን ላይ አንጎራጉረናል ። በየአለማቀፉ ሰብዓዊ መብት ድንጋጌ ታዋቂው አንቀጽ / 19 / ሁሉም ሰው ሀሳቡንና አስተያየቱን ያለማንም ጣልቃ ገብነት በማንኛውም ሚዲያ መግለጽ እንደሚችል ይደነግጋል ። ህገ መንግስታችን አባባሉን እንዳለ ወስዶ የአንቀጹን ቁጥር ብቻ ነው 29 ያደረገው ። ውበት ነበረው ። መልክ ብቻ ምን ያደርጋል ሆነ እንጂ ። በነገራችን ላይ ይህ መብት የተሰጠው  ለጋዜጠኛው ብቻም አልነበረም ።  በመሆኑም ሀሳብ መግለጫው ድልድይ በታሸገ ወይም በተሰበረ ቁጥር የመብት ግፊያና ነጠቃ እየደረሰበት የሚገኘው ብዙሃኑ ጭምር ሆነ ማለት ነው ።
ለማደግ በመፍጨርጨር ላይ በምትገኝ ሀገር ውስጥ ደፋር ፣ ነቃሽ ፣ እውነት አመላካችና ባለሶስት አይን ጋዜጠኛ አስፈላጊ ነው ። ምክንያቱም ማደግ የሚቻለው የልማት አጀንዳን እያግበሰበሱ ዴሞክራሲንና ነጻነትን በማስራብ አይደለም ። ማደግ የሚቻለው በልዩ ተዓምር ሳይሆን ጥሩና መጥፎውን ፣ ሜዳና ገደሉን ለይቶ ሚዛናዊ መስመር ማስመር ሲቻል ነው ። በተቃራኒው ለምን የድርጅቴ ሀሳብ ተብጠለጠለ ? ለምን የድርጅቴ አመራር ተተቸ ? በተቌሜ ክፍተት ሳይሆን በተክለቁመናው ለምን የገነፈለ የብእር ቀለም ተደፋበት ? ወዘተ በሚሉ እፍኝ ሰበቦች ጋዜጠኛውን ማስፈራራት ፣ ማሸማቀቅ ብሎም ወደ ወህኒ ቤት መወርወር በእውነት አሳፋሪ ተግባር ነው - መሰበር ያለበት ጭምር ።
ድርጅቱ በዚህ ረገድ ያለው ስዕል የደበዘዘ ነው ። ሲፒጄ ታህሳስ 2013 ባወጣው መግለጫ ከአፍሪካ ብዙ ጋዜጠኞችን በማሰር ኤርትራ ፣ ኢትዬጽያና ግብጽን የሚያህል የለም ። መንግስት በጸረ ሽብር ተግባር አንጂ በጋዜጠኝነት ያሰርኩት ሰው የለም ቢልም ማስተባበያው ለብዙዎች የተዋጠ አልሆነም ። ይህን መረጃ እውነት ነው ብለን ብንቀበል እንኴ በተከታታይ የተፈጸሙ ሌሎች ተግባራት ጥርጣሬ ውስጥ እንድንገባ አድርገውናል ። ለምሳሌ ፍሪደም ሃውስ የተባለው ድርጅት መንግስት 65 የዜናና አስተያየት ፣ 14 የፖለቲካ ድርጅቶች እና 27 ብሎጎች መዘጋታቸውን ግልጽ ማድረጉ ይታወቃል ። መንግስት ከድርጅቶች ጋር በርዕዬተ አለም ልዩነት ብቻ ሳይሆን ወንበርዋን ለዘለዓለም በማስጠበቅ ሹኽቻ ሊኖቆር ቢችልም ከግለሰቦች ጋር ታች ወርዶ የሚፈጥረው ግርግር ግን አሳማኝ አይደለም ። በሌላ አነጋገር የግለሰቦችን ብሎግ መዝጋት የግለሰቦችን እምነት ፣ አስተሳሰብና ፍልስፍና መርገጥ ነው ። የግለሰቦችን ብሎግ መዝጋት በሃሳብ ነጻነት አጀንዳ ዙሪያ ብዙ አለማወቅን ወይም ደንታ ቢስነትን ያመላክታል ። እንደናንተ ሳይሆን እንደእኔ አስቡ ብሎ ፈላጭ ቆራጭ መንገድን ማሳየትን ያስገነዝባል ።
ጸሀፊዎች አቌማቸው ግራም ሆነ ቀኝ ፣ ሊበራልም ሆነ ዴሞክራት ወይም እምነት የለሽ መከበር አለበት ። መንግስት በተሰደበና በተተቸ ቁጥር ብዕረኛን የሚያስር ከሆነ በነጻ ሃሳብን የመግለጽ ትርጔሜ አረዳድ ላይ ችግር አለ ማለት ነው ። እንግዲህ የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎች ከዚህም በላይ ነው የሚሉት ። ይህን ማድረግ ካልተቻለ ግን መብቱን ከህገ መንግስቱ በድፍረት ልጦ ማንሳትን ይጠይቃል ።
መንግስት በሪፖርቶቹና ለውጭ እንግዶች ፍጆታ የፕሬስ ነጻነት ከግዜ ወደ ግዜ እያደገ መምጣቱን ከመናገር ተቆጥቦ አያውቅም ። አዳማጮቹም ዲፕሎማሲያዊ ወጉን ለመከተል ያህል እንጂ ኢትዬጽያ በፕሬስ ነጻነት 137ኛ / ከ 179/ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ሳያነቡ ቀርተው አይደለም - የአለማቀፉ ፕሬስ ነጻነት ሪፖርትን ። ምን ይሄ ብቻ በሞ ኢብራሂም ፋውንዴሽን ተከታታይ ስኮር ካርድ ከ D በታች ውጤት ያላት መሆኑንም ያውቃሉ ። ይህ ሪፖርት የሚዘጋጀው በዴሞክራሲ ፣ ፕሬስ ነጻነትና ሰብዓዊ ልማት ውጤቶች ላይ በመንተራስ ነው ። ቀጣዬቹ አለማቀፍ ሪፖርቶች ደግሞ የከፋ ስዕል ይዘው ለመውጣት የተዘጋጁ ይመስላሉ ። ሰሞኑን ስድስት የዞን ዘጠኝ ጦማሪዎችና ጋዜጠኞች ባልታወቀ ምክንያት እስር ቤት ተወርውረዋልና ።
ዜጎች በታሰሩ በ48 ሰዓታት ውስጥ ፍርድ ቤት የመቅረብ መብት እንዳላቸው ሁሉ የተያዙበትና የተጠረጠሩበት ምክንያት ወዲያው በግልጽ ሊነገራቸው ይገባል ። ሃሳብን የመግለጽ ፣ የማስተላለፍና የማሳወቅ መብት ተገዢነቱም ለብዙሃኑ ነው ። በመሆኑም ቁጥሩ የበረከተ ብሎገርና ጋዜጠኞች ሲታሰሩ ምክንያቱ በግልጽ መነገር ይኖርበታል ። አርብን እየጠበቁ ማሰር ግዜ ለመግዛት የተለመደ ፖሊሳዊ አሰራር እየሆነ መጥቷል ። ህዝብንና ህጋዊነትን ማዕከላዊ አድርጌያለሁ የሚል መንግስት ግን ይህም አንደኛው ተጠየቃዊ መርህ መሆኑን በመቀበል መረጃውን ማስተላለፍ ግድ ይለዋል ።
ያም ሆነ ይህ የዚህ ሁሉ ጠለፋ መሰረታዊ ምክንያት ምንድነው ? እንዲህ ለማለት የምገደደው በመንግስት በኩል መረጃው ለህዝብ ይፋ ስላልሆነ ነው ። የዚህ ክፍተት ተጠያቂ ደግሞ መንግስት ነው ። የማወቅ መብታችንን አፍኗልና ። ስለዚህ ምክንያቱ ምን ይሆን ብሎ መጠየቅ ብቻ ሳይሆን ምላሹን መገመትም ስህተት አይሆንም ።
ከፊታችን ያለው ምርጫ ?
የሰማያዊ ፓርቲ ትከሻ መስፋት ?
የዘጠኝ አመቱ ቁስል ማገርሸት ? ታዲያ የዘጠኝ አመቱን ቁስል በዞን ዘጠኝ ብሎገሮች ማከም ይቻላል ወይም ማጣፋት ? ምንስ ያገናኘዋል ? ይህ ይህ ጠንካራ የጸሀፊዎች ቡድን መርፌ ሲወጉ እንደነበሩ የቀድሞ ፕሬሶች አይነተኛ ሚና ይጫወታል ተብሎ ተሰግቶ ይሆን ? ይሄኛው ግምት ሚዛን የሚደፋ ይመስላል ። ምክንያቱም እስካሁን ለንባብ ባበቋቸው ስራዎች ውስጥ የድርጅቱን ደካማ ጎን በአግባቡ ነቅሰው አውጥተዋልና ። 
ወይ የሀገራችን ፖለቲካ ... የአይኑ ቀለም ያላማረውን ሁሉ ማባረር ... የጠረጠረውን ወይም ያስደነበረውን በተገኘው ስለት
 መውጋት ወይም በሂሳብ ስሌት ማጣፋት ...
 
በዘጠኝ - አንድ ፣ በዘጠኝ - አንድ እንዲሉ ።

ያሳዝናል ።

Tuesday, April 1, 2014

ግብረሶዶማዊነት በሁለቱ ታዋቂ ጻጻሳት ልቦና


የተመሳሳይ  ታ ጋብቻ ህጋዊ የሆነበትን ቀን ተንተርሶ እንግሊዝ ሰሞኑን በግብረሰዶማዊያን ሰርግ ፈንጠዚያ ላይ ነበረች ። በስነስርዓቱ ላይ የተገኙት ዴቪድ ካሜሮን ጥምረቱን « ታሪካዊ » ሲሉ አወድሰውታል ። በምድረ እንግሊዝ ይህን መሰሉ ጥምረት በ2004 የተጀመረ ቢሆንም ወደ ህጋዊ ጋብቻነት የተቀየረው አሁን ነው ።
ይህ ጋብቻ እውን የሆነው የካቶሊኩ ሊቀጻጻስ ፍራንሲስ ታዋቂ አምስት ቃላቶች « ውዳሴ » ገና ባልከሰመበት ወቅት ነው « WHO AM I TO JUDGE » ይላሉ ጆርጅ ማሪዮ በርጎሊዬ - ለመፍረድ እኔ ማነኝ ? እንደማለት ።
ከዛሬ 24 ዓመታት በፊት ናዚር ጋይድ ሩፋኤል በበኩላቸው በእንግሊዝ ተገኝተው የግብረሶዶማዊነትን ኀጢያታዊ ተግባርና የወደፊት አደገኛነት ለታዋቂ ሰዎችና ምዕመናን ትምህርት እየሰጡ ነበር « HOMOSEXUALITY IS AGAINST NATURE » በማለት - ግብረሶዶማዊነት ተፈጥሮን ይቃረናል እንደማለት ። ይህን አባባል ግን ጋዜጠኞች ታዋቂው ባለአራት ቃላቶች በማለት አላወደሱትም ። ደግነቱ ሊቀጻጻስ ሺኖዳ ዛሬ በህይወት ስለሌሉ በዚህ ዜና አያዝኑም ።
እነዚህ ሁለት ጻጻሳት በትህትናቸውና አንቱ በሚያሰኝ ስራዎቻቸው ይመሳሰላሉ ።
ጻጻስ ፍራንሲስ የአርጀንቲና ሊቀ ጻጻስ በነበሩት ግዜ የተለየ ጥቅማጥቅም አያስፈልገኝም በማለት ተራ አፓርታማ ላይ ክፍሎች ተከራይተው ምግባቸውን ራሳቸው እያበሰሉ ፣ ህዝብን መስለው በአውቶብስ እየተጋፉ ነበር የሚጔጔዙት ። የካቶሊክ ሊቀጻጻስ ሆነው ሲሾሙም ቤተመንግስት ከመግባት ይልቅ የቫቲካን ሰራተኞች በሚኖሩበት ህንጻ ላይ መኖርን መርጠዋል ። ለሳቸው ይወጣ የነበረውን የትየለሌ ገንዘብ ለሰብዓዊ ርዳታ እያዋሉ ይገኛሉ ።
ጻጻስ ሽኖዳ የግብጽን በረሃ በመምረጥ የምንኩስና ህይወትን ለብዙ አመታት አጣጥመዋል ። ከግብጽ ውጭ ገዳማትንና መንፈሳዊ ኮሌጆችን በማሰፋፋት መንፈሳዊ እውቀት እንዲጎለበትና ቁጥሩ እንዲጨምር ልዩ ሚና ተጫውተዋል ። ኢል ከራዛ የተባለ ሃይማኖታዊ መጽሄት በማዘጋጀት ብቻ ሳይሆን ከሰፊው ዕውቀታቸው በመጨለፍ 101 የሚደርሱ መጽሃፍትን ለንባብ አብቅተዋል ። ስራዎቹም በልዩ ልዩ ቌንቌዎች ተተርጉመዋል ።
እነዚህ ሁለት ጻጻሳት ከክርስትና ባህር የተቀዱ ቢሆንም ዛሬ አለምን በስፋት እያነጋገረ በሚገኘው ግብረሶዶማዊነት ዙሪያ ያላቸው አመለካከት በፍጹም አይገናኝም ።
ለምን ?
አይታወቅም ።
አንድ መሆን ይጠበቅበት ነበር ?
ቢያንስ በጣም መራራቃቸው እንዴት ? የሚል ጥያቄ እንዲወለድ ምክንያት ይሆናል ።
የአሌክሳንደሪያው ጻጻስ ሽኖዳ ግብረሶዶማዊነት ከተፈጥሮና ከመጽሀፍ ቅዱስ ቃል የሚቃረን በመሆኑ ሃጢያት መሆኑንና አባላቱ መንግስተ ሰማያት እንደማይገቡ ያስረዳሉ ። የካቶሊኩ ጻጻስ ፍራንሲስ የቤተክርስቲያኒቱን መመሪያ በመንተራስ ግብረሶዶማዊነትን በሁለት ከፍለው ነው ሀሳብ የሚሰጡት ። የግብረሶዶማዊነት ዝንባሌ ያለው እንደሃጢያተኛ አይቆጠርም ። ግብረሶዶማዊ ተግባርን የሚፈጽም ግን ሃጢያተኛ ነው ። < ዝንባሌ > የሚለው ቃል እንዴት ሊፈጠር ቻለ ? በግርድፉም ደጋፊነትንና አድናቂነትን ይገልጻል ። የድጋፉ መነሻስ ከምንም ተነስቶ ነው ማለት ይቻላል ? ምናልባት ይህ ደጋፊ ነገ ተጨዋች ለመሆን በእጅጉ የቀረበ ይመስላል ። መገመት የማይቻለው አሰላለፉን ነው - ተመላላሽ አጥቂ ነው ወይስ ቌሚ ተከላካይ ? ወይም እንደ ሚስት ነው የሚተውን እንደ ባል እንደማለት ።
ቅጣቱን በተመለከተም የጻጻሳቱ አመለካከት እንደሰሜንና ደቡብ ዋልታ ጫፎች የተራራቀ ነው ። ሺኖዳ በብሉይ ኪዳንም ሆነ በአዲስ ኪዳን የተወገዘና ክፉ ውጤት የሚያስከትል መሆኑን ያስረዳሉ ። በኦሪት ዘሌላዊያን ምዕራፍ 20 ፡ 13 « አንድ ወንድ ከሌላው ወንድ ጋር የግብረ ስጋ ግንኙነት ቢፈጽም ሁለቱም አስከፊ ነገር ስላደረጉ በሞት ይቀጡ ። ስለመሞታቸውም ኃላፊነታቸው የራሳቸው ይሆናል » የሚለውን ለአብነት ጠቅሰዋል ።
የአዲስ ኪዳኖቹ
ወደ ሮም ሰዎች 1 ፡ 27
ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 6 ፡ 9
የይሁዳ መልዕክት 7 የግብረሶዶማዊነትን ቅጣትና የእግዚአብሄርን መንግስት አለመውረስ የሚያስረዱ ናቸው ።
ፍራንሲስ እነዚህን ጥቅሶች በመተው የተለየ ምላሽ መስጠትን መርጠዋል ። ታዋቂ የተባለውን who am i to judge ? በርግጥ እነዚህ ተሳቢ ቃላቶች ነገር ለማሳመር ተከርክመው ቀረቡ እንጂ ሪሞርኬው ከፊት አለ - እንዲህ ነው ያሉት « አንድ ግብረሶዶማዊ ፈጣሪን ከተቀበለና መልካም ስነምግባር ካለው እኔ ማነኝ እና ነው የምዳኘው ? » አንዳንዶች ይህን አባባል የተጠቀሙት ትህትናን ለማሳየት ነው ሲሉ ሌሎች ደግሞ ህገ መጽሀፉን ለመሸሽ ነው ብለዋቸዋል ።
እዚህ ጋ ፍጥነታችንን አቀዝቅዘን ከሀሳቦቹ  ጀርባ ሊሆን ስለሚችለው ጉዳይ የሆነ ነገር እንበል ። ሽኖዳ መጽሀፍ ቅዱስን ቃል በቃል ጠቅሰው ሞት ይገባል ነው ያሉት ። ኃላፊነቱም የሟቹ ነው ። ህግ ከውሃ የቀጠነ መሆኑ ቢታወቅም እንደዚህ አይነት ውሳኔዎች ወዳልተፈለገና የከፋ ጫፍ እንደሚያደርሱም ይታወቃል ። ምክንያቱም ስሜታዊነትን አቅፈዋልና ። ለአብነት ያህል ኡጋንዳ የጸረ ግብረሶዶማዊነት ህግን ባጸደቀች ማግስት በተነሳ አመጽ አንድ ግብረሶዶማዊ ተቃጥሎ እንዲሞት ተደርጔል ። መቼም የሶዶምና ገሞራ ሰዎችም በዚህ መልኩ ነው የተፈጁት ብለን የምንከራከር ከሆነ የጻጻስ ፍራንሲስ አምስት ቃላቶች ትክክል ናቸው ማለት ነው ። እኛ ማነንና ነው ህግን የተላለፈ ሰው በጣም በተጋነነና ለቀሪው ትምህርት ሳይሆን በሽታ ሊፈጥር በሚችል መልኩ በእሳት የምናቃጥለው ? ህግ በቀለኛ መሆኑ ይታወቃል ። የበቀሉን ጉማሬ ከኃላ ኪሱ የሚያወጣው ግን መጀመሪያ ገስጾና አስተምሮ ነው ። ሰው ሲሞት እንኴን አስከሬኑን የማቃጠል ባህል መቅረት አለበት በሚባልበት ዘመን ህይወት ያለውን ሰው እንደዳመራ በመለኮስ ሰብሰብ ብሎ ወደ ሰሜን ይወድቃል ወይስ ወደ ምዕራብ እያሉ መወራረድ እንዴት ያስደስታል ? ያሰቅቃል እንጂ ።

በሌላ በኩል ጻጻስ ፍራንሲስ እንደቀድሞው ጻጻስ ተጽዕኖው በዝቶባቸዋል አሊያም የሳይንሱን እውነታ እየሸራረፉም ቢሆን መቀበል ጀምረዋል ። እንደሚታወቀው ግብረሶዶማዊነት የምርጫ ጉዳይ ሳይሆን ሆኖ የመፈጠር ነው የሚሉ አንዳንድ ሳይንቲስቶች ጣጣውን የጄኔቲክና ሆርሞን ውጤት አድርገውታል ። ለዚህም ማሳያ ይሆን ዘንድ በክሮሞዞምስ ፣ አእምሮና ሆርሞኖች ላይ ጥናቶች አከናውነዋል ። ለአብነት ያህል 400 የሚደርሱ መንታ ልጆች ላይ የተደረገ ጥናት Xq28 የተባለውን ክሮሞዞም እንደሚጋሩት ያሳያል ። ይህን ክሮሞዞምስ ጥንድ ያልሆኑ ወንድሞች አይጋሩትም ወይም በጥቂቱ ነው የታየው ። በዚህም መሰረት አንዱ ልጅ ግብረሶዶማዊ ከሆነ ሌላኛው ጥንድ የመሆን እድሉ 50 ከመቶ ይደርሳል ። እነዚህና የመሳሰሉት ጥናቶች እውነት ይኖራቸው እንዴ የሚያሰኝ ጥያቄ እየፈጠረባቸው ይመስላል ።
ዛሬ አለምን ጉድ እያሰኘ የሚገኘው ግብረሶዶማዊነት ሳይሆን የግብረሶዶማዊያን የጋብቻ ጥያቄ ነው ። ምክንያቱም ጋብቻ የተባለውን አንጋፋና ህጋዊ ተቌም እየተጋፋ በመሆኑ ። አለም ተቀብሎት የኖረው የጋብቻ ብይን እድሜያቸው ለአቅመ አዳም / ሄዋን በደረሰና በፍቅር በተግባቡ አንድ ወንድና ሴት መካከል የሚደረገው ማህበራዊ ጥምረት ነው ። እነዚህ ጥምሮች ውለዱ ክበዱ የሚለውን የሰርግ ላይ ምርቃት ከአመት በኃላ ተግባራዊ ያደርጋሉ ። ፍሬና ፍቅር ማየት የሰው ልጆች ሁሉ ጸጋ ነውና ።
ዛሬ አንድ ተማሪ « ጋብቻ የሁለት ጺማም ሰዎች ቁርኝት ነው ፣ በፍቅር ለመደንገጥና ለመሳሳብም አጔጊ ዳሌ ፣ እንቡጥ ከንፈር ፣ የተቀሰሩ ጡቶች ፣ ገዳይ አይን ፣ አመለሸጋነትም ሆነ የጎን አካልነት ምክንያት ሊሆኑ አይችሉም ። በግብረስጋ ለመርካት የግድ ወርቃማ ምንተሃፍረቶች አያስፈልጉንም - ማንኛውም ቀዳዳ እንጂ » የሚል መመረቂያ ጽሁፍ ቢሰራ ማነው ትክክል አይደለም የሚለው ? ጋብቻ በትርጉም ብቻ ሳይሆን ቀጥሎ በሚመጣው ቤተሰባዊ ተቌምነቱም እየተኮማተረ ነው ። ህንጻው ውስጥ ከወጉ ፣ ከእምነትና ስርዓቱ ፣ ከባህሉና ከአኗኗር ዘይቤው ጋር የማይመሳሰል ምናልባትም የሚቃረን ደባል ሰተት ብሎ ገብቷል ። ትግሉ ከቀዝቃዛው ጦርነት በላይ የጦዘውም ለዚህ ነው ።
ውጣልኝ !  - አልወጣም !
በህግ አምላክ  ?! - በህግማ ነው የመጣሁት !
እረ የሀገር ያለህ ? የመንግስት ያለህ ? - ነባሩ ትዳር በስቃይ ተተብትቦ ነጋ ጠባ ሊጮህ ነው ። ቆይቶ የሚያገኘው ፖለቲካዊ ምላሽ « ተቻችላችሁ ኑሩ  - ተከባበሩ » የሚል መሆኑ አያጠራጥርም ።
እዚህ ላይ ጻጻስ ፍራንሲስ ጋብቻን በተመለከተ አስገራሚ ለውጥ ማድረጋቸውን ማስታወስ ያስፈልጋል ። የአርጀንቲና ጻጻስ በነበሩበት ግዜ « ይህ የፈጣሪን እቅድ የማጥፋት ዘመቻ ነው » በማለት ነው ተቃውሟቸውን በግልጽ አሰምተዋል ። የካቶሊክ ሊቀ ጻጻስ ሆነው ከኢጣሊያኑ ኮሬ ዴላ ሴራ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ « ጋብቻ በአንድ ወንድና ሴት የተወሰነ ነው ፣ ነገር ግን ቤተክርስቲያናችን የተመሳሳይ ጾታን ጥምረት በተለይም ከህክምና አገልግሎትና ከንብረት ባለቤትነት አንጻር መደገፍ አለባት » በማለት ልዩ ጉዳዮች በልዩነት የሚመዘኑበት ሁኔታ መኖሩን ተናግረዋል ።
ሺኖዳ ፍቅር መንፈሳዊና ንጽህ ከመሆኑ አንጻር በሁለት ተመሳሳይ ጾታ መካከል የሚደረግ ጥምረትን የሚበይኑት ዝሙት በማለት ነው < ግብረሰዶማዊነት ተፈጥሯዊ እኮ ነው ? > የሚል ጥያቄም ቀርቦላቸው ነበር ። አንድ ሰው በዚያ መልኩ ከተፈጠረ መጸለይ ፣ መፈወስ በህክናም ማስተካከል ይቻላል ባይ ናቸው ። ይሁን እንጂ ቤተክርስቲያን ሰዎች በዚህ መልክ ይፈጠራሉ ብላ እንደማታምን ይልቁንም ዝሙት መሆኑን በምሳሌ ማስረዳት መርጠዋል ። ቅዱስ አውግስቶ እና ቅዱስ ፓለጊያ ዝሙት ፈጻሚዎች ነበሩ ። ኃላ ቅዱስ እስከመባል የደረሱት በመጥፎ ተግባራቸው ተጸጸተው ራሳቸውን በማስተካከላቸው ነው ።
የግብረሶዶማዊያን ነገር « ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡ ? ውሃ ቢያንቅ በምን ይውጡ ? » አይነት ደረጃ የደረሰ ይመስላል ። ምክንያቱም የተቀጣጠለውን እሳት በማጥፋት ረገድ የእሳት አደጋ ተከላካይ ባልደረባ በመሆን ትልቅ ሚና ይጫወታሉ ተብለው የሚገመቱት ቄሶች ራሳቸው የእሳት ራት በመሆናቸው ።
ልክ እንደ ሺኖዳ ሁሉ የቀድሞው ጻጻስ ቤንዲክት XVI የግብረሶዶማዊነት ጥልቅ ዝንባሌ ያላቸው ሰዎች ቄሶች ሊሆኑ አይችሉም ብለው ፈርመው ነበር ። ጻጻስ ፍራንሴስ ግን ግብረሶዶማዊያን ቄሶች ይቅርታ ያገኛሉ የሚል አስተያየት ሰጥተዋል ። ጻጻሱ እንዲህ የተናገሩት ተቸግረው ይመስላል ። ምክንያቱም በሮማን ካቶሊክ የግብረሶዶማዊያን ቄሶችን ቁጥር በትክክል ማወቅ አስቸጋሪ ቢሆንም በርካታ መሆናቸው ብዙዎችን ያስማማልና ። ሌላው ቀርቶ በአሜሪካ ከ1970 እስከ 80ዎቹ በነበሩት ግዜያት በሎስ አንጀለስ ታይምስ በተደረገ ጥናት 1854 ቄሶች ራሳቸውን ግልጽ አድርገዋል ። ይህም በአሜሪካ ብቻ 33 ከመቶ የሚደርሱ ቄሶች ግብረሶዶማዊያን መሆናቸውን ያመለክታል ። ይህን አሃዝ 1 ነጥብ 2 ቢሊየን ተከታዮችን በምትመራው ካቶሊክ መካከል መመዘን የአደጋውን ስፋት በግልጽ ሊያመላክት ይችላል ።
በርግጥ የሁለቱ ጻጻሳት የተለያየ ምስጢር ምንድነው ?
አንዱ ለዘብተኛ ሌላው አክራሪ ስለሆነ ?
አንዱ የምዕራቡ ዓለም የስልጣኔ ውጤት ሌላው የአፍሪካ ኃላቀር ባንዲራ አራጋቢ ስለሆነ ?
አንዱ የተጽዕኖ ውጤት ሌላኛው በራሱ የቆመ ስለሆነ ?
ከእነሱ እምነትና አስተሳሰብ በመነሳት የነገዋን አፍሪካ መገመት ይቻላል ?
አይታወቅም ።


Tuesday, March 25, 2014

ወደ ባልዲው ነዎት ወደ ተራራ ?


እህል ውሃዬ አዲስ ዘመን በነበረ አንድ ቀን ድድ ማስጫ የምንላት ቦታ ላይ ገሚሳችን የተበላሹ ሞተር ሳይክሎች ወገብ ላይ ፊጥ ብለን  ሌሎች እንደቆሙ ክፉ ደጉን እንቀድ ነበር ። አንዱ ደራሲ ወደቢሮ እየመጣ ነው ። ቢሮ ለመግባት ድድ ማሰጫውን ማለፍ አለበት ። ለካስ አንዱ ደራሲ አትኩሮ እየተመለከተው ኖሯል « እዩት እስኪ » አለን በአገጩ ወደ ሰውየው እየጠቆመን « የተገለበጠ ኤሊ አይመስልም ? » ያልጠበቅነውን ተረብ መሃላችን ዘረገፈው ። በአንድ በኩል ድንጋጤ ቢወረንም በአካባቢው ታላቅ ነውጥ የፈጠረውን ሳቅ መቆጣጠር አልቻልንም ። የተበላሹት ሞተሮቹ ሳይቀሩ ሲንተፋተፉ ተሰማ ።
እኔን በወቅቱ የገረመኝ እንዴት አሰበው ? የሚለው ጥያቄ ነበር ። መጀመሪያ ኤሊዋን አመጣት ፣ ይህ አልበቃው ብሎት ገለበጣት ። የተረገመ ! ከዚያ በኃላማ ለተወሰነ ግዜ ተቸግሬ ነበር - ሰውየውን ባየሁት ቁጥር ምስሉ እየመጣብኝ ። ዛሬ አንደኛው በኢትዮጽያ ምድር የለም ፣ ሌላኛው በመላው ዓለም አይገኝም ። ፓ ! ሁለቱም ታዲያ ምርጦች ነበሩ ።
አዲስ ዘመንን « የስጋ መጠቅለያ » እያሉ ቁምስቅሉን የሚያሳዩት ጸሀፊዎጭ ይኀው ተረብ አላጠግብ ብሏቸው አንዱን ደራሲና ባልደረባችንን « ወደ ስምንተኛው ገጽ ይዞራል ፊት » ማለታቸውን የሰማንና ያነበብን ግዜም እንዲሁ ለአንድ ሳምንት በሳቅ ተንፈቅፍቀናል - ሞራል ቢገርፍም መሳቅ ጥሩ ነው በሚል ። የጥንት ቻይናዊያን የሰው ልጆችን ፊት በመመልከት መተረብ ብቻ ሳይሆን ውስጣዊና ውጫዊ ባህሪያትንም ይተነትኑበት ነበር ። ንጉስ ሲን - ቺ - ዋንግ / 221 BC / ፊትን የማንበብ ጥበብ ተጽዕኖ አሳድሮበት እንደነበር ድርሳናት ያስረዳሉ ። የፈት ቅርጾች በስያሜ ተከፋፍለው የተቀመጡ ሲሆን አጠቃላይ የሆነ ምንባብም አላቸው ። ይህ አጠቃላይ ምንባብ የሚዘረዘረው ደግሞ ፊት ላይ ያሉት አነስተኛ አካላት ሲመረመሩ ነው ። በዚህ ረገድ ግንባር ፣ ሽፋሽፍት፣ አይን ፣ አፍንጫ፣ ጥርስ ፣ ጉንጭ ፣ ከንፈር ፣ ጀሮና አገጭ ምን ሲመስሉ ምን እንደሆኑ የሚያብራሩ ብይኖች ተቀምጠዋል ። ለምሳሌ በጋዜጠኞችም ሆነ በኪነጥበብ ሰዋች ብዙ ያልተዘመረለት ሽፋሽፍት ስስ ሲሆን ምን ማለት ነው ...  ወፍራም ሲሆንስ ? ሲራራቅ ... ሲገጥም ? የጨረቃ ቅርጽ ሲይዝ ... ትሪያንግል ሲመስል ? ቀጥ ሲል ... ሲንጨባረር ? ወደላይ ሲሰቀል ... ወደታች ሲደፋ ? አንድም እንዲህ የሆነበት አንድም ያዘለውን ትርጉም ለቀቅ ባለ መልኩ ያጫውቱናል ። ሌሎቹንም እንዲሁ ።
ይሄን ሁሉ የሚያወራውን መጽሀፍ  ያነበብኩት ባለፈው ሳምንት ነው ። ከዚያ በፊት ቤንጃሚን ዚፋኒያ የተባለ ጸሀፊ የኤርትራና ኢትዮጽያ ዜግነት ያለው የአንድ ቤተሰብ ቡድን በባድመ ጦርነት በሁለቱም ሀገሮች መንግስትና ህዝብ የደረሰበትን ድርብ ሰቆቃና ፈታኝ ህይወት በሚያስተክዝ መልኩ Refugee Boy በሚል ርዕስ ጽፎት አንብቤው ድብርት ወስጥ ነበርኩ - ግሩም ስራ ነው ።  ቀጣዩ መጽሀፍ ይህን የሚኮሰኩስ ስሜት ነበር በፈገግታ ብሩሽ ማሰማመር የቻለው « The Secret Language of Your Face » ይባላል ። ፈልገው ቢያነቡት ይዝናኑበታል ። ራስዎትንና ጔደኞችዎን መስታውት ውስጥ በማስገባትም ማነጻጸር ይችላሉ ። ያለማመን መብትዎ እንደተጠበቀ ሆኖ ማለት ነው ። ለዛሬ ግን መጽሀፉ ስለፊታችን የሚለውን ብናነብስ ?
ጨረቃ ፊት ፣

ትልቅና ክብ ጭንቅላት አላቸው ። የጨረቃ ፊት ያላቸው ሰዎች ልፍስፍነት ፣ ንቁ ተሳታፊ ያለመሆንና እንደነገሩ መልበስ ይታይባቸዋል ። ብዙ በመብላትና በመጠጣት ደስታን መፍጠር ይፈልጋሉ ። ደረጃቸው ዝቅ ያሉ ምግቦችን ሁሉ በመውሰድ የሚታወቁ መሆኑ ብዙ ሊያስገርም አይችልም ። ያገኙትን ገቢ በማድረጋቸው የኃላ ኃላ ለአስቸጋሪ ክብደት መጨመርና ዘርጣጣነት  ይዳረጋሉ ።
ልዩ ክህሎታቸው ከሰዎች ጋር በሚያደርጉት ግንኙነት ዲፕሎማት ሆነው መፈጠራቸው ነው ። በስራ ረገድ ወንዱ ጨረቃ ፊት ጥሩ የንግድ ሰው ይወጣዋል ። ፈጣን የገበያ ልውውጥና ውጤት በሚያሳዩት አይነቶቹ ስራ ላይ እንጂ ትላልቅ ስራዎች ውስጥ ኃላፊነት ወስደው ለመግባት ጠርጣራ ናቸው ። ሴቷ ጨረቃ ፊት በስራ ረገድ ግዴለሽነት ይታይባታል ። ጥቅሞቿን በመከታተልና በመቆጣጠር ረገድ ዝንጉ ናት ፣ የዚህም ዋናው ምክንያቱ ስለራሷ ለማሰብ ረጅም ግዜ የምታጠፋ በመሆኑ ነው ። ስለሆነም ከፍ ባለ አስተዳደራዊ ስራ ላይ ለመገኘት አትችልም ።
ከግል ህይወት አንጻር የተናጥል ኑሮን መምራት ያስደስታቸዋል ። ወንዶቹም ሆነ ሴቶቹ እስከ አርባዎቹ ድረስ ትዳር ላይዙ ይችላሉ ። የዚህ መነሻው ደግሞ በወጣትነት ግዜያቸው ተቃራኒ ጾታን ችላ ብለው ማሳለፋቸው ነው ።
ብረት ፊት ፣
ሁለት አይነት ብረት ፊቶች አሉ ። አንደኞቹ አጭር ፊትና የሞላ ጉንጭ ያላቸው ናቸው ። አነዚህኞቹ ጤናቸው የማያስተማምን ሲሆን በተለይም በሆድ ችግር ይጠቃሉ ። ሁለተኞቹ ረጅም ፊት ያላቸው ሲሆን ቁመታቸውም ከስድስት ኢንች ሊበልጥ ይችላል ። በባህሪ ረገድ ራስ ወዳድነትና ከነገሮች ጋር አብሮ ያለመሄድ እንከን ይታይባቸዋል ። ብረት ፊቶች ለፍትህና ትክክል ነው ብለው ላለመኑበት ጉዳዮች መስዋዕትነት ከመክፈል ወደ ኃላ አይሉም ። ራሳቸውን እንደማስገረምና ማስደነቅ የሚያስደስታቸው ነገር የለም ። ሌላው ቢቀር ሰዎችን ሰብሰብ አድርገው በቀልዶቻቸው እንዲደሰቱ ማድረግ ያስፈነጥዛቸዋል ።
ጥሩ የሚባል እውቀት ቢኖራቸውም ራሳቸውን የሚመሩት በደመነፍስ ነው ጥሪታቸውን ያለስጋትና ፍርሃት እንዴት ማዋል እንደሚገባቸው ቢያውቁም አሁንም የሚያዳምጡት እውቀታቸውን ሳይሆን ደመነፍሳቸውን ነው   ፖለቲከኛና የህግ ሰው የመሆን ዝንባሌያቸው የላቀ ነው ። በአማካኙም ይህን የመሰለ ፊት ያላቸውን ሰዎች ፍርድ ቤቶችና ፓርላማ አካባቢ መታዘብ ቀላል ነው ።
ጄድ ፊት ፣

የተመጣጠነና አይን ግቡ የሆነ ገጽታ ያላቸው ሲሆን ጉንጫቸው አካባቢ የክብነት ቅርጽ ይታይባቸዋል ። ሴት ጄድ ፊቶች ከአንድ በላይ የሆነ መታጠቢያ ክፍል እንዲኖራቸው ቢፈልጉ አይገርምም ። ምክንያቱም ክፍሎቹ ቁንጅናና ስነውበትን የሚያደምቁ ቁሳቁሶች የሚሞሉበት ስለሆነ ።
እነዚህ ሰዎች ለህይወት ያላቸው አመለካከት ቀናማ ሲሆን ስሜታቸውን በፍጥነት ለማሳየት ወደኃላ አይሉም ። ሴቶቹ ትልቅ ትጋትና ጥረት ስላላቸው በማህበራዊ ህይወት ውስጥ ከፍ ያለ ቦታ ይደርሳሉ ። ይሁን እንጂ ማህበረሰቡ እብሪተኛ ወይም ይሉኝታ ቢስ በሚል ያልተገባ ሀሜት ያቆስላቸዋል ። ጄድ ፊቶች በስራ ረገድ ከፍተኛ ችግርና ውጤት ሲያጋጥማቸው እንኴ ተስፋ አይቆርጡም - እድሜ ለጠንካራ አቅማቸው ።
ወንድ ጄድ ፊቶች ከፍተኛ የሆነ የሀገር ፍቅር ስሜት አላቸው ። ለዚህም ይመስላል ብዙዎቹ በመከላከያ ሰራዊት ውስጥ የሚገኙት ። የፍቅር ግንኙነትን በተመለከተ ተጣማሪያቸው ከፍተኛ ፍቅርና እንክብካቤ እንዲያደርግላቸው ይሻሉ ። ይህ ፍቅራዊ ስሜት ካልተሟላ ሀዘናቸው ወዲያው ነው የሚታየው ።
ባልዲ ፊት ፣
 
ባልዲ ፊቶች ውሃ ፊትም በመባል ይታወቃሉ ። የሰፊ ግንባርና ትኩረት ሰራቂ አይን ባለቤት ናቸው ። ያላቸውን እውቀት በመጠቀም የሚከበር ውጤት ይጨብጣሉ ። ይሁን እንጂ በሀዘንና ትካዜ የተከበበ ህይወትም ይኖራሉ ፣ በዚህ ወቅት ውጤታማነታቸው በፍጥነት እያሽቆለቆለ ይወርዳል ። ከዚህ አሉታዊ ስሜት ውስጥ ለማውጣት የሚታገል ሰው ቢኖር እንኴ  ጥረቱ በቀላሉ እውን የሚሆን አይደለም ።
በቅርብ ጠጋ ብሎ ውስጣቸውን ለመረዳትም ረጅም ግዜያትን ይጠይቃል ። ባልዲ ፊቶች ብዙ ጔደኞች አሉን ብለው ቢያስቡም ይህን ጥበብ ወደላቀ ደረጃ ለማድረስ ከሌላቸው አቅም ጋር ብዙ ግዜ ይጋጭባቸዋል ። ሴቶቹም እንዲሁ የፈጣሪነት ጸጋ የተላበሱ ናቸው ። ይህን ጸጋ በትክክል መጠቀም ከቻሉ በተለይም መድረክ ላይ በሚሰሩ ስራዎች ስመጥር ሊሆኑ ይችላሉ ።
ፋየር ፊት ፣

እንቁላል የመሰለ ጭንቅላት ፣ ሰፊ ግንባርና የሾለ አገጭ አላቸው ። እውቀታቸው የላቀና አስገራሚ ነው ። ባህሪያቸውም ተለዋዋጭ ነው ። ብዙ ግዜም በበርካታ ሀሳቦች የሚንተከተኩ ሲሆን ወደ ተግባር ለመለወጥም ጥረት ያደርጋሉ ።
የበርካታ አዎንታዊ ዝንባሌ ባለቤቶች ቢሆኑም ሁልግዜም ከመጥፎ ሰዎች ጋር በጔደኝነት ይወድቃሉ ። ይህም የሚሆነው ሰዎችን የሚያነቡት በውጫዊ ገጽታቸው ብቻ በመሆኑ ነው ። ከፍተኛ ችግራቸው ግን እፍረት የማያውቀው የማጋነን ባህሪያቸው ነው ። ፈጣን ብቃት ቢኖራቸውም አንዳንዴ የስልጣን ረሃባቸውን በግልጽ እስከማየት ሊደርሱ ይችላሉ ።
ፋየር ፊቶች የፍቅር ስሜታቸውንና ምኞታቸውን በመግለጽ ረገድ ችግር ያጋጥማቸዋል ። ይህን በቅጡ ከመረዳት ይልቅ በፍቅር ህይወት ረጅም ግንኙነት የሚያሳልፉት ሌሎች ናቸው በማለት እድላቸውን ይወቅሳሉ ። ይሁን እንጂ ዘግይተውም ቢሆን ጥልቅ ፍቅር እንዲያጡ መሰረት የሚሆናቸው የራሳቸው ተጠራጣሪነት መሆኑን ይቀበላሉ ።
መሬት ፊት ፣


ግንባራቸው ጠበብ ብሎ ጉንጭ አካባቢ ሰፋ ይላሉ ። መሬት ፊቶች ምስቅልቅል ባለ አቌም የሚገለጹ ናቸው ። በመጠኑም ቢሆን በፍቅር እጦት ያደጉ በመሆኑ ሊሆን ይችላል ። አክብሮት የማያሳዩ ሲሆን ምላሽ የሚሰጡትም ስርዓትን በጣሰ መልኩ ነው ። አንዳንዴም ስድብንና ኃይልን ከመጠቀም ወደ ኃላ አይሉም ። በዚህም ምክንያት ብዙ ግዜ ጔደኝነትን ለመመስረት ይቸገራሉ ።
ሊጠቀስ የሚችለው አዎንታዊ ባህሪያቸው ታላቅ የእውቀት ጥማት ያለባቸው መሆኑና ይህን ችሎታ በተግባር ለማስደገፍ በትዕግስት የመጠበቅ ዝግጁነታቸው ነው ። መሬት ፊቶች ከተጣማሪያቸው ጋር ያላቸው ግንኙነት በግንፍልተኝነት የሚገለጽ ነው ።  ብዙ ግዜም በሰላም አውለኝን ከመግለጽ ይልቅ በቁጣ አለመስማማትን መግለጽ እለታዊ አጀንዳቸው ይመስላል ። ነገር ግን ሁለት ተቃራኒ መሬት ፊቶች በፍቅር የሚወድቁ ከሆነ አለምን ለመቀየር አያመነቱም ።
ግድግዳ ፊት ፣

ከግንባራቸው እስከ አገጫቸው ያለው ርቀት በጣም አጭር ነው ። ነገር ግን ፊታቸው ከጃልሜዳ ይዛመዳል - ሰፊና ደልዳላ ነው ። በል ያላቸው ግዜ ጠንክረው ይሰራሉ ። ነገር ግን ገልጃጃ የሚመስለው ጠባያቸው ወደ ስንፍናና ጭንቀት እንዲያመሩም ተጽዕኖ ይፈጥራል ። ለምሳሌ ጠንካራ ችግር በገጠማቸው ግዜ ራሳቸውን መቆጣጠር አይችሉም ። ይህም ነገሮችን ጠርጣሪዎች በመሆናቸው የሚፈጠር ሲሆን ትዕግስት አልባም ይሆናሉ ።
እንደዚህ አይነት ሰዎች ሃሳባቸውን ወደ ተግባር የመለወጥ ችሎታ ያንሳቸዋል ። ግድግዳ ፊቶች በፍጹም ባለስልጣን መሆናቸው ጥቅም የለውም ። ይሁን እንጂ በአንድ የሆነ ምክንያት ውስጣቸው ያለውን አቅም ጥቅም ላይ ማዋል ከቻሉ በጣም ታዋቂና የመገናኛ ብዙሃን ከከቦች ነው የሚሆኑት ።
በቤተሰብ ውስጥ ችግር ከተፈጠረ በአክብሮት የሚበረከተው ቀይ አበባም ሆነ ፍቅሩ እንዳይሞት የሚደረጉ ቃል የመግባት ስርዓቶች የተጋረጠውን አደጋ ፈቀቅ አያደርጉትም ። ግድግዳ ፊቶች ያለውን ግንኙነት ጠግኖ ወይም አጠናክሮ ጥቅም ላይ ከማዋል ይልቅ በእድላቸው በማለቃቀስ ሌላ ፍቅረኛ መፈለግን ይመርጣሉ ።
ተራራ ፊት ፣

ግንባራቸው ወደ ላይ እየጠበበ የሚወጣ ሲሆን በተቃራነው ጉንጫቸው ከመሬት ፊቶች የበለጠ ሰፊ ነው ። በወጣትነት ዘመን ያሳለፉት ግዜ ብዙም አርኪ ባለመሆኑ ፣ ከቤተሰብ ጋር የነበራቸው ቁርኝት ልል ስለነበር እንዲሁም በአቅም ውስንነታቸው ምክንያት የረባ ጔደኝነት ለመመስረት ሲያስቸግራቸው የቆየ ነው ።
ደካማ ጎናቸውን የሚቀበሉ ከሆነ ግን ውጤታማ ለመሆን ቅርብ ናቸው ። ለሚሰሩት እያንዳንዱ ነገር ክብርና ዋጋ ይፈልጋሉ ። ጠብ ጫሪታቸው ግን እንደ ማስታወቂያ አደባባይ የወጣ ነው ። በማህበራዊ ተሳትፎ ውስጥም የሚገኙት በጣም ውስን በሆነ ግዜ ነው ። ገለልተኛ መሆን ይፈልጋሉ ። በተለይም ሀሜትን ለመራቅ ጥረት ያደርጋሉ ። ተራራ ፊቶች ወደ ግንኙነት የሚገቡት በገንዘብ ድጋፍ ቃል ሲገባላቸው ብቻ ነው ።
ያልተመዛዘነ ፊት ፣

ብዙ ሰዎች ያልተመዛዘነ የፊት ገጽታ አላቸው ። ለምሳሌ ያህል ግማሹ የፊት ገጽታ ከሌላኛው ረጅም ወይም ሰፊ ሊሆን ይችላል ። ወይም ደግሞ አፍ ወይም አፍንጫ የተጣመመ ይሆናል ። ቻይናዎች ያልተመዛዘነ የፊት ቅርጽ ውጫዊ ማንነትን ብቻ ሳይሆን የውስጣዊ ገጽታችንም መስተዋት ነው ባዮች ናቸው ።
ያልተመዛዘነ ፊት ያላቸው ሰዎች ከፍተኛ የሆነ የፋሽን ፍላጎት አላቸው ። ገንዘብ ያባክናሉ ። ስራቸውን ግን በአግባቡ ያከናውናሉ ። የተዝናና የፍቅር ህይወት መምራት የትርፍ ግዜያቸው አቢይ ተግባር ይመስላል ። በቀላሉ ከተቃራኒ ጾታዎች ጋር መግባባት ይችላሉ ። አንዱ ቢያልቅ ወይም ባይሳካ እንኴ ቀጣዩን ለመያዝ ብዙ አይቸገሩም ። ደሞ ለሴት ... ደሞ ለወንድ የሚሉ አይነት መሆናቸው ነው ። ይሁን እንጂ ማንኛውም ሰው ሌላው ቀርቶ ራሳቸው ያልተመዛዘኑ ፊቶች ጋብቻ ለምን እንደማይሳካላቸው ወይም ለምን እንደማይስማማቸው አያውቁም ።
እህስ የለመዱትን አይነት ገደል ፊት ፣ ጅብ ፊት ፣ ጨ ፊት ፣ ፈረስ ፊት ወዘተ አላገኙትም ወይስ ተጠማዞ ነው የመጣው ? እስኪ ፊትዋን አትኩረው ይመልከቱት ... ማንም ቦሃቃ ፊት ተነስቶ ሽልጦ ወይም ተራራ ፊት ቢልዋት ፊትዋ ለራስዋ የማይጠገብና ውብ ነው ...


Tuesday, March 11, 2014

እረኞቹ ምን እያደረጉ ነው ?





ፓሰተር የሚለው ቃል ምንጩ ላቲን ሲሆን ትርጔሜውም ጠባቂ ወይም እረኛ ማለት ነው ። እረኛ የሚለው ቃል በመጽሀፍ ቅዱስ ውስጥ 27 ግዜ ተጠቅሷል ።
በሀዲስ ኪዳን መጻህፍት ውስጥም በተለይም ወደ ኦፌሶን ሰዎች/ 4 ፡ 11 / በሀዋርያት ስራ / 20 ፡ 28 / እና የጼጥሮስ መልዕክት / 5 ፡ 2/ ላይ ፓስተር የሚለው ቃል ከመምህርነት ጋር ተያይዞ ቀርቧል ማለት ያስደፍራል ። ለአብነት ያህል በሀዋርያት ስራ ላይ « የእግዚአብሄርን ቤተክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጻጻሳት አድርጎ ለሾመበት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ » የሚለውን ጥቅስ እናነባለን ። በሌሎቹ ጥቅሶች ላይ ደግሞ መንጋውን ጠብቁ የሚላቸው ሽማግሌዎችንና አስተማሪዎችን ነው ።
ዞሮ ዞሮ በፈጣሪ ትልቅ ቦታ የተሰጣቸው ቄሶችም እንበላቸው ፓስተሮች የእግዚአብሄርን መንጋ እንዲጠብቁ ከፍተኛ ኃላፊነት ተጥሎባቸዋል ። በጼጥሮስ መልዕክት ምዕራፍ 5 ላይ ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ የሚለውን ሀረግም ለዚህ አባባላችን ማጠናከሪያ መጠቀም እንችላለን ። ታዲያ እረኞቹ ምን እያደረጉ ነው ? እያስተማሩም እየተመራመሩም ... እያገዱም እያንጋደዱም ይመስላል ። በተለይ በአንዳንዶቹ ላይ
አፈንጋጭነት ፣
ራስን ቅዱስ አድርጎ መሾም
እና ያልተገባ ተግባር መፈጸም በተደጋጋሚ እየታየ ነው ። የጥቂት ወራቶችን ጥቂት አስገራሚ አብነቶችን እየመዘዝን ለምን ቆይታ አናደርግም ? በጣም ጥሩ ...
ደቡብ አፍሪካዊያኑን ፓስተር ሌሴጎ ዳንኤልን እንመልከት ። በቅርቡ « እግዚአብሄርን መቅረብ ከፈለጋችሁ ሳር ብሉ » የሚል ትዕዛዝ በማስተላለፉ ጉባኤተኛው ሳሩን ሲያሻምደው ውሏል ። አንዳንዶቹ ታመው ወደ ሆስፒታል ቢሄዱም አንዳንዶቹ የፓስተሩን ተግባር ደግፈው ሲከራከሩ ነበር « የፈጣሪ ኃያልነትን ማሳያ በመሆኑ ሳር በመብላታችን እንኮራለን ፣ ማንኛውንም ነገር እናደርጋለን » ብላለች አንዲት የህግ ተማሪ
እንግዲህ ይህ ፓስተር ትዕዛዙን የፈጸመው መንፈስ ቅዱስ በራዕይ ተገልጦለት መሆኑ ነው ። በከፋ የረሃብ ዘመን የሰው ልጆች ህይወታቸውን ለማቆየት ርስ በርስ ከመበላላት አልፎ ተሞክረው የማያውቁ ስራስሮችን ለጠኔ ማስታገሻነት ሙከራ አድርገዋል ። በመጽሀፍ ቅዱስ ታሪክም እንደ በሬ ሳር እንዲበላ የተፈረደበት ንጉስ ናቡከደነጾር ነበር ። እሱም ለዚህ ቅጣት ያደረሰው ስልሳ ክንድ የሚያህል የወርቅ ምስል አሰርቶ ለምስሉ እንዲሰግዱ የታዘዘውን አዋጅ የተላለፉ ሰዎችን በግፍ በእሳት በማቃጠሉ ነው ። ስለዚህ < ሳር > የቅጣት ምልክት እንጂ የፈጣሪ መቅረቢያ ስጦታ አይደለም ። የሰው ልጅ አንጀት ሊፈጨው የማይችለውና መጠነኛ መርዛማ ባህሪ ያለውን ሳር መመገብ ሳይንስም አይቀበለውም ።
ባለሁለት እግራሙ የሰው ልጅ ቀሪውን ሁለት እግር ከእጁ ተበድሮ እንደ በግ ሳር ሲግጥ ማየት ሞራላዊና ተፈጥሯዊ ውድቀት ነው ። በዚህ ስሌት ባልታሰበ ሰዓት ሽንት እያሸተተ እንደ በግ ሲያገጥና አባሮሽ ሲጫወት ማየት ይቻላል ። የፓስተሩ የፈጣሪ መቅረብ እሳቤ ሳርን ለአንድ ቀን እንደ ስለት ጧፍ አብርቶ ለማምኖ መለያየትን ብቻ የሚያሳይ አይመስልም ። ምናልባትም ከጥቂት ወራቶች በኃላ ደፋር ነውና  « በግ » ስለሆናችሁ ቤዛነትንም እንለማመድ ብሎ ካራ ሊያስታጥቅ ይችላል ። ይህን የሚደግፍ አንቀጽ ደግሞ አያጣም ። ኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ 22 ፡ 1 – 2  እንዲህ ይላል « የምትወደውን አንድ ልጅህን ይስሀቅን ይዘህ ወደ ሞሪያም ምድር ሂድ ፣ እኔም በምነግረህ በአንድ ተራራ ላይ በዚያ መስዋዕት አድርገህ ሰዋው » ፓስተር ሌሶጎ እኔ የአብርሃም እናንተ ደግሞ የይስሀቅ ምሳሌ መሆናችሁን አትዘንጉ ካለ የህግ ተማሪዋን ጨምሮ ሌሎቹም ድጋፍ ከመስጠት ወደ ኃላ አይሉም ማለት ነው ።
የኬንያው ፓስተር ኖሂ « ሃይማኖታዊ » ግኝት ደግሞ የሴቶች አለባበስ ላይ ያተኮረ ነው ። ፓስተሩ አንድ ቀን በ « lord ‘s propeller redemption church » የሚታደሙ ሴቶች በሙሉ ፓንት ማድረግ የለባቸውም ሲል ትዕዛዝ ሰጠ ። ምክንያት ሲባል ቅዱስ መንፈስን ለማቅረብ ፣ በአጠቃላይ አምልኮ ከጭንቅላትና ከሰውነት ነጻ ሆኖ ማሰብን ስለሚፈልግ የውስጥ ቁምጣቸውን ቤት ትተው መምጣት ይኖርባቸዋል ።
የፓስተሩን ግኝት የመነሻና መድረሻ ክር ይዤ ለማገናኘት ሌት ተቀን ብማስን ውሉን ማግኘት አልቻልኩም ።
ምን ለማለት ፈልጎ ነው ?
ከምን አንጻር ተመልክቶት ይሆን ? መንፈስ ቅዱስ የህሊናችንን በር ሲያንኴኴ ቶሎ የማናዳምጠው ፓንት መጥፎ ጋርድ እየሆነ ነው ? የሚል አስመስሎበታል ። ይህ ቦታ ከነስሙ « ሃፍረተ » እንጂ « ቤተልሄም » ወይም « ጎለጎታ » አይደለም ።
ታዲያ እንዴት መረጠው ? በጣም የሚያስደንቀው ደግሞ የፓንት ማውለቁ ትዕዛዝ ወንዶችን የማይመለከት መሆኑ ነው ።
ለነገሩ የአሜሪካዊውን ፓስተር አለን ፓርከር ግኝት ብናዳምጥ የላይኛውን « እረ ይሻላል » ማለታችን ይጠበቃል ። በቨርጂኒያ የ « white tail chapel » መሪ የሆኑት ፓስተር ትዕዛዝ ደግሞ ጉባኤተኛው ስብሰባውን ራቁቱን ሆኖ እንዲከታተል መገፋፋት ነው ።
የጼጥሮስ መልዕክት ምዕራፍ አምስት « ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ » ተፈጻሚ ይሆን ዘንድም ፓስተሩ ራቁታቸውን በመሆን ትምህርት ሰጥተዋል ። እረ ጥንዶችንም ለጋብቻ ራቁታቸውን  አማምለዋል ። ከተወለድን ከጥቂት ወራት በኃላ እረኞች ለክርስትናችን ውሃ ውስጥ ፣ እናቶች ለመጪው ህይወታችን ተድላ እንጀራ ላይ ሊያንከባልሉን እንደሚችሉ ነው መረጃው ያለን ። ይኀው ቃልኪዳንም የጸና ማህተም ይፈጥርልናል ብለን ነው ተስፋ የምናደርገው ። አድገን በውሃ የተረጨነውንም ሆነ እንጀራ ላይ « ግፍ » ሳይሆንብን የተንደባለልነውን ፎቶ ስንመለከት ያረካናል ። ራቁትነት የንጹህነት ፣ የፍጥረት መነሻነት ነው ብለን ልንወስደውም እንችላለን ። በትናንት ንጹህነትና በዛሬ ተጨባጭ ማንነታችን መሃል ያለውን አንድነትና ልዩነት ለማነጻጸርም ይረዳል ።
በጉርምስና እና በጉልምስና ወቅት ራቁታችንን የምንቀበለው ቃልኪዳን ልብስ ለብሰን ከምናደርገው ጋር በምን እንደሚለያይ ግልጽ አይደለም ። ተምሳሌትነቱም ስውር ወይም ድፍን ነው ። በራቁትነት ለመደናነቅ ከሆነ ባልና ሚስቱ በመኝታ ፣ በሻወር በወዘተ ግዜ የሚያገኙት ነው ። ይህን ለማድረግ ደግሞ አይተፋፈሩም ። ህግ የተላለፉት አዳምና ሄዋን የደረሰባቸውን የእፍረት መሸማቀቅ ይሄ ትውልድ ያካክሰዋል ነው የሚሉት - ፓስተሩ ? በጋብቻ ማግስት እየፈረሰ ያስቸገረውን ትዳር ለማጽናት ይሄኛውን ዘዴ እንሞክረው ነው የሚሉት - እረኛው ?
የኚህ ፓስተር ግኝት ሁለት መሰረታዊ ጉዳዮችን የሚዳስስ ነው ። የመጀመሪያው  ጉባኤተኛው ሁሉ ራቁቱን መማር ከቻለ ሁሉም የሰው ልጆች እኩል መሆናቸውን ያሳያል የሚል ነው ። ርግጥ ነው ሰዎች በሚለብሱት ፣ በሚያጌጡበትና በሚጠቀሙባቸው ዕለታዊ ቁሶች የኑሮ ደረጃቸው ሊገመት ይችላል ። ችግሩ ይኀው ጉዳይ የሰዎችን ውስጣዊ ማንነት ፣ ጥንካሬ ፣ ባህሪ ፣ አስተሳሰብ እና ፍልስፍና በፍጹም ሊያሳይ አለመቻሉን ፓስተሩ የተረዱ አለመምሰላቸው ነው ወይም ባላወቀ ተራምደው ማለፋቸውም ይሆናል ።
ሁለተኛው መነሻቸው ቤተክርስቲያን በምሳሌ ማስተማር ይኖርባታል ከሚል ሀሳብ ይመነጫል ። ክርስቶስ ሲወለድም ሲሰቀልም ራቁቱን ነበር ያሉት ፓስተሩ ፈጣሪ በዛ መልክ ካሳየን እኔ እንዴት ነው ስህተት የምሆነው በማለት ሲኤንኤንን ሞግተዋል ። በርግጥ እድሜ ለአዳምና ሄዋን እንጂ ዛሬ የሰው ዘር በሙሉ መላመላውን ነበር ታች ላይ የሚለው ። ሆኖም እንደ ፓስተር አለን በመምህርነቱ የሚታወቀው እየሱስ በገጠር ፣ በከተማ ፣ በመንደር ፣ በገበያ ስፍራና በመስበኪያ ቦታዎች ሁሉ እየተዘዋወረ ያስተማረው ራቁቱን ሆኖ አይደለም ።
ሌላው ችግር ራቁት ሆኖ ትምህርት መማርና ማስተማር ከባድ ፈተና ላይ በግድ የመውደቅ ያህል መቆጠሩ ነው ። አእምሮ ከምዕራፍና ቁጥሮች ይልቅ ቅርጽንና ከርቮችን ማጥናትና ማድነቅ ላይ ማተከሩ ሳይታለም የተፈታ ነው ። የአካል ንኪኪ ባይፈጠር እንኴ በሃሳብ መመኘትን ለማስቀረት ምን ዋስትና አለ ? እና ራቁትነት ከሌሎች ለመለየትና ጀብዱ ለመፍጠር ካልሆነ በስተቀር ዘለቄታዊ መፍትሄ ነው ብሎ መስበክ ወንዝ የሚያሻግር አይደለም ።
ናይጄሪያዊው ፓስተር ኬንዲ ቦሉዋጂ ያደረገው ምርምር ደግሞ ከፓንት ነጻ በሆነው የሴት ልጅ ብልት ላይ ነው ። ለምርምሩ የተጠቀመባቸው ቁሶች የተፈጨ ጨው ፣ መሃረብና ጸሎት / ድግምት / ናቸው ። የዚህ አይነቱ ፓሰተሮች የሚሰሩትን ውስብስብ ጥናት « pastorization » ብሎ መጥራት ሳይቻል አይቀርም ። ፓስቸራይዜሽን እና ፓስተራይዜሽን ይቀራረቡ እንጂ አይመሳሰሉም ። 
እንደሚታወቀው ፓስቸራይዜሽን ከፈረንሳዊው ቀማሚና ማይክሮ ባዮሎጂስት ሉዊስ ፓስተር ተግባር ጋር የተያያዘ ነው ። በክትባትና እርሾ ዙሪያ ትልቅ ስራ የፈጸመው ሉዊስ ወይን ፣ ቢራና ወትት እንዲቆመጥጥ በሚያደርገው ባክቴሪያ ላይም አንድ ግኝት አፍልቌል ። ባክቴሪያውን ለማጥፋት ፈሳሹን በጣም ማሞቅ ፣ ቀጥሎም በጣም ማቀዝቀዝ የሚለውን ሂደት ነበር ያበረከተው ። ይህም ሂደት « ፓስቸራይዜሽን » ለሚለው ሳይንሳዊ ቃል መወለድ ምክንያት ሆነ ።
ፓስተር ኬንዲም እንግዳ በሆነ መንፈስ የሚሰቃዩ ሴቶች በተለይም አግብተው መውለድ ካልቻሉ ያለግዜያቸው እንደሚሞቱ አወቀ ወይም ተገለጠለት ። መንፈሱ ደግሞ ባል እንዳይገኝ ደንቃራ ይሆናል ። በዚህ ስሌት ተጎድታለች ብሎ ላሰባት አንዲት የ22 ዓመት ወጣት ሴት ጉዳዩን ያጫውታትና መፍትሄውም በእጄ ነው ይላታል ። < ከፈጣሪ በታች እናንተን ነው የምናምነው በእርሶ መጀን > ትላለች ልጅት በልቧ ። ወዲያው ፓስተሩ
 < ያዝ እጇን
  ዝጋ ደጇን >
የተባለውን ኢትዮጽያዊ ዘፈን ተተርጉሞ የሰማው ይመስል ወጣቷን አስገብቶ ክፍሉን ይጠረቅምና  ለምርምሩ ይዘጋጃል ። በገቢር አንድ ልብስዋን አውልቃ እርቃኗን ቁጭ እንድትል ተደረገች ። በገቢር ሁለት ጸሎት ይሁን ድግምት ለደቂቃዎች ማንበልበል ቀጠለ  ። በክፍል ሶስት በነጭ መሃረብ ጨው ካወጣ በኃላ ብልቷ ውስጥ እንድታስገባው ይነግራታል ። ያልተለመደ ነገር ነውና ይተናነቃታል ፣ የሷ ፈራ ተባ ማለት ሂደቱን ሊያጔትተው ስለሚችልና ተግባሩን ለማፋጠን ይቻል ዘንድ ጣቱን ብልቷ ውስጥ ይጨምራል ። በዚህ የሚያበቃ ግን አልሆነም ። ከግራ ወደ ቀኝ ፣ ከቀኝ ወደ ግራ ማማሰል ይጀምራል ። ምናልባት ይኀው ተግባር እንደ ሊዊስ ፓስተር ባክቴሪያ ፣ ክፉ መንፈሱንም ይገድለው ይሆን ? አነጋጋሪ ጉዳይ ነው ። ግራም ነፈሰ ቀኝ  ይህ ሂደት « pastorization » ለሚለው መንፈሳዊ ቃል መወለድ ምክንያት ሆነ ብሎ መሳለቅ ይቻላል ። ዞሮ ዞሮ ፓስተር ኬንዲ ወደ ሌላ ምዕራፍ ከመሸጋገሩ በፊት በሩን ሲጠረቅም አይተው በተጠራጠሩ ሰዎች በቁጥጥር ስር መዋል ችሏል ።
አንዳንድ ፓስተሮችም ልክ እንደ እየሱስ ተዓምር መስራት እንችላለን በማለት አሳፋሪ ተግባር ከመስራት አይቆጠቡም ። በዚህ ረገድ ተጠቃሽ የሚሆነው ናይጄሪያዊው ፓስተር ፍራንክ ካቢሌ ነው ።
ራዕይ ስለታየኝ የተአምሩ ታዳሚ ሁኑ በማለት ደቀመዛምሩን ኮምቦ ሃይቅ ሰበሰበ ። ከዚያም ማቲዎስ ምዕራፍ 14ትን በመጠቃቀስ የሰው ልጅ በቂ እምነት ካለው እንደ እየሱስ በውሃ ላይ መራመድ እንደሚችል ማብራሪያ ሰጠ ። በተለምዶ ሃይቁን ለማቌረጥ የሃያ ደቂቃ የጀልባ ጉዞ ማድረግ አስፈላጊ ቢሆንም ፓስተሩ ርቀቱ አላሳሰበውም ።
መቼም በውሃ ላይ እንደባለሞተር ጀርባ እየነጠሩ መራመድ በእጅጉ አስደሳች ነገር መሆን አለበት ። ብዙዎቹ ቢሸበሩም አንዳንዶቹ መምህራቸው የውሃውን ጫፍ በጫማው ሶል እያነጠረ ብዙ ርቀት ሴሄድ ማለም ጀምረው ነበር ። ዞር እያለም እጁን ሲያውለበልብላቸው ለማጨብጨብ ፣ ለማፏጨትና እልልታቸውን ለማቅለጥ ተቁነጥነጥዋል ። ምናልባትም ጫፍ ደርሶ ከመጣ በኃላ ተሰብሳቢውን ለጉዞ ሲጋብዝ ፍርሃት በማየቱ « እናንተ እምነት የጎደላችሁ ስለምን ትጠራጠራላችሁ ? » እንደሚላቸውም ከማሰብ ወደ ኃላ አላሉም ።
እውነት ነው ፓሰተሩ ጉዞ ጀመረ ለማለት እንኴ ይከብዳል ። በሁለተኛው ርምጃ ሰውነቱ ሰመጠ - በፍጹም ወደ ደቀመዛምሩም አልተመለሰም ። ምዕመናኑ በድንጋጤ ተውጠው « RIP » ለማለት እንኴ አልታደሉም ነበር ። እኔ ግን አሁን ትዝ ያለኝ የእንግሊዛዊው ገጣሚ ዊሊያም ኮስሞ ሞንክሃውስ ግጥም ነበር ። ርዕሱ There was a young lady of niger ይሰኛል ። በአምስት ስንኞች ጣጣውን የጨረሰውን ግጥም እነሆ ብያለሁ
There was a young lady of niger
Who smiled as she rode on a tiger
They returned from the ride
With the lady inside ,
And the smile on the face of the tiger .
እውነት እረኞቹ ምን እየፈጸሙ ነው ? ወዴትስ እየተሄደ ነው ? ዮሀንስ ወንጌል 10 ፡ 11 ላይ እየሱስ መልካም እረኛ እኔ ነኝ ፣ መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል ይላል ። ይህ ምሳሌ በሌሎቹም ላይ እንዲጋባ ነበር የተፈለገው ። ግን የምናያቸውና የምንሰማቸው ነገሮች ተስፋ ከመስጠት ይልቅ የሚያስፈሩ እየሆኑ ነው ። ብዙ እረኞች ተኩላና ቀበሮ ለመሆን እየቸኮሉ ይመስላል ።

« መንጋውን ለሚተው ለምናምንቴ እረኛ ወዮለት  ! » የሚለው ቃል የትኛው ትንቢት ላይ ነበር የሚገኘው ?

Friday, February 28, 2014

የባለገሩ ስነቃልና የ « አቶ አለምነው ቤት »


ንደማንኛውም መጽሀፍ በትኩረት ላንብበው ብዬ አይደለም የገለጽኩት ። < እስኪ ትንሽ በአነጋገራችን ልዝናና > በማለት እንጂ ። ድንገት ከመሃሉ ገለጥ ሳደርገው < ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል > ከሚለው ንባብ ጋር ግጥምጥም አልኩ ። < ጎሽ ይዞልሃል > አልኩት በፈገግታ - የምሳሌያዊ አነጋገር መጽሀፉን ።
እናም ከ ሀ እስከ ታች የተዘረዘሩትን አነጋገሮች እንደ ፎቶ አልበም እያገላበጥኩ መጫወት ቀጠልኩ ። የገረሙኝን መቼ ይሆን የተነሱት ይቅርታ መቼ ይሆን የተነገሩት ፣ በየትኛው አካባቢ በማለት caption ብጤ እፈላልግ ነበር ። አንዳንዶቹ ሳይታዘዙ የሰው ብብትን ኮርኩረው በግድ ሳቅ መፍጠር የሚችሉ ናቸው ። ለምሳሌ ያህል ፣
< ለሰበበኛ ቂጥ መረቅ አታብዛበት ! >
< ቢያንጋልሏት ጡት የላት ፣ ቢደፏት ቂጥ የላት ! >
< ምንም ብትሞቺ ፣ እንዴት አደርሽ አንቺ ?! >
< እግዜር ሲቆጣ በዝናብ አር ያመጣ >
< ተደብቃ ትጸንሳለች ፣ ሰው ሰብስባ ትወልዳለች ! >
< አባቴ ትንሽ ነው ፣ ብልቴ ትልቅ ነው የሚል የለም ! >
< ልጅ አባቱን ገደለ ቢለው እረ የኔ ልጅ እንዳይሰማ አለው >
የሚሉት ጋ ስደርስ ከትከት ብያለሁ ።
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ አንዳንዶቹ አባባሎች ጥያቄ የሚያስነሱ ... እንደ መጽሀፍ ቅዱስ ቃል አስረጅ የሚፈልጉ ወይም ደግሞ ሃይለኛ ማስተካከያ የሚፈልጉ ሆነው ነው ያገኘኃቸው ።
ለአብነት ያህል < ነገሩ ነው እንጂ ጩቤ ሰው አይጎዳም ! > የሚለው አባባል ድሮ ጩቤ ከጎማ ወይም ከቆዳ የሚሰራ መሆኑን ነው የሚያመለክተው ። ካልሆነ ታዲያ በአሁኑ ግዜ እንቅፋት ፣ የበዛ ሀሳብ ፣ ድንጋጤና ትንታ እንኴን ሰው ለመግደል ፍቃድ አውጥተው እንዴት ሆኖ የሾለ ብረት ሰው ለመግደል የሚያንሰው ?
< ማን ይሙት ጠላት ፣ ማን ይኑር አባት ! >
የሚለው ስነቃል የተደረሰው የእንጀራ እናት ባሳደገችው ባላገር እንደሆነ ግምት አለኝ ። አሊያማ ከአባት በላቀ መልኩ እናቱንና ሀገሩን « እምዬ » የሚለው ኢትዮጽያዊ ተቆጥረው የማያልቁ የእናት ክብር መግለጫ ግጥሞችን እንደ ዝናር ታጥቆ አይደለም እንዴ የሚዞረው ? ድንገትም
< እናቱን ለናቀ ክብሯን ላዋረደው >
መሬት ትዙርበት ጸሃይ አትሙቀው » ብሎ ሊቆጣ እንደሚችል ሁሉ መች አጣችሁት ?
< ለሰው ሞት አነሰው ! >
የሚለው አባባልስ በምንድነው የተሰራው ? በዝሆን ሀሞት መሆን አለበት ። በዚህ ሀሞት እንጀራ ፈርፍረው በግድ ያጎረሱት አንድ ሰው ክፋትንና ጭካኔን ለመግለጽ  አክ - እንትፍ ያለው ሀረግ ይመስላል ። መቼም ሞት አነሰው የሚለን እድሜ ልክ በእስር ይበስብስ ለማለት አይደለም ። ምናልባት የሚረካው ከጀግናውና ሀገር ወዳዱ አጼ ቴዎድሮስ አንድ የጭካኔ ሰበዝ መዞ ሲተገብረው ሊሆን ይችላል ። አጼ ቴዎድሮስ በደግነትና ጭካኔ ተደባልቀው የተሰሩ ንጉስ ነበሩ ። ቁጣ የንዴታቸውን ጣሪያ በሚያግለው ግዜ የሚያቀዘቅዙት የሰው እጅና እግርን አስቆርጠው ነበር - ከዛ ቁራጭህን ይዘህ ሀገር ግባ ነው ። እግር እንደ ዛፍ የሚመለመልበት ዘመን ። ለነገሩ ይህ ዘመን አልፏል ። ዛሬም ግን ሰዎች በድንጋይ ተወግረው ይሞታሉ ፣ አንገታቸው በሻሞላ ይቀላል ፣ ሰውነታቸው ተቀብሮም ከብቶች በላያቸው ላይ ይነዳል ። እዛ ያሉት አጼ ልክም ነው ህግም ነው ይሉሃል - እኛ የምንለው ያዝልን መጀን ! ነው ።
 < ሙቅ ውሃና የሰው ገንዘብ አይጠቅምም  ! >
በመርህ ደረጃ ልክ ነው ። ዳሩ ግን ጂ+1 ውስጥ እየኖሩ ጂ+6 የሚያስገነቡት ፣ ሚሊየን በሚደፍር መኪና የሚንፈላሰሱት ፣ ለልደታቸው ወይ ዱባይ አሊያም አካፑልኮ ደርሰው የሚመጡት ፣ ይህ ካልተመቸ ከፓሪስ ኬክ የሚያሰጋግሩት ልማታዊ ሀብታሞች በኑሮ ሰረገላ ከአያት ተራራ እስከ እስከ ካራማራ የሚንፈላሰሱት ስፍር ቁጥር የሌለውን የሰው ገንዘብ በጥቂት ማግኔታዊ ላባቸው በመሰብሰብ አይደለም እንዴ ? መሰለኝ እንግዲህ !
< ልጅ ቢያስብ ምሳውን ፣ አዝማሪ ቢያስብ ጠላውን ! >
ይህች አባባል ገና ድሮ ጡረታ መውጣት ሲገባት ለሰዎች በተጨመረው የስራ ዘመን ፍዳዋን ትቆጥራለች ። ለማንኛውም የዛሬ ልጅ ከአባቱ የተረፈውን ሳይሆን ከአባቱ ጸሎት በፊት አስቀድሞ የሚጎርስ ፣ እንግዳ አክብሮ ጔዳ የሚሸሸግ ሳይሆን ልክ እንደ ርዕሰ ብሄር እንግዳውን በራሱ ክፍል ውስጥ ተቀብሎ የሚያነጋግር ፣ አንዲት ምሳውን ሳይሆን ለትምህርት ቤት ከሰኞ እስከ አርብ በሁለት ሳህን ስለሚያስቌጥራቸው የምግብ አይነቶች ከፈለገ ከአረብ ቻናል ፣ እንዳማራጭም ኢቢኤስን ቁጭ ብሎ በመቃኘት  መርሃ ግብር የሚነድፍ ነው ። ስለፍቅር ፣ ስለኑሮ ውድነት ፣ ነገር ስላሰከራቸው ጎረቤቶች ፣ ስለተሸራረፉ መብቶች ፣ ስለቀበሌም ሆነ ገዢው ፓርቲ አያውቅም ብለው ፊቱ ካወራችሁ ተሳስታችኃል - ምክንያቱም በሌላ ቀን እርስዎን እንደ ዋቢ ምንጭ በመጥቀስ ለጔደኛው ወይም ለጥቁሩ እንግዳ ገለጻ ሲያደርግ ሊሰሙ ይችላሉና ።
ስለሴትነት ብዙ ተብሏል ። ጥቂቱን ብቻ እንምዘዝ ።
< ሴትና አህያ በዱላ ! >
የወረደ ነው ወይስ የተጋነነ ንጽጽር የሚባለው ?
 < ሴት የወደደ ገሃነም እሳት ወረደ ! >
የመላከ ጊዮርጊስ ?! እናቴን ? እህቴን ? ልጄን ? ሚስቴን ? ያለው ማን ነበር ?
< ሴት ካልወለደች ቌንጣ አትጠብስም ! >
በጉዴ መጣ አሉ እትዬ ዘነቡ - ባለስልጣኗን አይደለም
< ሴት በማጀት ወንድ በችሎት ! >
ወቸው ጉድ ?! ይህን የማህበራዊና ባህላዊ ልምድ ጣጣ ነው ብሎ ማለፍ እንዴት ይቻላል ? ጠንካራ ፖለቲካም ጭምር እንጂ ። ቆይ ግን የወ/ሮ ዘነቡ መ/ቤት በተለይም ሴቶችን በተመለከተው ርዕሰ ጉዳይ ምን እያሰበ ነው ? ለነገሩ እሳቸው ሰሞኑን የግበረ ሶዶማዊያን አጀንዳ ላይ ናቸው ። ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ ጻጻስ ፍራንሲስ ስለ ጌይ ምን ይላሉ ሲባሉ « እኔ ማነኝ እና ነው ይህን የምዳኘው ? » የተመድ ዋና ጸሃፊ ባንኪሙን በበኩላቸው « ግብረ ሶዶማዊያን እንደ ሁለተኛ ዜጋ ብቻ ሳይሆን እንደ ወንጀለኛም እየተቆጠሩ ነው » በማለት ኡኡ ብለው ያውቃሉ  ። ፕሬዝዳንት ሮበርቱ ሙጋቤ በአንድ ወቅት “ ግብረሰዶማዊያን ከአሳማና ከውሾች የከፉ ናቸው » ማለታቸው አይዘነጋም  ። ሚኒስትር ዘነቡ ማን ከማን ያንሳል ብለው ምን ነበር አሉ የተባሉት ? መቼም ይሄ ሁሉ የስነቃል የቤት ስራ እያለባቸው እዛ ውስጥ ከገቡ የጉድ ነው ።
< በሽተኛ ያድርቅህ መጋኛ  ! >
አሁን ነው መሸሽ ። በደጉ ዘመን በነገር ወይም በቦክስ ገጭቶት አሁን ብድሩን የሚመልስ ሰው ይሆን ? ነው ህመምተኛው ሲያቃስት ከእንቅልፉ እየተቀሰቀሰ በቃሬዛ ጤና ኬላ ማመላለስ የሰለቸው አባወራ ? ለነገሩ የአቶ ቦጋለ መብራቱ እና የወ/ሮ ውድነሽ በጣሙ ዘመድም ሊሆን ይችላል ። አቶ ቦጋለ ወጥሮ የያዛቸው የተስቦ በሽታ ለሌላውም እንዳይተርፍ ለመጋኛ ስለት የሚያቀርብ ምስኪን ገበሬ ። ወይ አጨካከን ?! በሽተኛን ፈጣሪ ይዳብስህ በማለት ያጽናኑታል እንጂ እንዴት ይለጥፉበታል ። ግድየለም እንዲህ የሚናገሩት የሰው ልጆች ሳይሆኑ የሰው ገዢዎች መሆን አለባቸው ።
እነዚህን የመሳሰሉ አነጋጋሪ ፣ ተሻሻይ ወይም ተሰራዥ አባባሎች ጥቂት አለመሆናቸውን መገንዘብ ይቻላል ። ለዚህ ለዚህ የቀድሞው ባህል ሚኒስቴር ከተፎ ስራ ይሰራ ነበር ። የአሁኖቹ እንኴ በፍላጎትና በሞያ ሳይሆን በሹመትና ሽረት ብሎም በአንሚ ደረጃ የተወከሉ ናቸው ስለሚባል  ደረትን ለመንፋት የሚያስችል መሰረት መኖሩ ያጠራጥራል ። ለማንኛውም ግልባጩ ይድረሳቸው ።
ትልቁ እውነት ግን አብዛኛው አባባል ወይም ስነቃል ዘመን ተሻጋሪ መሆኑ ነው ። በነዚህ በርካታ ስነቃል ውስጥ ያልተዳሰሰ ማህበራዊ ፣ ፖለቲካዊ ፣ ኢኮኖሚያዊ ፣ ሃይማኖታዊ ፣ ባህላዊ ጉዳዮች አለ ለማለት ያስቸግራል ። ከማጣት እስከ ማግኘት ፣ ከስንፍና እስከ እውቀት ፣ ከጅልነት እስከ ብልሃት ፣ ከፍቅር እስከ ጥላቻ ፣ ከጉንዳን እስከ ዝሆን ፣ ከሸፍጥ እስከ ታማኝነት ፣ ከክብር እስከ ውርደት ፣ ከረሃብ እስከ ጥጋብ ፣ ከልጅ እስከ አባት ፣ ከልደት እስከ ሞት ፣ ከዲያቢሎስ እስከ ክርስቶስ ፣ ከሴት እስከ አማት ፣ ከሹመት እስከ ሽረት ፣ ከፍርሃት እስከ ጀግንነት ፣ ከነጻነት እስከ አምባገነንነት .... ምናለፋችሁ ጥላሁን ገሰሰ ያልዘፈነበት ባላገሩ ያልተቃኘበት ፍልስፍና የለም ብሎ እውቅና መስጠት እንደማጋነን የሚያስቆጥር አይመስለኝም ። እያንዳንዱን ርዕሰ ጉዳይ የሚመለከቱትን ስንኞች እዚህ ገጽ ላይ ፈሰስ ባደርጋቸው እደሰት ነበር ። ብዛታቸው ግን አስፈራኝ ። ማንን መርጦስ ማንን መተው ይቻላል ።
እውነት ይህን ሁሉ የደረሰው ብዙዎቻችን ቀለም አልዘለቀውም የምንለው ባላገር ከሆነ የ < ቀለም >ጉዳይ ማጠያየቁ አይቀርም ። እውነት ይህን ሁሉ ነባራዊ እውነት በቃላት ሸብልሎ ያጎረሰን ባላገር ከሆነ < ባገረስኩ ተነከስኩ > ቢል አይፈረድበትም ።
ማነው ነካሽ ?
አሁን በቅርቡ የሚያስተዳድሩትን ባላገር ያበሻቀጡትና ያዋረዱት የአማራው ክልል ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አለምነው እውነት ባላገሩን ያውቁታል ?  ካወቁትስ እንዴት ነው የመዘኑት ? ለማለት ስለምንገደድ ነው ። ለምሳሌ ያህል ሹሙ የእውቀትና የልምድ ሀብት የሚለካው ጫማ በማድረግና ባለማድረግ ነው ብለው የተነሱ አስመስሎባቸዋል ። ከዛው ክልል የተገኙት አጼ ቴዎድሮስ ሀብት ሳያንሳቸው ጫማና ኮፍያ ማድረግ አይወዱም ነበር ። ጀግንነትና የሀገር ፍቅር ከባዶ እግር ጋር አይያያዝም ። አበበ ቢቂላ በሮም የኦሎምፒክ ውድድር ያሸነፈው 11 ቁጥር ማሊያና ቁምጣ አድርጎ እንጂ ጫማ ተጫምቶ አልነበረም ። ማራቶን ከጽናትና ጥበብ ጋር እንጂ ከባዶ እግር ጋር ግንኙነት እንደሌለው ሌላ ማሳያ ሊሆን ይችላል ። ርግጥ መንገዱ በማይመችበት ቦታ ተጽዕኖ ሊፈጥር እንደሚችልም ግምት ውስጥ በማስገባት ።
እናም  < ባላገሩ ባዶ እግሩን እየሄደ የሚናገረው ግን መርዝ ነው  > ማለት አንድም ጭንቅላታቸው ውስጥ የሚውለበለብ የንቀት ባንዲራ መኖሩን በሌላ በኩል ደግሞ ያላዋቂነት መነሻ ይሆናል ። ይኀው መነሻ መድረሻ ይኖረው ዘንድ ደግሞ  < ትምህክተኛ ነው ፣ ለሃጫም ነው > እያሉ ልጥፉን ማወፈር በርግጥም ባዶ እግርን ሳይሆን የጎደለ ወይም በዘይት እጦት የሚንጣጣ ጭንቅላትን ወገግ አድርጎ የሚያሳይ ነው ።
በሀገራችን ታሪክ ትላልቅ ስራ የሰሩ በርካታ የሀገራችን ጀግኖች እንደተግባራቸው ስማቸው በክብር እንዲታወስ ተደርጔል ማለት አይቻልም ። ይሁን እንጂ የታደሉት ደግሞ ስንት የጀግንነት ተግባር ፈጽመው በስማቸው እውቅና አግኝተዋል ። ለምሳሌ ያህል አትሌት ኃይሌ  « ሃይሌ ገብረስላሴ ጎዳና »ን በስሙ ማግኘቱ ያንስበታል ።  አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ሆስፒታል አይደለም  ሰሞኑን ለደነገጠው አየር መንገድ ማስታወቂያ ብትሆን መሳ ለመሳ ናት ። ያም ማርሽ ይቀይራል - እሷም ዙሩ ሲሳሳ አዲስ አቦሸማኔ  ትሆናለች ። ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን የራሱን የአገጣጠም ስልት በመፍጠሩ « የጸጋዬ ቤት » የተባለ ስያሜ ተበርክቶለታል ። በዚሁ መሰረት በባዶ ጭንቅላት የሚመረቱ መረን የወጡ ስድቦችን « የአቶ አለምነው ቤት » ብሎ መጥራት  ተገቢ ይሆናል ።
ስራ ለሰሪው እሾህ ላጣሪው እንዲል ባላገሩ ።