Sunday, September 23, 2012

‎‹‹ የስልጣን ዘመን ገደብ ›› - ህግና ህዝብ አክባሪ መሪ ይፈልጋል‎



መሪነት የቀደመ መስዋዕትነትን ይጠይቃል

ከቅኝ አገዛዝ ነጻ ወጥታ ራሷን በራሷ የምታስተዳድረው አፍሪካ ተስፋና ህልሟን ለማሳካት በ1990 ዋቹ አካባቢ ይበል የሚያሰኝ ፓለቲካዊ ርምጃዋችን መውሰድ ጀምራ ነበር ፡፡ ይህ ርምጃ ‹ አፍሪካ ያለ እኛ ድጋፍ ማየትም ሆነ መራመድ አትችልም › ይሉ ለነበሩት ምዕራባዊያን የጠነከረ ምላሽ ተደርጎም ሊወሰድ ይችላል ፡፡

ህገ መንግስታቸው ውስጥ በደማቅ ቀለም እንዲጻፍ ያደረጉት ‹‹ የስልጣን ዘመን ገደብ ›› የተረጋጋች አህጉር ብቻ ሳይሆን በአጭር ርቀት እከኳን አራግፋ የልማትና የዴሞክራሲ ተቋዳሽ ልትሆን እንደምትችልም ምልክት የፈነጠቀ ዘመናዊ አሰራር ነበር፡፡ 33 የሚደርሱ የአፍሪካ ሀገሮች የህዝብ እንጂ የጥቂት ብልጣ ብልጥ ሰዋች ርስት አይደለም በማለት ገደቡን ከሁለት ግዜ በላይ እንዳይበልጥ አድርገዋል ፡፡ ሶስት ዙር ከምትፈቅደው ሲሸልስ በስተቀር ፡፡ በርግጥ ብዙዋቹ በገደቡ ወሰን ቢመሳሰሉም አንዱ የስልጣን ዘመን ምን ያህል ዓመት ይይዛል በሚለው ልዩነት ነበራቸው ፡፡ አንዳንድ ሀገሮች ትንሹን አራት ሲያስቀምጡ አንዳንዶች ደግሞ ትልቁን ሰባት ዓመት ህገ መንግስታቸው ላይ አስፍረዋል ፡፡

ብዙዋች አንዱን የስራ ዘመን አምስት ዓመት በማድረግ ለሁለት ግዜ ያህል የፈቀዱ ናቸው ፡፡ ቤኒን፣ ቦትስዋና፣ ቡሩንዲ፣ ኬፕቨርድ፣ ሴንትራል አፍሪካ ሪፐፕሊክ፣ ዴሞክራቶክ ኮንጎ፣ ኬንያ፣ ማዳጋስካር፣ ማላዊ፣ ማሊ፣ ሞሪታንያ፣ ሞሪሺየስ፣ ሞዛምቢክ፣ ናምቢያ፣ ኒጀር፣ ሳኦቶሚፕሪንስፔ፣ሴራሊዮንና ዛምቢያ እዚህ ምድብ ውስጥ ይካተታሉ ፡፡

ጋናና ናይጄሪያ አራት ኣመት ፤ የኮንጎ ሪፐፕሊክና ሩዋንዳ ሰባት ዓመት ፤  ኮሞሮስ ፣ ኤርትራና የመሳሰሉት ደግሞ ገደብ ካልጣሉ ሀገሮች ውስጥ ይመደባሉ ፡፡ ግራ የሚያጋባ ምድብ ውስጥ ለረጅም ግዜ ቆይተው ከነበሩ ሀገሮች ውስጥ ኢትዮጽያ ‹‹ የቡድን አባት ›› ሆና ቆይታለች ማለት ይቻላል ፡፡ ልክ እንደኛ በኢትዮጽያ የአሜሪካ አምባሳደር የነበሩት ዴቪድ ሺንም ግራ ተጋብተው እንደነበር በብሎጋቸው ላይ የሰፈረው የሚከተለው ጽሁፍ ያስረዳል ‹‹ የኢትዮጽያ ህገ መንግስት ትልቁን የፓለቲካ ስልጣን ለያዘው ጠ/ሚ/ር ገደብ ማስቀመጥ ቢኖርበትም ያደረገው ለፕሬዝዳንቱ ነው ›› አንዳንዶች ጉዳዩን የሃያው ዓመት ምርጥ ፓለቲካዊ ስላቅ በማለት ሲጠሩት ተሰምቷል ፡፡

እናም ሀገራችን ለረጅም ዓመታት የግራ እግር ጫማ በቀኝ ተጫምታ ስትወላከፍ ቆይታለች ፡፡ ሰሞኑን ታዲያ የቀኝ እግር ጫማ- ለቀኝ እግር ብቻ መዋል አለበት የሚል የሚመስል መግለጫ ይፋ ተደርጓል ፡፡ በኢትዮጽያም የመንግስት ኃላፊዋች የስልጣን ዘመን በአስር ዓመት ተገድቧልና  ፡፡ እልልታ ያስፈልገው ነበር - ግና ከአፍሪካ በሃያ አመታት ወደ ኃላ ቀርቶ ዛሬ የተነገረው ዜና በህዝቡ አንደበት ቀድሞ በመነገሩ  ‹‹ ሰበር ›› ለመባል አልቻለም ፡፡ ምናልባት ለሰበር ጥቂት ቀረብ የሚለው ‹‹ ከ65 ዓመት በላይ የሆነው ሰው በስልጣን ላይ መቀጠል አይችልም ›› የሚለው ገደብ ነው ፡፡ በዚህ ያልወጣ ህግ መሰረት የ66 ዓመት አዛውንት ስለጃጃ ሀገር ለመምራት ብቃት የለውም ማለት በራሱ የጃጀ ሀሳብ ሊያስብል የሚችል ይመስለኛል ፡፡ በሌላ አነጋገር በ80 ዓመታቸው ምርጥ ስራ የሰሩትን የዓለማችንን መሪዋች ታሪክ አለማወቅን ያቃጥራል ፡፡ በመሰረቱ የብዙዋች / አንደኛው / ጥያቄ አንድ መሪ ረጅም ግዜ አይቆይ እንጂ በ66 ዓመቱ አይስራ የሚል አይደለም ፡፡ ለመሆኑ ይህ እድሜ ብቁ አለመሆኑ በምንድነው የተረጋገጠው ? ጥሩ ስም ባላቸው ሰው የሚመራው የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በዚህ ጉዳይ ላይ አዲስ ግኝት ካለ ሊግረን ይገባል ፡፡ ነው የሀገሪቱን Life expectancy በመሾፍ ብቻ ነው ከአራት ነጥብ የተደረሰው ፡፡  አሁን ደግሞ የቀኝ እግር ጫማ በግራ እግር እንዲደረግ ማዘዣ የተጻፈ አስመስሎታል ፡፡

አሁን የወጣው ‹‹ የስልጣን ዘመን ገደብ ›› ተነገረ እንጂ ገና በተግባር ያልተፈተሸ በመሆኑ  ‹‹ ጥሩ ነው ›› የሚል የሞራል ታርጋ ለመለጠፍ የሚያስችል መነሻ የለም ፡፡ ይህን ለማለት የሚያስችለው  ደግሞ አፍሪካ ባለፉት ሃያ አመታት የመጣችበት መንገድ አስተማማኝ አለመሆኑ ነው ፡፡ ብዙዋቹ የአፍሪካ መሪዋች ለወሬ እንጂ ለተግባር ቅርብ አይደሉም ፡፡ ለቁጥር የሚታክት ሚሊዮን ዶላር ወደ ውጭ አግዘው እንኳ ሙስናው ውስጥ ከመልከስከስ አይታቀቡም ፡፡ ሃያና ሰላሳ ዓመታት በፈላጭ ቆራጭነት መንገድ ወንበር ይዘው በመጨረሻ እንኳ የተሻለ ስርዓት ለመፍጠር ፍቃደኛ አይሆኑም ፡፡ ፕሬዝዳንት ሙጋቤ ለአንድ ጋዜጠኛ ‹‹ በህይወት እስካለሁ ድረስ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ነኝ ›› ማለታቸውን እናስታውሳለን ፡፡ የጋዳፊና የሙባረክ ዓይነቱ ደግሞ እስከመጨረሻው ሰዓት ‹ ህዝባችን ይወደናል፣ ህዝባችን ለኛ ይሞታል ! › ይሉ ነበር ፡፡

የኡጋንዳው ፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ ወደ ስልጣን የመጡት በ1986 ነበር ፡፡ እስከ 2004 ድረስ ሀገሪቷን መሯት ወይም መጠመጧት ፡፡ በዚህ ግዜ ትዝ ሲላቸው ለካ የስልጣን ዘመን ገደብ አስቀምጠዋል ፡፡ በ2005 ለሀገሪቱና ለህዝቡ ጥቅም በሚል ህገ መንግስቱን ፐውዘው የገደቡን ግዜ አሻሻሉት ፡፡ በ2006 በተደረገው ሶስተኛ ምርጫ ደረታቸውን ነፍተው አሸነፉ ፡፡ አሁንም አሉ ፡፡ የገደቡም ቁጥር ከፍ እንዳለ ነው ፡፡

ይህን ምርጥ የዴሞክራሲ ጎዳና የናሚቢያው ፕሬዝዳንት ሳምኒዮማ በ1999 በይፋ ከጣሱት በኃላ ስንት ፈሪ - ጅግኖች ተከተሏቸው ? የሴኔጋሉ ዲዩፍ፣ የጊኒው ላንሳና ኮንቴ፣ የቶጎው ጋንሴቤ ኢያዴማ፣ የጋቦኑ ኦማር ቦንጎ፣ የቡርኪናፋሶው ካምፓወሬ፣ የቻዱ ኢድሪስ ዳቤ፣ የቱንዝያው ቤን አሊ፣ የካሜሮኑ ቢያ፣ የአልጄሪያው ቡተፍሊካ … ማን ቀረ ታዲያ ?  እያንዳንዱ መሪ ራሱ ያወጣውን ህግ ለመሻር ያደረገውን ብልጠትም ሆነ የጭካኔ መንገድ ስናነብ ወይም ስንሰማ የሚያሳፍር ሆኖ ነው የሚገኘው ፡፡

በርግጥ የወጣውን ህግ ጠንክረው በመጠበቃቸው መፈንቅለ ህግ ሊያደርጉ የሞከሩ መሪዋቻቸውን አሳፍረው የመለሱ ህዝቦችም አሉ ፡፡ በዋናነት የዛምቢያ፣ ማላዊና ናይጄሪያ መሪዋች ህገ መንግስቱን የመቀየር ሙከራ ሲከሽፍባቸው የእነሱን እኩይ ተግባር የሚፈጽሙ አሻንጉሊት መሪዋችን ለመተካት ጥረት አድርገዋል ፡፡

የዛምቢያው ፍሬዲሪክ ቹሉባ ለሶስተኛ ዘመን ምርጫ ሲሯሯጡ የሀገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዋች፣ የሲቪክ ማህበረሰብ፣ የሰራተኛ ማህበራት፣ የተማሪዋች ህብረት፣ የሴት አደረጃጀቶች፣ ቤተክርስትያናት፣ የህግ ባለሙያዋች እንዲሁም ህዝቡ አረንጓዴ መቀነት በመልበስ፣ የመኪና ጡሩንባ በማሰጮህና በመዘመር አስደንጋጭ የተቃውሞ ሰልፍ አካሂደዋል ፡፡ ተቃውሞው ያሰቡትን እንዳይፈጽሙ ያደረጋቸው ቹሉባ ሌላ ዘዴ ቀየሱ ፡፡ በቀላሉ እቆጣጠረዋለሁ፣ የእኔንም ሃሳብ እንዲፈጽም አደርገዋለሁ ብለው ያሰቡትን  ሌቪ ምዋናዋሳን ለፕ/ት ምርጫ ዕጩ አድርገው መረጡ ፡፡ ምዋናዋሳም ምርጫውን አሸነፉ ፡፡ ነገር ግን ከድሉ በኃላ አዲሱ መሪ የቀድሞውን ጓደኛቸውን ሀሳብና ተጽዕኖ አሽቀንጥሮ በመጣል በራሳቸው መንገድ ተጓዙ ፡፡ የቹሉባን ያለመከሰስ መብት በመግፈፍ በሙስና እንዲጠየቅ አስደረጉ፡፡

የማሊውም  ታሪክ ከዛምቢያው የሚርቅ አይደለም ፡፡ ፕሬዝዳንት ባኪሊ ሙሉዚም ከህዝቡ የደረሰባቸውን ተቃውሞ መቋቋም ባለመቻላቸው አንድ አሻንጉሊት ወራሽ ፈለጉ ፡፡ ቀልባቸውም ቢንጉዋ ሙታሪካ ላይ አረፈ ፡፡ ብዙዋች እኚህ ሰው ታማኝ ጩሎ እንደሚሆኑ እምነት አሳድረው ነበር ፡፡ በርግጥም ከምርጫው ድል በኃላ / ያው በአፍሪካ ፕሬዝዳንቱ የወከለው ሰው በተዓምር አይሸነፍም / ሙሉዚ እና ሙታሪካ በተመሳሳይ መንገድ የሚጓዙ መሰሉ ፡፡ ከጥቂት ቆይታ በኃላ ሙሉዚ ሙታሪካ የቀረጹትን የጸረ ሙስና ፓሊሲ መቃወም ጀመሩ ፡፡ ያኔ ጨዋታው ፈረሰ… ዳቦው ተቆረሰ…

የናይጄሪያው ፕሬዝዳንት አባሳንጆ ህገ መንግስቱን ለመቀየር ያደረጉት ጥረት ከህዝብና ተቃዋሚዋች ብቻ ሳይሆን ከራሳቸውም ፓርቲ ተቃውሞ አጋጥሟቸዋል ፡፡ በመሆኑም የራሴ ሰው ነው የሚሉትን ኡማሩ ሙሳ ያርአዱም ለፕሬዝዳንትነት ዕጩ አድርገው አቀረቡ ፡፡ ሚያዚያ 2007 በተደረገው ምርጫ በአጨቃጫቂ ሁኔታ አሸነፉ ፡፡ እኚህ ሰው ግን ከህዳር 2009 ጀምሮ በጠና ታመው ወደ ሳኡዲ አረቢያ ለህክምና በማቅናታቸው የስልጣን ክፍተት በሀገሪቱ ሊፈጠር ችሏል ፡፡ የካቲት 2010 ሴኔቱ የፕሬዝዳንቱን ስልጣን ለምክትላቸው ጉድላክ ጆናታን አስተላለፈ፡፡ ፕሬዝዳንቱ መጋቢት 5 ቀን 2010 በመሞታቸው የስልጣናቸውን ግዜ እንኳን መጨረስ አልቻሉም ፡፡

ርግጥ ነው አፍሪካ ጥቂት ሞዴል መሪዋችም አሏት ፡፡ ኔልሰን ማንዴላ ከአንድ የስልጣን ዘመን ቆይታ በኃላ ብቻ ነበር ወንበራቸውን ያስረከቡት ፡፡ የቤኒኑ ማቲሁ ኬሬኩ ፣ የኬፕቨርድ ማስካሪንሃስ ሞንቲሮ ፣ የማሊው አልፋ ኮናሬ ፣ የሞዛምቢኩ ጃኪም ቺሳኖ ፣ የሳኦቶሚፕሪንስፒ ማገል ትሮቫዳ ፣ የታንዛኒያው ቤንጃሚን ማካፓ፣ የቦትስዋናው ፌስተስ ጎንተባይ ሞይ የሁለት ግዜ የስልጣን ዘመናቸውን እንደጨረሱ በህገመንግስቱ ላይ ግፍ ወይም ዘረፋ ሳያካሂዱ ቦታቸውን ለተተኪው አስረክበዋል ፡፡ አፍሪካ እኒህን መሰል ህግና ህዝብ አክባሪ መሪዋች በብዛት ያስፈልጋታል ፡፡ እነዚህ ጥቂት ምርጥ ዘሮች ግን የአረምና የእንክርዳድን ሚና የሚጫወቱት በርካታ መሪዋች እያጠወለጓቸው በመሆኑ የስጋቱ በረዶ ዛሬም ህሊናችን ወስጥ እንደተጋገረ ይገኛል ፡፡

ስልጣን መገደብ የዴሞክራሲ ስርዓትን ለማጠናከር ፣ ውድድርን ለማላቅ ፣ አዲስ አስተሳሰብን ለማመንጨት ፣ የገነገነ ቢሮክራሲንና  ሙስናን ለመሞረድ ከፍተኛ ጥቅም አለው ፡፡ ሀገራችን ዛሬ ወደዚህ ስርዓት እቀላቀላለሁ ብትልም አባባሉ ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታነት ይሁን ለእውነት የተተኮሰ መሆኑ አይታወቅም  ፡፡ ትክክለኛ ቢሆን ይመረጣል ፡፡  አጠራጣሪ የሚያደርገው  ደግሞ ከላይ ለማሳየት የተሞከረው የአፍሪካ መሪዋች ልምድ ነው ፡፡ ኢትዮጽያም ከዚህ የተሻለ የልምድ ሪከርድ አላስመዘገበችም ፡፡  ግራም ነፈሰ ቀኝ መሪዋቻችን በቺሳኖና በማንዴላ ወይስ በሙሴቬኒና በፓውል ቢያ መንገድ ይጓዛሉ  የሚለውን ጥያቄ  በአግባቡ ለመፍታት ገና ረጅም ርቀት ይቀረናል ፡፡

Saturday, September 15, 2012

ነገን ማየት



ይህ ስዕልና ግጥሙ ምንና ምን ናቸው ? የስዕሉስ ውክልና ምን ይሆን ? ቀዛፊው አሞራ … ዳመና ያነቃት ጸሃይ …ወርቅ የመሰለው ሰማይ …በዳመናው የተሰሩ ጅምር የስዕል ንድፎች … ጥግና ጨለማ ውስጥ መልህቋን የጣለችው መርከብ … በሰማዩ ቅላትና በባህሩ ጥቁረት መካከል ያለው ልዩነት …


ሰላም ፍቅር ሽቶ - ያሰቡት ሲጠፋ
ህብረት ተስፋ ቋጥሮ - የእኩይ ሽል ሲፋፋ
ፍርሃት ያለ ድንበር - ፍጥረታት ሲደቁስ
ጭፍሮቹን አንግሶ - ሰቆቃ ቢለኩስ
በእሳቱ ወላፈን - በወበቁ ጨረር
ርግጥ ባይታወቅ - ነገን ማየት አይቀር
የውስጥ ግብ አንካሴ - ከአድማስ ጫፍ መወርወር
ፍጹም አይገታም - ለድል ቀን መዘመር ፡፡
ምድር በዶፍ ትዕቢት - ዘወትር ብትወቃ !
ምኞት የደም ዕጢ - ሮጦ አያበቃ ፡፡

Saturday, September 8, 2012

‎በቀጣዩ መንግስት የሚወራረዱ ሂሳቦች … ?!?‎






አቶ መለስ በሞት ምክንያት ዱላቸውን ለተተኪው መሪ አላቀበሉም፡፡ ዱላው አንዳንዴም እንደ አራት አንዳንዴም እንደ አንድ በሚያስበው ድርጅት እጅ ነው ያለው ፡፡ ከብዙ ፍትጊያም እንበለው የሰከነ ውይይት በኃላ በአንድ ሰው እጅ ውስጥ መውደቁ የግድ ነው ፡፡ ድርጅቱ ለግዜው ባለዱላውን አይወቀው እንጂ እንዴት መሮጥ እንደሚገባው አስቀድሞ ወስኗል፡፡ ይህን መስመርም ለህዝቡ   ‹‹ የመለስ ፖሊሲና ስትራቴጂን ያለ አንዳች ማዛነፍ እናስቀጥላለን ›› በማለት አውጇል ፡፡

በሌላ አነጋገር አየለም መጣ አየለች ፖሊሲው ትክክለኛ በመሆኑ ሃዲዱን ይዘው እንዲጓዙ ይጠበቃል ማለት ነው ፡፡ እንግዲህ አከራካሪው ጉዳይ የሚጀምረው ከዚህ ምዕራፍ ላይ ነው ፡፡ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ ወገኖች፣ የፖለቲካ ምሁራኖች፣ ጋዜጠኞች፣ ለሚዛናዊ ብይን የቀረቡ ሰዋች የሚሉት አቶ መለስ እንደ ጥንካሬያቸው ሁሉ ደካማ ጎንም ነበራቸው ፡፡ ህዝቡን አንድ አድርጎ ልማቱን በአስተማማኝ መልኩ ለማስቀጠል ከተፈለገ ዱላውን የያዘው ድርጅት ስለ ደካማ ጎናቸውም መስማት ይኖርበታል ፡፡ መስማትም ብቻ ሳይሆን እውነተኛና ተቋማዊ ለውጥ ለመፍጠርም መዘጋጀት ይገባዋል ፡፡

ዱላውን የሚረከበው መንግስት በመስመሩ ወይም በሃዲዱ ላይ የተለመዱትን አሰራሮች ይዤ እሮጣለሁሁ ከሚል ግራና ቀኛ በማየት አማራጮችን መፈተሸ አለበት ፡፡ የድርጅቱ አጋር የሆኑት ሱዛን ራይስ በቀብር ወቅት በዴሞክራሲ ግንባታ ፣ በሰብዓዊ መብት አያያዝና በሲቪክ ማህበራት እንቅስቃሴ ዙሪያ መንግስታቸው ሰፊ ስራ መስራት እንደሚፈልግ ጠቁመዋል ፡፡ ይህን ሃሳብ ጨምሮ ሌሎች መሰረታዊና መፈታት ያለባቸው ጥያቄዋች በብዙሃኑ ህዝብ አእምሮ ውስጥ እየተመላለሱ መሆኑን መረዳት ይጠቅማል እንጂ አይጎዳም ፡፡

ኢህአዴግ ዘግይቶም ቢሆን / የ97 ምርጫ ደውል / በልማት ዘርፍ ላይ አበረታች ውጤቶችን እያስመዘገበ መምጣቱ ይታወቃል ፡፡ ይህን ውጤትም በተሻለ ደረጃ ማሳደግ ይጠበቅበታል ፡፡ አንድ ምሁር የተናገሩትን መሰረታዊ ንግግር ላስከትል ‹‹ ማንኛውም ሀገር በመጀመሪያ መሰረታዊ የሰው ልጆችን መብት በተጻፈ ህግ መደንገግ ይኖርባታል ፡፡ ህጉና ህገመንግስቱ ደግሞ በየዕለቱ በፖለቲከኞችና በባለስልጣናቱ መጠበቅ ይፈልጋል ›› ምሁሩ እንደሚሉት ለዴሞክራሲና ሰብዓዊ መብቶች ዕውቅና በመስጠት ረገድ የሀገራችን ህገ መንግስትም ሆነ ሌሎች ህጎች የተጋነነ ችግር የለባቸውም ፡፡ ችግሩ እነዚህን እንደ ውሃና እንጀራ የሚያሰፈልጉንን መብቶች እንደ ቤት ጌጦች አስቀምጠን ማየታችን ነው ፡፡ የሚያምር ህግ ነው ከማለት ውጪ ከጥቅማቸው እንድንጋራ በተግባር አልተተረጎመም ፤ ሶስቱ ጉልበተኞች / ስራ አስፈጻሚ፣ ህግ አውጪውና  ተርጓሚው / አስፈላጊ በሆነ ግዜ ሁሉ ሺሸራርፏቸው የማስፈጸም ችግር አለ በሚል ይታለፋል ፡፡

ከሲቪል መብቶች ውስጥ የመናገር ፣ የመጻፍ ፣ የመቃወም ፣ ነጻ የፍርድ ቤት አሰራርና የመልካም አስተዳደር አሰራሮችን ለአብነት ብናነሳ ሰፊ ችግሮች የሚታይባቸው ናቸው ፡፡

መረጃ የሚገኝባቸውና ነጻ ሃሰብ የሚተላለፍባቸው ጋዜጦች በተለይም ከ1997 ምርጫ ወዲህ አደጋ ውሰጥ መውደቃቸውን ጥናቶቸ አረጋግጠዋል ፡፡ ጋዜጠኞች በትልቅ በትንሹ ከመከሰስና ከመዋከብ አልፈው ህትመቶች ስርዓት በሌለው መንገድ እንዲዘጉ ይደረጋል ፡፡ ማተሚያ ቤቶች የፈለጉትን ማተም የማይፈልጉትን ቀይ ማሳየት ጀምረዋል ፡፡ መቼም በራሱ የሚተማመን ፣ ለልማትና ፈጠራ የተጋ ፣ በሀገሩ ተግባር የማይሸማቀቅና ነጻነት የሚሰማው ፣ የሰለጠነ አመለካከት ያለው ህብረተሰብ ለመፍጠር ንባብና ከወቅታዊ መረጃ ጋር የተገኛኙ ዜናዋች ሁሉ አስፈላጊ ግብዓቶቹ ናቸው ፡፡ እነዚህን ግብዓቶች ከመንግስታዊ ሚዲያዋችና ጋዜጦች ማግኘት ይቻላል የሚል የውስጥ አቅጣጫ ካለ የታመመ አሰራር በመሆኑ ቀዶ ጥገና ያስፈልገዋል ፡፡ የታመመው ደግሞ ከህገ መንግስቱ መብቶች ጋር በመቃረኑ ነው ፡፡ መቼም ይህ ህገ መንግስት እያለ ‹  ቻይናም ያደገችው ዴሞክራት ሳትሆን በመሆኑ እንቀጥልበታለን ›  ማለት ወደ ለየለት ህመም መድረስን ያሳብቃል ፤ ምክንያቱም የቻይናን የፕሬስ ፈለግ ለመከተል መጀመሪያ ህገ መንግስቱን በወፍራም ቀለም መደለዝ  ስለሚያስፈልግ ፡፡ በመሰረቱ የግል ጋዜጦችና መጽሄቶች ሁሉ አጥፊ ተልዕኮ አላቸው ከሚለው ጭፍን አመለካከትም መጽዳት ያስፈልጋል ፡፡ የግል ፕሬሱ የተዛነፉና አድሏዊ አሰራሮችን ነቅሶ በማሳየት ረገድ አይነተኛ ሚና እንዳለውም መቀበል ያስፈልጋል ፡፡ ከዚያ በመለስ የሚታይባቸውን የእውቀትና የአሰራር ችግር ማስተማር ይቻላል ፡፡ ማስተማር ብቻ ሳይሆን መንግስት ንፉግ ሆኖ የቆየበትን መረጃ የመስጠት ግዴታና ኃላፊነት ማሰተከከል ይኖርበታል ፡፡ መንግስትን መተቸት የሚያስፈራና አሳሳሪ መሆን የለበትም ፡፡

ለነገሩ ብዙም አይወራላቸውም እንጂ የመንግስት ጋዜጠኞችም የኤዲቶሪያል ነጻነት የላቸውም ፡፡የሙያው ስነምግባር በሚፈቅደው መልኩ ስራቸውን እንዳይሰሩ ያደረገው የአቅም ችግር ብቻ ሳይሆን የመንግስት የበዛ ጣልቃ ገብነት ነው ፡፡ በዕውቀትና በልምድ የላቁ ጋዜጠኞች የድርጅት አባል እንዲሆኑ ይገደዳሉ ፡፡ ቦታቸውንና የዕለት እንጀራቸውን ላለማጣት ሲሉ ስነ ምግባሩ በማያዘው ጎዳና ውስጥ ገብተው ይዳክራሉ ፡፡ የድርጅት አባል ሆኖ ደግሞ የምርመራ ጋዜጠኝነትን ፣ የመልካም አስተዳደር ችግርን እዘግባለሁ ማለት አይቻልም ፡፡ እረ የድርጅት አባል ሆኖ ህዝባዊ ጋዜጠኛ ነኝ ለማለት ሞራል ይተናነቃል ፡፡ 

ከትንሷ ሀገር ኬፕ ቨርድ እንኳ ብዙ መማር ይኖርብናል ፡፡ ይች ሀገር ከ 2006 ጀምሮ እያሳየች በመጣችው የፕሬስ ነጻነት ከአፍሪካዊው ሞ ኢብራሂም ፋውንዴሽን የዘንድሮው ተሸላሚ ሆናለች ፡፡ እንደሚታወቀው የዓለማችን ሶስት የፕሬስ አፋኝ ሀገሮች ኤርትራ ፣ ሰሜን ኮሪያና ሶርያ ናቸው ፡፡ ቀም ነገሩ እኛስ ? የሚለውን ጥያቄ ጠይቆ በአግባቡ መመለሱ ላይ ነው ፡፡ ፍሪደም ሀውስ ፕሬስ በያዝነው ዓመት የዓለም ሀገራትን ከዲሞክራሲና ከፕሬስ ነጻነት አንጻር በይኗቸው ነበር ፡፡ በዚሁ መሰረት ኢትዮጽያ ከ194 ሀገሮች 176ተኛ ላይ ተቀምጣለች ፡፡ ነጻ ያልሆነች ዞንም ብሏታል ፡፡ ሀገራችን ከአፍሪካ አንጻር እንኳ ደረጃዋ ሲታይ የሚያሳፍር ነው ፡፡ 43ተኛ ናትና ፡፡ ይህች ያልተገዛች ፣ ስለ ነጻነት የምታውቅ ለጎረቤቶቻም ድጋፍ ስትሰጥ የነበረች ሀገር መጨረሻ አፋፍ ላይ መታየት ነበረባት ? 

ባንዲራና መፈክር ያነገቡ ተቃዋሚ ሰልፈኞችን ማየት አልናፈቃችሁም  ? ይህ መሰረታዊ መብት ለምን ኮሰሰ  ?  መቼም የመቃወሚያ ርዕሰ ጉዳይ ጠፍቶ አይደለም ፡፡ በነገራችን ላይ የተቃውሞ ተቃራኒ ወንድም የሆነው ‹ ድጋፍ ወይም ድጋፌ › ግን አልፎ አልፎ ብቅ ከማለት አልተቆጠበም ፡፡ ታዲያ ይህ ድጋፍ መልኩ ወደ ሁለት መቀየሩን ልብ ይሏል ፡፡ መንግስት በደስታ ሲገለፍጥ  አደባባይ ወጥቶ ይጨፍራል ፡፡ መንግስት በሆነ ጉዳይ ሲናደድ አደባባይ ወጥቶ ያስከፋውን ነገር ያወግዝለታል ፡፡ ዞሮ ዞሮ ድጋፍና ተቃውሞ ለዴሞክራሲ ስርዓት ጠቃሚ በመሆናቸው እንደ አቤል እና ቃየን የተለየ ትርጉም አይሰጣቸው ነው ጥያቄው ፡፡

በየመ/ቤቱ በሚካሄድ ስብሰባ ላይ ሰራተኞች ጭብጥ ብለው እንደገቡ ለምን ጭብጥ ብለው ይወጣሉ ? እንዲጠይቁና አስተያየት እንዲሰጡ ሲነገር አንገታቸው ወደ መሬት ያዘቀዝቃል ፡፡ የሚናገሩት ችግር ሳይኖር ቀርቶ ነው ? አንዳንዴ ከሰብሳቢው የተሻለ እውቀት ሳይኖራቸው ቀርቶ ነው ? አይደለም ፡፡ ጠንከር ያለ ሃሳብ ከሰነዘሩ ጀርባቸው ይጠና … የሆነ አመለካከት ተሸካሚ ሳይሆኑ አይቀርም … የእገሌ ደጋፊ ናቸው … የሚለውን ማሰፈራሪያ ወይ በግምገማ ወይ በሌላ አጋጣሚ ስለሚሰሙ እንጂ ፡፡ እናም ቢያውቁም ባያውቁም ይሐው ‹‹ ጎመናን በጤናን ›› በሆዳቸው አሳምረው መዘመር ከያዙ ስንት ዘመን አለፈ ፡፡ እንግዲህ የዴሞክራሲ ስርዓት ከሚፈልገው ግብዓት አንዱ  የሆነው  ‹ ተሳትፎ › ዛሬ ስግግ ያለ ስዕል ያገኘ መስሏል  ፡፡

ፍርድ ቤቶቻችን ፍትሃዊ አሰራርን ማስፈን ግን አልቻሉም  ፡፡ ቀጠሮውና መመላለሱ ወገብ ያነክታል ፡፡  ህገ መንግስቱ የሰጣቸው ነጻ አሰራር ተግባራዊ አልሆነም  ፡፡ አቶ ስዬን የለቀቀው /ቤት በሆነ የፖሊስ ተቋም መንገድ ላይ ሲጠለፍ ተቋሙን ለመክሰስና  የህግ የበላይነትን ለማሳየት አቅም የለውም ፡፡ ፖሊሶች ለበርካታ ግዜያት ስለሰብዓዊ መብት አያያዝ ስልጠና ቢወስዱም ዛሬም አይናችን እያየ  ግለሰቦችን በየአደባባዩ ይወግራሉ  ፡፡እረ በህጉ መሰረት… › ብሎ አስተያየት ለመስጠት የከጀለ ጀርባው ላይ ወፍራም ዱላ ሊያርፍበት ወይም የአይጥ ምስክር ዲንቢጥ ተብሎ  ወደ ጣቢያ ሊጎተት ይችላል ፡፡ ለአንዳንዶቹ  እስረኞችን  አለማክበር ፣ ማንጓጠጥ ፣ መሳደብ የተፈቀደላቸው ይመስላል ፡፡ የሰብዓዊ መብቶች ሪፖርት እንደሚገልጸው ዜጎች ዛሬም በማያውቁት ሁኔታ ይታሰራሉ፣ ይገረፋሉ ፡፡

ኢህአዴግ ብሄር ብሄረሰቦችን የሚገልጸው ‹ ልዩነታችን ውበታችን ነው › በሚል አሪፍ አገላለጽ ነው ፡፡ ይህ ውበት ለባህልና አኗኗር ብቻ ሳይሆን ለአመለካከትና አስተሳሰብም መዋል ይኖርበታል ፡፡ እሱን የሚደግፉ እንዳሉ ሁሉ የሚቃወሙና የሚተቹ  መኖራቸውንም ከልብ መቀበል ያስፈልጋል ፡፡ የዴሞክራሲም ውበት እዚህ ላይ ነው ፡፡ እኔን ብቻ አዳምጡኝ ወይም ተከተሉኝ ካልሆነ ግን መጥፎ ስምና ታርጋ እለጥፍባችኃለሁ ማለት የዴሞክራቶች ፍልስፍና አይደለም ፡፡ በራስ ድምጽና ዘፈን ብቻ ከመደሰት ይልቅ የሌሎችንም ዜማ ማጣጣም ‹ ልዩነት ውበት ነው › የሚባለው ብሂል አካል መሆኑን መቀበል ያስፈልጋል ፡፡ በአጠቃላይ የዴሞክራሲውን ግንባታ የሚያኮሰምኑ ተግዳሮቶችን አዲሱ መንግስት መቃኝት ይጠበቅበታል ፡፡
ልዩ ልዩ የሲቪክና የሙያ ማህበራት እንዲደራጁና በልማትና በዴሞክራሲ ግንባታው ውስጥ ትልቅ ሚና እንዲጨወቱ እገዛ ማድረግ ቢቀድምም አምሳያቸውን ፈጥሮ እንዲኮሰምኑ የማድረግ አሰራርን ስንከተል ቆይተናል ፡፡ አዲሱ መንግስት ይህን አካሄድ በድፍረት ተችቶ የተሻለ አቅጣጫ ማሰቀመጥ ይኖርበታል ፡፡


Monday, September 3, 2012

ጥቁርና ነጭ ንግግሮች




የጠ/ሚ/ር መለስ ስርዓተ ቀብር ከመርዘሙና በተፈጥሮ ዝናብ ከመታወኩ በስተቀር የተዋጣለት ነበር ፡፡ በርግጥ ወደ መጨረሻ አካባቢ የጣለው ዝናብ ከሰሜን ኮሪያው ፕሬዝዳንት ኪም ጆንግ ኢል  ቀብር አንጻር ከታየ ‹ ጥቂት ነው  › የሚባል ዓይነት ነው ፡፡ የያኔው ቀብር ሶስት ሰዓታት ሲፈጅ ኃይለኛ በረዶ አልተለየውም ነበር ፡፡ እንዲያም ሆኖ ትንሽ ትልቁ፣ ሲቪል ሰራዊቱ መንገድ ላይ ወጥቶ አንብቷል ፡፡ የሀገሪቱ ጋዜጣም ኃይለኛውን ዝናብ ‹‹ የገነት ዝናብ ›› ሲል ጠርቶታል፡፡ በሀገራችን ባህል ቀብርን ዝናብ እንዲያውክ ባይፈለግም አንድ እናት  ‹‹ ለመለስ ፈጣሪም አለቀሰለት! ›› በማለት አዛማጅ ትርጉም ሰጥተውታል ፡፡
የመሸኛ ስነስርዓቱ የአቶ መለስን የተሳካ የመሪነት ተግባር በታዋቂ ሰዋች ማስመስከር ላይ ያነጣጠረ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ሁሉም ተናጋሪዋች የአቶ መለስን ተክለ ሰውነት በተመቻቸው መንገድ ገልጸውታል ፡፡ ሳቢ ንግግሮችንም አድምጠናል ፡፡አልፎ አልፎ ግን የመስካሪዋቹን ውብ ቋንቋና ከቋንቋው ጀርባ ያለውን ጉዳይ ያለቦታው እያነጻጸርኩ ከጥቁርና ነጭ ምስሎች ጋር ተላትሜያለሁ፡፡
 
ለምሳሌ ዩዎሪ ካጉታ ሙሴቬኒ ምስክርነታቸውን ሲገልጹ የነበሩት ወረቀት ሳያነቡ ነው ፡፡ ጣፋጭ ንግግራቸው ብቻ ሳይሆን ተክለ ቁመናቸውም ፊልም ከሚሰራ ካው ቦይ ጋር ይመሳሰላል ፡፡ ታዲያ እንዲህ እንዳፈዘዙኝ ስልጣን ወደያዙበት 1986 በሀሳብ አፈናጠሩኝ፡፡ ያኔ ‹‹ ማንኛውም የአፍሪካ መሪ በስልጣን ከ10 ዓመት በላይ መቆየት የለበትም ›› በማለት በይፋ ተናግረው ነበር ፡፡ ዛሬ ረስተውት ይሆን ? ይኀው እሳው በስልጣን ላይ 26 ዓመታቸው ፣ ለነገሩ ይሄ የአፍሪካ መረዎ በሽታ ነው ። 
 
አቶ ኩማ ደመቅሳ ኦማር ሀሰን አህመድ አልበሽርን ‹‹ ፊልድ ማርሻል ›› እያሉ ሲያስተዋውቁ ሰማው ልበል ?  ‹‹ ፊልድ ማርሻል ›› መድረሳቸውን መቼ ሰማሁና ?! እኚህ መሪ ከ2003- 2009 ባሉት ግዜያት ከአምስት መቶ ሺህ በላይ ሰዋች ማስገደላቸውንና በተመድ ከሚፈልጉ  መሪዋች አንዱ መሆናቸውን ግን አውቃለሁ ፡፡ አፍሪካዊያን መሪዋች ግን ይህን ክስ አልተቀበሉትም ፡፡ ‹  በሰው ጉዳይ ጣልቃ እየገቡ የሚፈተፍቱ ነጮ ›  በኛ ጉዳይ አያገባውም ይላሉ - ከሳሾቹን ፡፡ እርዳታ በሚፈልጉ ግዜ ደግሞ ነጫጭባ የሚቸውን ነጮጭ ወደ መላዕክትነት ይቀይራሉ ፡፡ እናም አልበሽር መኪና ፈርቶ ዳር ዳሩን እንደሚጓዝ ገጠሬ ጥግ ጥጉን ሲጓዙ ዘመናት አስቆጥረዋል  ፡፡ ግን ነጻነትን እንዴት ይሆን የሚተረጉሙት ?
አሜሪካዊቷ አምባሳደር ሱዛን ራይስ ጥቁርና ነጭ ብቻ ሳይሆን ቀይ ቀለምንም ጨምረው የተናገሩ ብልህ ዲፕሎማት ናቸው ፡፡ ልብ በሚነካው ሀዘናዊ ቋንቋ የወ/ሮ አዜብ መስፍንን ልብ ኮርኩረዋል ፡፡ አሜሪካና አቶ መለስ የነበራቸውን ጥብቅ ቁርኝት መግለጻቸው ብቻ ሳይሆን ታላቋ ሀገር ዛሬም ለኢህአዴግ ቀኝ እጅ ሆና እንደምትቀጥል ማረጋገጣቸው ሁለተኛው ቀለም ነው ፡፡ ኢህአዴጎች ዲፕሎማሲያዊ ግባችንን እንደ ምርጫችን 99 ከመቶ አሳካን ብለው የሚያስቡትም ይህንኑ ይመስለኛል ፡፡
 
እኚህ ብልህ ዲፕሎማት የመጡት የሀዘን ተካፋይ ለመሆንና የሽብርተኞችን ጉሮሮ አንቃ የቆየችውን ምስራቃዊ ሀገር ‹ አይዞሽ › ለማለት ብቻ አይደለም ፡፡ ለሀገሪቱ አባታዊ ቡራኬ ለመስጠትም ጭምር እንጂ ፡፡ ቡራኬው በፓለቲካዊው ጎዳና ላይ ምን እንደሚጓዝና እንዴት እንደሚንቀሳቀስም አቅጣጫ ያስቀምጣል ፡፡ ይህን አቅጣጫ በንግግራቸው መጨረሻ አካባቢ በገደምዳሜ ጠቁመውታል ፡፡ ሀገራችን ዴሞክራሲን፣ የሰብዓዊ መብት አያያዝና የሲቪክ ማህበራትን እንቅስቃሴ አጠናክራ እንድትቀጥል በመናገር ፡፡
ትንሽ ደቂቃ የቆየው የወ/ሮ አዜብ መስፍን ንግግርም ብዙ ሰዓታት ሊያወያይ የሚችል ፍቺ ያቀፈ ይመስላል ፡፡ ‹‹ የመለስ ፓሊሲና ስትራቴጂ እስካልተበረዙ ድረስ ዓላማው እውን ይሆናል ›› የሚል ሀሳብ ፈንጥቀዋል ፡፡  ‹ ድርጅቱ ያለምንም ለውጥ ያለውን አሰራር ይዞ ይቀጥላል ›  ከሚለው የሃላፊዋቹ አስተሳሰብ ጋር የእሳው ንግግር ለምን ተቃረነ ? ወይም ስጋት ያደረበት መሰለ ብሎ መጠየቅ በርካታ ሚስጢሮን ሊያስገኝ ይላል ።
 
ይበልጥ ትኩረቴን የሳበው ግን በአቶ መለስ ምንነት ላይ የተነገረው ንግግር ነው ፡፡ ‹‹ መለስ ቢል ቦርድ እንዲለጠፍለት ፣ ሃውልት እንዲቆምለት አይፈልግም ! ›› የሚለው ፡፡ ቀደም ብሎም መለስ ስለ ራሱ ማውራትም ሆነ እንዲወራለት አይፈልግም የሚል ሀሳብ ከትግል አጋሮቹ ተንጸባርቋል ፡፡ ታዲያ በእለቱ አቶ መለስ እንዴት ሲገለጹ ነበር ? ለተገላጩ ይሰጡት የነበሩት ቅጽሎች ከላይ የተጠቀሰውን ሀሳብ ያከበሩ አይመስልም ፤ ገደል የከተቱ እንጂ ፡፡ ካድሬዋቹ የማንነት ብቻ ሳይሆን የድርጅት ገጽታ ግንባታ እየሰሩ መሆኑ ግልጽ ቢሆንም ጥንቃቄን  ‹ ዞር በል ባክህ ! › ያሉት ያስመስላል ፡፡ በዕለቱ ንግግሮች ውስጥ አቶ መለስ በርካታ መለዮና ካፖርት አጥልቀው ነበር :: ብዙዎቹ ግን በልካቸው የተሰፉ አልነበረም ። ተንቦርቅቀው ያስጠላሉ ። አንዳንዶን እንጥቀሳው ።
 
የህዳሴ መሃንዲስ
የለውጥ ጠንሳሽ
የተስፋ አባት
የድሃ አባት
ታላቁና በሳሉ
ገናና መሪ
ተወርዋሪ ኮኮብ
ብልሁና አስተማሪው
የቁርጥ ቀን ታጋይ
ብርቅዬ የአፍሪካ ልጅ
ባለ ራዕይ
የህግ ምሁር
የወታደራዊ ሳይንስ ቁንጮ
ሳይንቲስት
ዴሞክራሲያዊ እሴቶችን ያከበረ መሪ
ሆደ ሰፊ መሪ
ለዓለም አቀፍ ህግ ራሱን ያስገዛ መሪ
አፍሪካዊ መሪ
ህዝባዊ መሪ
የጸረ ደህንነት አርበኛ መሪ
የአፍሪካ ቃል አቀባይ
ህዝባዊ ፍቅር የተላበሰ መሪ
የማይናወጥ የዓላማ ጽናት ያለው መሪ በሚሉ ሀሳቦች ተገልጸዋል ፡፡ በርግጥ አንድ ሰው ይህን ሁሉ ሊሆን አይችልም ፣ ከሆነ ደግሞ የዓለም አስደናቂው መጽሀፍ ላይ መስፈር ነበረበት :: ፖለቲከኞቹ ጊነስ ቡክ ላይ ማስመዝገብ ትተው ሰው ሲሞት ይህን ሁሉ ካፖርት ማሽከም ማዕረግ መሆኑ ነው ?
 
እንደዚህ ዓይነት ምስል መፍጠርም ለማንነታቸው ሌላ ትርጉም የሚያሰጥ ነው የሚሆነው ፡፡ ለምሳሌ ያህል የሰሜን ኮሪያው ኪም ጆንግ ኢል  50 የሚደርሱ ልዩ ልዩ መጠሪያዋች ነበሩት ፡፡ ጓድ ሊ /መንበር ፣ የላቀው ሊ/መንበር ፣ የኛ አባት ፣ የተለየው ጄነራል ፣ የሀገሪቱ ጭንቅላት ፣ ጀግናው ፣ የሁሌም ባለድል ፣ የ21ኛው ክ/ዘመን መሪ ኮኮብ ፣ አስገራሚው ፓለቲከኛ የሚሉት ከብዙ ጥቂቶቹ ናቸው ፡፡ ይህ መሪ ግን በተግባር ከነሂትለርና ስታሊን ጋር የሚነጻጸር አምባገነን እንደነበር የፓለቲካ ምሁራን አረጋግጠዋል ፡፡
 
ኢዲያምን ዳዳንም ማስታወስ ይቻላል ፡፡ ይህ መሪ ራሱን የሚጠራው ‹‹ የተከበረው የእድሜ ልክ ፕሬዝዳንት ፣ ፊልድ ማርሻል አልሀጂ ዶክተር ኤዲያሚን ፣ በምድር ላይ የሚገኙ እንስሳትና በባህር ውስጥ የሚገኙ አሳዋች ሁሉ ጌታ ፣ የእንግሊዝን መንግስት በመላው አፍሪካ በተለይም በኡጋንዳ ያሸነፈ ›› በሚል ነበር ፡፡ ታዲያ የአቶ መለስስ ከዚህ በምን ይለያል ? 
 
እናም ጎበዝ ግራና ቀኝ ማየት የሚገባው መስቀለኛ የትራፊክ መንገድ ላይ ሲቆም ብቻ አለመሆኑን ደጋግሞ ማሰብ ያስፈልጋል ፡፡



Tuesday, August 28, 2012

ሞትና ንግድ





ታዋቂ ሰዋች ሲሞቱ የብዙዋች ትኩረት ወደ ሟቾቹ ይሳባል  ፤ ይህ የሚሆነው ደግሞ በብዙ ምክንያቶች ነው ፡፡ ሰዋቹ በሰሯቸው ታላላቅ ስራዋች ክብርና ሞገስ ስለሚያገኙ እንዲሁም ከብዙዋቹ ታላላቅ ሰዋች ጀርባ አከራካሪና አወዛጋቢ ጉዳዮች በመኖራቸው  ብሎ መጥቅለል ይቻላል ፡፡

አንዳንድ ሰዋች ታዋቂዋቹ በህይወት እያሉ ግልብ በሆነ አድናቆትና ፍቅር ውስጥ ነው የሚያስቧቸው ፡፡ ለአድናቆታቸውና ለፍቅራቸው መሰረት የጣለላቸውን አብይ ጉዳይ ካወቁ በቂ ነው ፡፡ ታዋቂዋቹ በሞት ሲለዩ ግን ከመደናገጥና ከመሸበር ባሻገር የመጸጸትና የጥፋተኝነት ስሜት ያበቅላሉ ፡፡ ስለ ሰውዬው ማንነት የሚገልጹ ስራዋችን ከዛሬ ነገ አያለሁ፣ አነባለሁ፣ ለማወቅ ጥረት አደርጋለሁ እያሉ የቆዩበትን መንገድ ይተቻሉ ፡፡

በሁለተኛ ደረጃ የታዋቂ ሰዋች ህይወት ባለ ሁለት መስተዋት መሆኑ ይታወቃል ፡፡ ህዝቡም ሆነ አድናቂው የሚያውቀው የፊት ለፊት ገጽታቸውን ነው ፡፡ የጀርባ ህይወታቸው ከባህል፣ ፓለቲካ፣ ስነ ልቦናና ማህበራዊ ህይወት አንጻር ያፈነገጠና በግጭቶች ውጤት ያበጠ በመሆኑ በብዙ መልኩ ደብቀውት ይጓዛሉ ፡፡ ስለዚህ ህብረተሰቡ አንድም ይህን የተደበቀ ማንነታቸውን በሌላ በኩልም አጉድሎ ያቆየውን ፕሮፋይል ለማወቅ በብርቱ ይፈልጋል ፡፡ ከሞቱ በኃላ የሚያገኛቸው ልዩ ልዩ መረጃዋች ስሎ የቆያቸውን ጀግኖች ይበልጥ ለማክበርና ለመዘከር ይረዳዋል ፡፡ ተቃራኒ በሆነው ስብዕናቸውም ለመደመም፣ ሚዛናዊ ምስክርነቱን ለመስጠት ብቻ ሳይሆን እይታውን በማስፋት ትምህርትና ልምድ ለመውሰድ ይጠቀምበታል ፡፡

ይህ የሰው ልጆች የጋለ ባህሪ ነው ፡፡ እንግዲህ ይህን  ተዝቆ የማያልቅ ፍላጎት በማንበብ ነው ‹ አቅርቦት › ፈጣሪዋች ምናባቸውን የሚያሰሩት ፡፡ ለምሳሌ ያህል የማይክል ጃክሰን ልጆች ምግብ ማዘጋጃ ክፍል ውስጥ ባለ ጥቁር ሰሌዳ ላይ ‹ I Love Daddy › ብለው የጻፉት የተለመደ ስሜትን መግለጫ ሃሳብ  ከሞተ በኃላ በ 5 ሺህ ዶላር ተሸጧል ፡፡ አርቲስቱ ጠዋትና ማታ ፊቱን የሚያይበት የቁም ሳጥን ደግሞ 25 ሺህ 750 ዶላር አውጥቷል ፡፡ የሙዚቃ ስራው  ተለቆ 170 ሚሊዮን ዶላር አስገኝቷል ፡፡ 

ስፔናዊውን ስመ ጥር ሰዓሊ ፓብሎ ፒካሶን ብዙዋች ያውቁታል ፡፡ ግንቦት 2010  Nude, Greeen Leaves and Bust የተሰኘው ስራው ለጨረታ ቀርቦ በ105 ሚሊዮን ዶላር ተሸጧል ፡፡ ይህ ስራ በ1951 የተሸጠው በ19 ሺህ 800 ዶላር ብቻ ነበር ፡፡ የዊትኒ ሀውስተን ቀሚስ 20ሺህ 480 ዶላር፣ የኤልቪስ ፕርስሊ የሞተር ሳይክል ጃኬት 41 ሺህ 600 ዶላር አውጥቷል ፡፡ በወቅቱ ብዙም ልብ ያልተባሉ ንግግሮች፣ መሸጥ ያቆሙ ካሴቶች ወይም የፎቶ አልበሞች ተጠርዘው ለህትመት ሲበቁ ሚሊዮኖች ያለ ጥያቄ ይገዟቸዋል ፡፡ አንድም ድሮ የዘለልኩትን መረጃ አገኛለሁ በሚል አንድም ለማፍቀርና ለመዘከር ፡፡

የአገራችን የሙዚቃ ንጉስ ጥላሁን ገሰሰ ሲሞት ያልደነገጠና ያላዘነ ሰው አልነበረም ፡፡ ጥላሁን እጅግ የሚከበር የመሆኑን ያህል አነጋጋሪ ማንነቶች እየተከተሉት የቆየ አርቲስት ነበር ፡፡ በተለይም በራሱ አንደበት የተገለጸው ‹‹ የሆድ ይፍጀው ! ››ን እውነተኛ ታሪክ ብዙዋች ማወቅ ይፈልጉ ነበር ፡፡ ከደራሲ ስብሃት ገ/እግዚአብሄር፣ ማሞ ውድነህና አፈወርቅ ተክሌ በበለጠ መልኩ በጥላሁን ላይ የንግድ ስራዋች በስፋት ተከናውነዋል ማለት ይቻላል ፡፡ ልዩ ልዩ ፎቶዋቹ  ‹የዝነኛው…የአንደኛው …የንጉሱ .. › በሚል ማስታወቂያ ታጅበው እንደ ጉድ ተሽጠዋል ፡፡ ፎቶውን የያዙ የቁልፍ መያዣዋች፣ የማይጠገቡ ድምጾቹን ያቀፉ ዘፈኖች ፣ ማንነቱን የሚተርኩ የህትመት ውጤቶች ገበያ ላይ ውለው ብዙ አልቆዩም ፡፡ የስብሃት ገ/ እግዚአብሄር የተወሰኑ መጻህፍት ጀትን መወዳደር በቻለ ፍጥነት ታትመው አንባቢው ያለበትን ክፍተት ብቻ ሳይሆን የነጋዴዋችንም ኪስ መሙላት ችለዋል ፡፡

በቅርቡ አቡነ ጻውሎስና ጠ/ሚ/ር መለስ በሞት ተለይተዋል ፡፡ የአቶ መለስ እልፈት አቡኑን በመሸፈኑ ማየት የሚገባንን ንግዳዊ ትርዒት ገድቦብናል የሚል እምነት አለኝ ፡፡ የአቶ መለስን ሞት ተከትሎ እየታየ ያለው ንግዳዊ ስርዓት ግን የሚገርም ሆኗል ፡፡ በከተማችን በሁሉም ማዕዘን ሌላ ነገር ሲሰሩ የነበሩ ወይም ስራ ያልነበራቸው ወጣቶች የመለስን ፎቶ በተለያዩ መጠን በማሳተም ከሁለት እሰከ አስር ብር ይሸጣሉ ፡፡ በተለይም የቀብር ስነ ስርዓቱ እንደ ሀገራችን ፍርድ ቤቶች ረጅም ቀጠሮ የተያዘለት መሆኑን መሰረት በማድረግ አቀራረባቸውን አሳድገዋል ፡፡ የመጀመሪያዋቹ ቀናት ሲሸጡ የነበሩ ፎቶዋች ልሙጦች ነበሩ ፡፡ በሂደት ግን ፎቶዋቹ ላይ ሳቢ ጥቅሶች እንዲጨመሩበት አድርገዋል ፡፡ በአንድ ወረቀት ላይ ሁለትና ሶስት ፎቶዋችን በማካተትም የገዢውን ትኩረት ለመሳብ ጥረዋል ፤ አነጋገራቸውስ ብትሉ !! በፊት ‹ የጀግናው መሪ ማስታወሻ አያምልጣቸሁ ! › የሚል ነበር ፡፡ አሁን ደግሞ ‹ ሞቶም ስራ የፈጠረውን መለስ ዜናዊን በእጅዋ ያስገቡ ! › ወደሚለው ማዕረግ ተሸጋግሯል  ፡፡

እንደ ፎቶው አይብዙ እንጂ ሰው የበዛበት ቦታ ላይ ጥቅስ እያነበቡ በመሸጥ የሚተዳደሩ ሰዋች እንዳሉ ይታወቃል ፡፡ የነዚህ ሰዋች ስነ ልቦና የማንበብ ትጋት በጣም የሚያስገርም ነው  ፡፡ ድሃ የበዛበት አካባቢ

‹‹ ድሃና አክተር ይንገላታል እንጂ አይሞትም ! ››

‹‹ ምንም ድሃ ቢሆን ባይኖረው ሀብት
ከደጃፍ ሲቀመጥ ደስ ይላል አባት ›› የሚሉ ዓይነት ጥቅሶችን ለገበያ ያቀርባሉ ፡፡ መርካቶ መንገድ ላይ የሚነግዱ እናቶች ጋ ጠጋ ብለው ደግሞ     

‹‹ እናት ለምን ትሙት ትሂድ አጎንብሳ
   ቅማል ታገኛለች በጨለማ ዳብሳ ›› ካሉ መሃረብና መቀነቶች የግድ መላላታቸው አይቀርም ፡፡
ቤተክርስትያን አካባቢ ‹ እግዚአብሄርን ፈልጉት ትጸናላችሁም !! › የሚል ዓይነት ጥቅሶችን ከነመገኛ ቁጥራቸው ሲያንበለብሉ መልስና ብርታት የሚሹ ልቦች በፈገግታ ይቀበሏቸዋል ፡፡  ዐስርቱ ትዕዛዛትን ከሚያምር ስዕል ጋር አስደግፈው ያቀርባሉ ፡፡ በሰሙነ ህመማት ግዜ ከሰኞ እስከ እሁድ ያሉ ቀናቶች ያላቸውን ሚና በመጻፍ ጮክ ብለው ያስተዋውቃሉ ፡፡ ታዲያ ለዚህ መሰሉ አስታዋሽ ጥቅስን መግዛት አይደለም ‹ ይባርክህ ! › የተሰኘውን ብሩክ ምርቃት መጨመርስ ምን ይጎዳል ? ምንም ነው መልሱ ፤ ሰዋቹ ድንገት እንኳን አፈንግጠው

‹‹ በማያልቀው እቃ እየተነገደ
  ሴቱ በማርቼዲስ ወንዱ በእግሩ ሄደ ››  ቢሉ አንዴ በበጎ ያወጡትን ‹ ይባርክህ - ይድፋህ ! › በሚለው ለመለወጥ አቅም አይኖሮትም ፣ ባይሆን በስሱ ፈገግ ይላሉ እንጂ ፡፡ የነሱም ዓላማ ሳቅና ትኩረትን በጅምላ ማጋባት ነው - ቻይናዋች ፈገግ የማይል ሱቅ አይክፈት እንደሚሉት ፡፡ ጥቅሰኞቹ በትዕዛዝም ሊሰሩ ይችላሉ ፡፡ ለዚህ ምሳሌ የሚሆነው ሃይገር ባስ ላይ ያየነው ‹‹ ጎበዝ የአባይ ቃል ስላለብን ጠጋ ጠጋ በሉ ! ›› የሚለው ልመናዊ ትዕዛዝ ነው ፡፡ የሰሞኑ ወቅታዊ ጥቅሳቸው ደግሞ መልኩ ተቀይሮ

‹‹ አባይ ይገደባል ፤ መለስ ይታወሳል ! ››
‹‹ የሞተው ታጋይ እንጂ ትግል አይደለም ! ››
‹‹ ቆራጡ መሪ እናከብርሃለን ! ›› የሚሉና የመሳሰሉ ሆነዋል ፡፡ ጥቅሱ ብቻ ሳይሆን አነባበባቸው ረጋ ያለና ሀዘንን አቀጣጣይ በመሆኑ ደንበኞች አላጡም ፡፡

የጠ/ሚ/ር መለስን ሞት ምክንያት በማድረግ የልብስ ነጋዴዋችም የአቅጣጫና የቀለም ለውጥ ያደረጉ ይመስላሉ ፡፡ ጥቁር ልብስ ለክፉ ቀን እንደሚፈለግ ቢታወቅም  ጥቁር መዘዝን ሊጠራ ይችላል በሚል ልማዳዊ መመሪያ ድንበር ከልለው እንደሁኔታው ብቻ የሚወዳጁት ጥቂቶች አይደሉም ፡፡ ዛሬ ግን ገለልተኛ ፖሊሲያቸው እንደተጠበቀ መሆኑን በማሳየት የአሰቸኳይ ግዜ አዋጁን ዕውን ለማድረግ ተነስተዋል ፡፡ ጥቁር ሻሽ፣ ቢትልስ፣ ነጠላ፣ ሸሚዝ፣ ኮፍያ፣ ቀሚስ፣ ሱሪ ወዘተ ተፈላጊነታቸው በመጨመሩ ደፋ ቀናውን በእጥፍ አሳድገዋል  ፡፡ ፎቶ ቤቶች ቢታዘዙም ባይታዘዙም በትልቁ አጥበው መስቀል ከያዙ ቀናት አስቆጥረዋል ፡፡ በአነስተኛና ጥቃቅን በህትመት ዘርፍ የተሰማሩ ወጣቶች ቲሸርት ፣ ኮፍያ፣ የደረት ባጅ ፣ ፓስተር ወዘተ በብዛት እያመረቱ ይገኛሉ ፡፡

በየግዜው ዋጋ በመጨመር የሚታወቁት ስጋቤቶች ራሳቸውን ከወቅታዊው ሁኔታ ጋር ለማዛመድ እያሶመሰሙ ይመስላል ፡፡ የት አካባቢ እንደሆነ ባይታወቅም አንድ ስጋ ቤት መጠሪያውን ‹‹ ጀግናው አይሞትም ስጋ ቤት ›› ብሎታል ፡፡ ከስያሜው አጠገብም        ‹‹ ለሀዘን የሚሆን ጥሬና ጥብስ አለ ›› በማለት ያስረዳል ፡፡  ነገና ከነገወዲያም የኢህአዴግን ስትራቴጂዋችንና የትኩረት አቅጣጫዋች እየመዘዙ ለንግድ ስራቸው ስያሜ የሚሰጡ ሰዋች እንደሚኖሩ መገመት ትክክል ነው ፡፡ ጥያቄው ግን ስያሜዋቹ የሚያስተላልፉት መልዕክት ምን ያህል በአግባቡ ተቀናጅቷል የሚለው ነው ፡፡

አንድ ለአምስት የተባለውን አደረጃጀት አንስቶ ‹‹ አንድ ለአምስት ዳቦ ቤት ›› ብሎ መጥራት አሻሚነትን በአዋጅ እንደማስነገር ይቆጠራል ፡፡ የኔ አንድ ዳቦ የአምስት ሰዋችን ጉሮሮ ያረካል ለማለት ከሆነ ጠዋት ጠዋት ከውሃ ጋር የምንውጠውን ኪኒን ዳቦ እያስታወስን በአላጋጭ ፈገግታ ልንደምቅ ነው ፡፡ በርግጥ በተቃራኒው ማሰብ የሚቻል ከሆነ አምስቱ ዳቦ ለአንድ ሰው ረሃቡን ተንፈስ ሊያደርግለት ይችላል ፡፡ በየቀኑ ይህን እንዳናደርግ ግን የተቀደደው ኪሳችን እስካሁን አልተሰፋልንም ፡፡

አንድ ሌላ ነጋዴ ንግድ ቤቴ ጨዋታ በጣም የሚዳመቅበት ስለሆነ ከዛሬ ጀምሮ ‹‹ ሂስና ግለሂስ ጠጅ ቤት ›› ብየዋለሁ ሊል ይችላል ፡፡ አንባቢው ሲተረጉመው ደግሞ ‹ ይህ ሂስና ግለሂስ በጠጅ የደነበዡ ሰዋች የሚንጫጩበት መድረክ ነው ለካ ? › በማለት ቢያፍታታው ትርጉሙ አውዱን ስቷል ብሎ ለመከራከር አያስችልም ፡፡ እንዲህና እንዲህ የመሳሰሉ ነገሮች ተጠባቂ ይመስላሉ ፡፡ ነጋዴዋች በሃሳብ    ‹ በቅርብ ቀን  › የሚል ማስታወቂያ እያዘጋጁ ይመስለኛል ፡፡ ምን ሊሉ  ? ከተባለ

‹ ውሃ ማቆር ግሮሰሪ ›
‹ ድሃ ተኮር ጋዜጣ ›
‹ ቢፒአር ሁለገብ መናፈሻ ›
‹ ትራንስፎርሜሽን ጫማ ቤት › የመሳሰሉትን ፡፡

ጋዜጦችና መጽሄቶች መረጃ ከማድረስ አንጻር ወቅታዊ ሁኔታን መዘገብ ኃላፊነትና ግዴታቸው መሆኑ ይታወቃል ፡፡ ሆኖም የፓለቲካውና የሃይማኖቱ  መሪዋች ማለፍ አቅጣጫዋችንና ገቢያቸውን አለወጠውም  ብሎ መናገር ያስቸግራል ፡፡ አዳዲስ ጉዳዮችን ለመጠቆም የሚጥረውን መረጃ ከላይ በመግቢያዬ እንደገለጽኩት ህብረተሰቡ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ ይፈልገዋል ፡፡ ይህም የህትመቶቹ ኮፒ እንዲያድግ አይነተኛ አስተዋጽኦ ያደርጋል ፡፡ በሌላ በኩል ድርጅቶችና ግለሰቦች ከወትሮው በተለየ ምልከታ የሀዘን መግለጫቸው ጋዜጣ ላይ እንዲወጣ ይፈልጋሉ ፡፡ ይህም ለጋዜጦች ያልታሰበ በረከት ነው ፡፡ እነሆ በግማሽ ዓመት ስራቸውን ሲገመግሙ ‹‹ ከዕቅድ በላይ አትርፈናል ! ›› የሚል የደስ ደስ ያለው ንግግር ይጠቀማሉ ፡፡

የባንዲራ፣ የአበባ፣ የጧፍና ሻማ ገበያም በቀላሉ የሚታይ አይደለም ፡፡ ወቅታዊውን ሞት አዘል ንግድ መዘርዘር ስለሰለቸኝ ወደፊት የሚጠበቁትን አንዳንድ ሁኔታዋች ላመላክት ፡፡ ድርጅቶች ለአዲሱ ዓመት አጀንዳ፣ ፓስት ካርድ፣ የቀን መቁጠሪያ ወዘተ ያሳትማሉ ፡፡ መረጃውን አስቀድመው ወደ ማተሚያ ቤት የላኩ ካሉ መከለሳቸው አይቀሬ ነው ፡፡ መንገድ ላይ ያሉት የፈጀው ግዜ ፈጀቶም ቢሆን ስለ መሪዋቹ ብዙ እንደሚዘክሩ ይጠበቃል ፡፡ ደብተር አሳትመው የሚያከፋፍሉ ድርጅቶች ከከባድ ይቅርታ ጋር በእቅድ የያዟቸውን ታዋቂ ስፖርተኞችና ምርጥ እጆች የተጨነቁባቸውን ስዕሎች ላልተወሰኑ ግዜ ያስተላልፋሉ ፡፡ እነሆ በግማሽ ዓመት ስራቸውን ሲገመግሙ ‹‹ ማቀድ ብቻ ሳይሆን ደራሽ ስራዋችም ያበለጽጋሉ ! ›› የሚል አባባል ያንጸባርቃሉ ፡፡

 ፊልም፣ ቲያትር፣ የቴሌቪዥን ድራማ፣ ሙዚቃ፣ የሙዚቃ ኮንሰርት መነሻውና መድረሻው በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የጠ/ሚ/ር መለስ ተጽዕኖ እንደሚያርፍበት ይገመታል ፡፡ በእንቁጣጣሽ ክብረ በዓል ስፖርተኛ፣ አክተርና መላዕክትን ማዕከል አድርገው ሲጓዙ የቆዩ ወጣቶች በአቡነ ጻውሎስና በአቶ መለስ ህይወት ዙሪያ ያነጣጠሩ ስዕሎች ላይ ቢያተኩሩ ምንም አይገርምም ፡፡

እንደሚታወቀው ሙዚቃ ቤቶች ከበሮው ወፈር ያለ ሙዚቃ ማሰማት አቁመዋል ፡፡ በምትኩ በድምጽ መሳሪያ ብቻ የተቀነባበሩ ሙዚቃዋች እየተሰሙ ናቸው ፡፡ ለዚህ የጥበብ ስራ በርካታ ሰዋች ያን ያህል በቂ ትኩረት ይሰጣሉ ማለት ያስቸግራል ፡፡ እኔ ሳነብም ሆነ ስጽፍ በአብዛኛው የምጠቀመው በክላሲካል በመሆኑ ሊሆን ይችላል  ይህ የጥበብ ስራ ሳይታሰብ በከተማው ገኖ መውጣቱ አስደስቶኛል ፡፡ ይህ ስልት ለዘመናት አላፈናፍን ያሉትን የነሮክ፣ ሬጌ፣ ራፕ፣ ጃዝ ወዘተ የጭቆና ቀንበር የሰበረ ሁሉ መስሎኛል ፡፡ ድሮንስ አንድ ዓይነት ነገር ሲበዛ ይጎመዝዝ የለ ! ጥበቡ ልክ እንደ ቋንቋ በራሱ ሙሉ በኩልሄ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ለጥሞና ፣ ለፍቅርና ራስን ለመመርመር ምን ያህል ፍቱን መድሃኒት መሆኑን እያሳየ ነው ፡፡

 ክላሲካል ህይወት ከጫጫታና ግርግር ወጪ ያላትን የማይፋጅና የማይበርድ ገጽታን በሚያስደምም መልኩ የሚያንጸባርቅ ጥበብ ነው ፡፡ የሙዚቃ የዓለም ቋንቋነት ይበልጥ ደምቆ የሚታየው በክላሲካል ነው ማለት ይቻላል ፡፡ እስኪ ለአብነት የቻይና፣ የጃፓን ፣ የሱዳንና የግብጽን ክላሲካሎች ያዳምጡ ፡፡ የሰሟቸውን ሀገሮች ብቻ ሳይሆን የሰው ልጅን ረቂቅ ማንነት እንደ ቴሌቪዥን ይመለከታሉ፣ እንደ ሬዲዮ ያዳምጣሉ፣ እንደ መጸሀፍ ያነቡታል ፡፡ ፓለቲከኞች ፣ የሃይማኖት አባቶች፣ መምህራን የሚሰብኳቸውንና የሚመኟቸውን ሰላም፣ ፍቅር፣ መተሳሰብና አንድነት በረቂቅ ድምጾቹ ውስጥ ገዝፈው ያገኟቸዋል ፡፡

ነፍስ ይማር !!

Thursday, August 23, 2012

‹‹ አለሁ !! ›› ማለት






የሰው ህያውነት ተቋርኗዊ ግብሩ
ምንድነው ተብሎ ቢጠየቅ ተዓምሩ
መዛኝ... ምጡቅ ... ማህበራዊ
ጨቋኝ ... አጥፊ ... አድሏዊ
በሚል ይበየናል በቁም ሰውነቱ
በዛሬ ምህዋር ነገን በማስላቱ ፡፡
ግና የነገን ጆንያ የውስጡን ቋጠሮ
ማን ያውቃል ? ጭነቱን ድርጊቱን መንዝሮ ፡፡
ፊት ያለችው ጸሃይ የተምሳሌቷ ግርማ
ወበቅ ትደብቅ መብረቅ ፤ ብርሃን ትቀፍ ጨለማ
ማን ያውቃል ? የውሎዋን መዘርዝር
የርግማንዋንና ምርቃቷን ሚስጢር ፡፡
ልምድ ሆኖ ብቻ ‹‹ ፍጡሩ ›› አርበኛ
ነገን ይማርካል ‹‹ ፈጣሪ ›› ሆኖ ዳኛ
አለሁ ይላል ‹‹ ያደገው ›› እንስሳ
እንደዛሬው ሁሉ ነገንም ሳይረሳ
ግና ‹‹ አለሁ ! ›› ማለት
ታላቅ ዘበት ! የዘመኑ እብደት !!!

Monday, August 20, 2012

አፓርታይድ በጓሮ በር መጣ




ከዓለማችን ፈጣጣ ህግ አንዱ አፓርታይድ ነበር ፡፡ የዘር ልዩነትን የሚያራምድ ፓሊሲ በመደንገጉ ፡፡ በህጉ መሰረት ደቡብ አፍሪካዊያን ነጭ፣ ባንቱ፣ ጥቁር አፍሪካና ኤሽያ/ ህንዶች ተብሎ በተከፈለው መሰረት ብቻ ይማራሉ…ይሰራሉ.. ይኖራሉ…

ይህ ጨቋኝ ህግ ማንዴላንና ጓደኞቻቸውን ለ ‹ እረ ጥራኝ ደኑ ! › አነሳሳ፡፡ ክፉው ዘመን ከ 1948 እስከ 1994 አካባቢ ሲቆይ 21 ሺህ ዜጎችን ጨፍጭፏል ፡፡ ሁሉም የጥቁር ት/ቤቶች እንግሊዝኛንና የአፍሪካን ቋንቋ በእኩል መጠቀም ይኖርባቸዋል ብለው ተቃውሞ ለማሰማት ከወጡ 20ሺህ ተማሪዋች መካከል 700 ያህሉ የጥይት ራት ሆነዋል ፡፡ በሶዌቶ ህጻናት በጥይት ሲፈነገሉ የተመለከተ ሰብዓዊ ፍጡር ሁሉ የደም እንባ አፍስሷል ፡፡ ነጭ የደቡብ አፍሪካ ፓሊሶች ወጣቶችን በመርዘኛ ውሾች እያስነከሱ ሲዝናኑም ዓለም አልቅሷል ፡፡

የጸረ አፓርታይድን እንቅስቃሴ የሚመሩት ማንዴላና ጓደኞቻቸውም ለረጅም ዓመታት በሮበን ደሴት በእስር ማቀዋል ፡፡ በህዝቡ  ከፍተኛ መስዋዕትነትና በውጩም ዓለም ግፊት ክሌርክ በፓርቲው ላይ የጣሉትን ዕገዳ ጨምሮ ማንዴላን ለመፍታት ተገደዱ ፡፡ አዲሱ ህገ መንግስትም በፊርማ ጸደቀ ፡፡ በኃላም ዴሞክራሲያዊ በሆነ ምርጫ ስልጣኑ ለተገቢው ህዝብ ደረሰ ፡፡

ዓለምና ነጭ ደቡብ አፍሪካዊያን በቀል ቢፈሩም ማንዴላ ‹‹ ይልቅ ይቅር ተባብለን ብሄራዊ እርቅን እናንግስ  ›› አሉ ፡፡ ያልተጠበቀና የማይታመን የጀግንነት ውሳኔ ነበር ፡፡ በዚሁ መልኩ አፓርታይድ በርህራሄ ተሸንፎ ራሱን ገደለ ፡፡ በጣም ተጸጽቶም ‹ ጉድጓዴን በጣም አርቃችሁ ቆፍሩ ! › ብሎ በተወው የኑዛዜ ወረቀት መሰረት ግብዓተ መሬቱ ተፈጽሟል ፡፡

ሰሞኑን የሞተው አፓርታይድ ተነስቶ ይሁን ወይም እሱ ሲሞት አስረግዞት የነበረው ክፋት በውል ባይታወቅም ሀገሪቱ አስደንጋጭ ጭፍጨፋ አስተናግዳለች ፡፡ በማሪካና በሎንሚን ፕላቲኒየም ድርጅት ውስጥ የሚሰሩ ሰራተኞች ዘወትር ጥልቅ ግድጓድ ውስጥ ከፍተኛ ስራ ብንሰራም የምናገኘው አነስተኛ በመሆኑ ደመወዝ ይጨመርልን የሚል ጥያቄ ያነሳሉ ፡፡ የሰራተኞቹ ደመወዝ ከ 4 እስከ 5 ሺህ ራንድ የሚደርስ ሲሆን ለጉልበታቸው የሚመጣጠነው ዋጋ 12 ሺህ 500 ራንድ መሆኑን ገልጸው ነበር ፡፡

ታዲያ ምን ዋጋ አለው  ? ፓሊሶቹ ቀጥታ ወደ ሰራተኞቹ በመተኮስ የ 34 ሰዋችን ህይወት አጠፉ ፡፡ 78 ቱ ሲቆስሉ 259 ያህሉ እስር ቤት ተወረወሩ ፡፡ አማረብኝ ብለው ደግሞ ‹‹ የተኮስነው ራሳችንን ለመከላከል ነው ›› የሚል ምላሽ ሰጡ ፡፡ መከላከል እንዲህ ነው እንዴ ? ሲባሉ ‹‹ መጀመሪያ ውሃ፣ አስለቃሽ ጋዝና የመሳሰሉትን ተጠቅመን ነበር ›› ብለው እርፍ፡፡ እንደው መቼ ይሆን አፍሪካ ከእንደዚህ ዓይነቶቹ ማፈሪያ ፓሊሶች ተግባር የምትጸዳው  ? የአፍሪካ ፖሊሶች ዘወትር ስልጠና ወሰደን ይላሉ - ግን መቼ ይሆን ስልጠናው ህዝብን የማክበር ምዕራፍ ላይ የሚያደርሳቸው  ? የሰው ልጅ በተለመደው አልሰር፣ ስኳር ወይም ሌላ በሽታ ይጠቃል እንጂ እንዴት የማመዛዘን ክፍተት ሰለባ ይሆናል ፡፡ ለሀገር ክብር ሲፋለሙ ስለወደቁ የዓለማችን ጀግኖች ከመስማትና ከማንበብ ይልቅ እንዴት Made in ራሳችን በሚሉት የዱላና ጥይት ተረቶች ይበልጥ ይነቃቃሉ ?

በእውነት ተስፋ ያስቆርጣል ፡፡ አንዳንድ ሰልፈኞች ዱላ፣ ቆንጨራና ጦር ይዘው ቢታዩም እነዚህን የሚመክተውና  ጸጥ የሚያደርገው ጥይት ነው ብሎ ተመጣጣኝ ትርጉም መስጠት በእውነት ያሳፍራል ፡፡ ለነገሩ ጥቂት የማይባሉ የአፍሪካ ፖሊሶች
አትኩሮ ላያቸው - ወፍራም ስድብ
ሰው አገኘው ብሎ ለሚያስረዳው - ወፍራም ኩርኩም
የመንግስት ያለህ ብሎ ለሚጮኀው - ጥይት የሚያቅሙ ናቸው ፡፡

አሷፊ ፓርላማ፣ አጣሪ ኮሚቴ ወይም የእንባ ጠባቂ ድርጅት ድንገት ከጠየቃቸው ‹ በህጉ መሰረት ነው የሰራነው › ይላሉ ፡፡ ይህ መልስ እንግዲህ ሳያስፈቅድ የጮኀ ሌላ ትርጉም እስካልተሰጠው ድረስ ሞቱን በራሱ ግዜ የጠራ ፍጡር ነው ወደሚለው የቃላት መፍቻቸው የሚያደርሰን ይሆናል ፡፡ ይህን ዝነኛ ወታደራዊ መፍቻ መጨረሻውን አያለው ብላችሁ ከተጓዛችሁ ፖሊሶች ልክ እንደ ማዕረግ ሁሉ በአስተሳሰብም እንደሚከፋፈሉ ትረዳላችሁ ፡፡ በመሆኑም ይላል ቃላት መፍቻው  ‹ አንዳንድ ፖሊሶች ማለት ከጥይት የተሰሩ ጥቁር ድንጋዮች ናቸው ›  ፡፡ ይህ ነጻ ትርጉምማ መጨረሻው ሊሆን አይችልም በሚል ሌላ ‹ እንዴትን ? › ያነሳ ደግሞ በመጽሀፉ ማገባደጃ  ገጽ ላይ  ‹ ህልምና ቋንቋ እንደፈቺው ነው የሚባለው አባባል የዋዛ አይደለም ›  ከሚል ማጣቀሻ ጋር ይላተማል ፡፡

እና ተስፋ መቁረጥ ብቻ ሳይሆን አሳምረው መፍራት ይጀምራሉ ፡፡ የደቡብ አፍሪካ ፖሊሶች እየጮኀ እንጀራ የጠየቀውን ድሃ ሰራተኛ በላስቲክ ጥይት ቀጥ ማድረግ ይሳናቸው ነበር ?  ወደ ሰማይ መተኮስ ነው የሚቀድመው ወደ ሰው ?  ጥይቱን ወደ ሰማይ በመተኮስ ብቻ መበተን እንደሚቻል አያውቁም ወይስ አልፈለጉም ?

የደቡብ አፍሪካው የሩምታ ጭፍጨፋ የሀገራችንን አነጣጥሮ ገዳዮች አስታወሰኝ ፡፡ ምርጫ 97ትን ተከትሎ በኢትዮጽያ 193 ሰዋች በጥይት ሲሞቱ 763 ያህል ቆስለው ነበር ፡፡ በወቅቱ ጉዳዩን እንዲያጣራ የተሾመውና በአቶ ፍሬህይወት ሳሙኤል የሚመራው ቡድን   ‹ መንግስት ያልተመጣጠነ ርምጃ ወስዷል ! › በማለት ሪፖርቱን አቀረበ ፡፡ ቀደም ብሎም ሪፖርቱን እንዲያለሳልሱ በመንግስት ቢነገራቸውም ሰብዓዊና ፍትሃዊነት የሚሰማቸው ሰዋች ያባ ቢላዋ ልጅ ነን አሉ ፡፡ በርግጥ በሪፖርቱ አንስማማም ብለው ሸርተት ያሉ አባላትም ነበሩ ፡፡ ዞሮ ዞሮ ሪፖርቱ ‹ ተቃውሞ የሚበተንበት ቀላል አማራጭ የለም እንዴ ?  የፖሊስ አመለካከትስ ለምንድነው የማይቀየረው ? › የሚል አሽሟጣጭ አስተያት አቅርቦ ነበር ፡፡

የኛን ሪፖርት ለደቡብ አፍሪካዊያን አስቀድመን በግልባጭ ብናሳውቅ ኖሮ ምን ያህል በጠቀማቸው ፡፡ ለነገሩ አርቃችሁ ቅበሩኝ ያለ ስርዓት እንደ እባብ አፈር ልሶ ይነሳል ብሎ የገመተ ማን አለ ? በጅምላው የእኛን ጨምሮ የአፍሪካ ፖሊሶች የአመለካከት ችግር ካልተቀየረ ነገና ከነገ ወዲያም የሌሶቶውን ጭፍጨፋ ሃትሪክ ለማድረስ የሚሯሯጡ ጭፍኖች ይፈጠራሉ  ለማለት ያስደፍራል ፡፡ ጭንቅላታቸው ውስጥ የተጠራቀመውን  አለቃ ! ታዘዝ ! ጥይት ! ተኩስ ! ግደል ! አቁስል ! ወዘተ የተሰኙ መራራና የታሸጉ ቃላቶችን ገላልጠው መፈተሸ ይኖርባቸዋል ፡፡ ህዝብ ! ሰብዓዊ ክብር ! ርህራሄ ! ወገን ! ድሃ ! ለምን ! የሚሉ ሃሳቦችን ከመራራዋቹ ጋር ማዋሃድ ባይችሉ እንኳን እንደ ኮዳ ወይም ጥይት ማስቀመጫቸው ከቻሉ ጭንቅላታቸው ውስጥ ካልቻሉ ወገባቸው ላይ አንጠልጥለው መዞር ይጠበቅባቸዋል ፡፡ ‹ በለው ! ግደል ! › የሚል አረመኔ አለቃ ቢያጋጥም እንኳ ሀሳቦቹ ‹ ለምን ! ወገንህን ! › ብሎ ያስታውሳቸዋልና ፡፡

ለማንዴላና ለእውነተኛ ታጋዮቹ በንጹሀን ላይ የደረሰው ፍጅት ሰቆቃ ይፈጥራል ፡፡ እርጅና ተጫጭኗቸው በገጠር ሰፈራቸው የሚኖሩት ማንዴላ ስልጣናቸውን ሲያስረክቡ የመጨረሻ ንግግራቸውን በም/ቤቱ ውስጥ እንደሚከተለው ተናግረው ነበር ‹‹ የህገ መንግስታችን የመርሁ ምንጭ የሰው ልጆች ክብር ላይ የተመሰረተ ነው ፡፡ የሰው ልጅ ክብር መልካምነት ላይ መስማማት ይኖርብናል ፡፡ ታሪካዊ ባላንጣችን ከነበረው አፓርታይድ ወደ ዴሞክራሲ ያደረግነውን ሰላማዊ ሽግግር የተቀበልነው ለሰው ልጆች ካለን መልካምነትና ይህንኑ ማግኘት ከሚገባው ተገቢነት አኳያ ነው ፡፡ ዴሞክራሲያችን ለሁሉም በጎ ፍሬ ማምጣት ይኖርበታል ፡፡ በተለይም ለድሆችና ትኩረት አጥተው ለቆዩት ››

ይህ አደራ ለዚያውም ሰላማዊ በተባለው ዘመን በአይጠ መጎጦች ተበልቷል ፡፡ የፍቅር፣ ርህራሄና ነጻነት ካባ የደረቡት ማንዴላ በድርጊቱ ምን ያህል እንደሚጎዱ ማሰብ ከባድ አይሆንም ፡፡ Long Walk to Freedom በተባለው መጽሀፋቸው ‹‹ ረጅም ጎዳና የተጓዝኩት ነጻነትን ለማግኘት ነው ፡፡ ብዙ ተጨባጭ ውጤቶችን አግኝተናል ፤ አሁን ያረፍኩት ለግዜው ነው ፡፡ ረጅም ጉዞዬ ግን ገና አልተጠናቀቀም ›› ብለው ነበር ፡፡
 

የሚገርም ትንቢት ተናግረዋል ፡፡ በፍቅር፣ በፍትህና በአድልዋ ላይ የሚደረገው ጉዞ ገና የተጠናቀቀ አይመስልም ፡፡ አዝኛለሁ በማለት ምርመራ እንዲደረግ ያዘዙት ጃኮብ ዙማ አዲስ ትንሳኤ ያስገኛሉ ወይስ አፈሩን አርግፎ ራቁትን በከተማው ዳር ለቆመው አፓርታይድ ጂንስና ካፖርት ያቀብላሉ ?

Friday, August 10, 2012

‎የጀግና መንገድ‎



ኒክ ከባለቤቱ ጋር


--- እጅም እግርም የለውም ፤ ግን የዓለማችን ደስተኛ ሰው ነው ፡፡
--- እጅና እግር አለን ፤ ግን የዓለማችን ሀዘንተኛ ህዝቦች ነን ፡፡
--- < life is greater purpose > በሚል ርዕስ መጽሀፍ አሳትሟል ፡፡
--- < life is knife ! > የሚል ሰፊ ሀሳብ ውስጣችን ቢከማችም ‹ ሆድ ይፍጀው ›  ብለን ለህትመት አላበቃነውም ፡፡

ተቃርኗችን ቢዘረዘር ሰፊ ነው ፡፡ በርግጥ እሱ በአንድ ወቅት እጅግ ተከፍቶና ተስፋ ቆርጦ ራሱን ለማጥፋት ሙከራ አድርጓል ፡፡ ጥያቄውና ጸሎቱ አንድ ነበር ፡፡ ‹ እጅና እግር ስጠኝ › የሚል ፡፡ ሰሚ ባለማግኝቱ በጣም ተከፋ ፡፡ እናም በዚህ የሚደርስበትን ሙከራ መቋቋምና መታገስ ባለመቻሉ ድርጊቱን ፈጸመ ፡፡

ለኛ ተስፋ መቁረጥና መከፋት ብርቅ አይደለም ፡፡ አንዱ ጥያቄ ሳያድግ በላዩ ላይ ሌላ ጥያቄ ስለሚረገዝ የጥያቄዋቻችን ብዛት እንደ ህዝብ ብዛታችን አስጊ ደረጃ ላይ የደረሱ ናቸው ፡፡ ጥያቄዋቻችን ብዙ ህጻናት እንደሚያሳድጉ ቤተሰቦች አእምሯችን ውስጥ ያለ ስርዓት ይንጫጫሉ ፡፡ አእምሯችን ሰላም፣ ፍቅር፣ ፍትህ፣ ነጻነት፣ እንጀራ ወዘተ እያለ ዘወትር ይጠይቃል ፡፡ ከጥያቄዋቻችን መላመድ የተነሳ ነው መሰለኝ ጥያቄዋቹን እንደ ቤት ቁጥር ወይም ታርጋ ከማንነታችን ጋር ለጥፈናቸዋል ፡፡ እንጀራ የሚል ስም አልሰማሁም እንጂ ሰላም ፣ ፍቅር፣ ፍትህና ነጻነት የተባሉ ሰዋች በሺዋች የሚቆጠሩ ናቸው ፡፡ እንዴት ሊሆን ቻለ ? በተጨባጭ ያጣናቸውን ጉዳዮች በምኞት ወይም በመምሰል ለማካካስ ይሆን ? ላይሆንም ይችላል ፡፡

ለማንኛውም ስማቸውን ሳይሆን ከጀርባ ያለውን ማንነት ጠይቀው ምላሽ ያላገኙ ሰዋች መከፋታቸው ይጠበቃል ፡፡ መታገስ ያልቻሉት ውድ ህይወታቸውን በበረኪና፣ በገመድ፣ በጥይትና በመሳሰሉት ለማጥፋት ፈትነውታል ፡፡ ብዙዋች የጥያቄዋቻቸውን ግልባጭ ጆሮ ላለው ለማድረስ ከኬንያ እስከ አሜሪካ ድረስ ተበትነዋል ፡፡ በርግጥ በስደት ህይወት በቂ ምላሽ ያገኙ የታደሉና የተቀደሱ መሆን አለባቸው ፡፡ እስራኤላዊያን ግብጽ ውስጥ ለአያሌ አመታት ኖረው በተፈቀደው ግዜ መመለሳቸውን ያስታውሷልና ፡፡ ጥያቄውን ለሚመለከተው ሁሉ ያላለው የኔ ቤጤ ደግሞ ይሐው በርካታ የእህህ … ክላሲካሎችን እየደረሰ ይገኛል ፡፡ ድምጽ ሳይሆን በቂ ድፍረት ያላቸው ቢያንስ የአይዶል ውድድር ላይ
        ‹‹ እህህ ጠዋት ማታ ዋውዬ
           እህህ ሌሊት ዋውዬ  …. ›› እያሉ ይገኛሉ ፡፡ ‹ ተመስገን › የተሰኘውን ልማዳዊ መዝሙር ጠዋትና ማታ በማቀንቀን የሚታወቁት ቡድኖች ደግሞ  ‹ እነ ፍቅርና ነጻነት › በተሰኙት ስሞች እየተጽናኑ ይመስላል ፡፡

ግን ከባድ ነው ፡፡

በጦርነት ታምሶ የቆየ ቀጠናን እንጂ በጥያቄ የተወጣጠረ አእምሮን በ ‹ ማረጋጋት › መስመር ማስያዝ ይከብዳል ፡፡ በርግጥ ብርቅዬውን ‹ ደስታ › አሁንም በስም መልክ ካልሆነ በተግባር እንዴት መገብየት ይቻላል ? ተስፋ መቁረጥን እንዴት ማከም ይቻላል ?

አዋ ከባድ ነው ፤ በመሆኑም የፈጣሪ ብቻ ሳይሆን የኒክ መንገድም ሳያስፈልገን አይቀርም ፡፡
ቢቻል በአካል ልንጨብጠው ካልሆነ መንፈሱን ልንሞቀው ሳይገባ አይቀርም ፡፡   

እሱ ነው እንደ አማዞን ደን የረዘመውንና የገዘፈውን ተስፋ መቁረጥ ከርክሞ የበረንዳ አበባ ያደረገው ፡፡ እሱ ነው በክፋትና በፌዝ ያበጡ ቦርጮችን አስተንፍሶ የቅርጽ ተወዳዳሪ ያደረጋቸው ፡፡ እሱ ነው የጨካኞችን የደነደነ ልብ ሞርዶ ከውስጣቸው ከርሰ ምድር የሩህሩህነትን እንባ ማፍለቅ እንደሚችሉ እያለቀሱ እንዲያረጋግጡ ያደረገው ፡፡

እሱ ማነው ?

ሙሉ ስሙ ኒኮላስ ጀምስ ቩጂክ ሲሆን ብዙዋቹ የሚጠሩት ኒክ እያሉ ነው ፡፡ ታፍሳስ 4 ቀን 1982 በአውስትራሊያ ሆስፒታል ውስጥ ሲወለድ እጆችና እግሮች እንደሌሉት ታወቀ ፡፡ ወላጆቹ ጤነኛ በመሆናቸው ይህን ክስተት መቀበል አልቻሉም ፡፡ እንዴት ይበላል ? እንዴት ይራመዳል ? እንዴት ይሮጣል ? እንዴት ይማራል ? እንዴት ይጫወታል ? እረ እንዴት ሆኖ እንዴት ይሆናል ?  እናትና አባት ጥያቄዋቹን እያነሱ ምላሽ ሲያጡ ይንሰቀሰቃሉ ፡፡ ሰማይ ምድር ተደፋባቸው ፡፡

ዕድሜው ለትምህርት ሲደርስ ከትልቅ ችግር ጋር መጋጨት ጀመሩ ፡፡ በአውስትራሊያ ህግ አካል ጉዳተኛ መደበኛው ት/ቤት ውስጥ ገብቶ መማር አይችልም  ፡፡ ቤተሰቦቹ ሳያቋርጡ ‹ የመብት ያለህ ! › እያሉ በመጮሃቸው ግን ህጉ ሊሻሻል ቻለ ፡፡ ኒክም የመጀመሪያው አካል ጉዳተኛ ተማሪ ሆኖ ተመዘገበ ፡፡ እንደ ልጆቹ ወንበር ላይ ሳይሆን ከፍ ያለ ጠረጼዛ ላይ ቁጭ ብሎ ልጥፍ ግራ እግሩ ላይ ባሉት ጣቶች እየታገዘ መጻፍ ለመደ ፡፡

ትንሽ ከፍ እያለ ሲመጣ ግን ከውጪውና ከውስጡ የሚደርስቡትን ጥያቄዋችና ተጽዕኖዋች መቋቋም አልቻለም ፡፡ እኔ እንዴት ከሌሎቹ ልጆች በተለየ መልኩ ተፈጠርኩ ? ለምን የሰዋች መጠቋቋሚያና መሳለቂያ ሆንኩ ? ማለት ጀመረ ፡፡ በብቸኝነትና በመገለል ቆሰለ ፡፡ ስምንት ዓመት ሲሞላው ራሱን ስለማጥፋት ማንሰላሰል የጀመረበት ግዜ ነበር ፡፡ ቢቸግረው በልጅነት ልቡ ‹‹ አምላኬ ለኔም እጅና እግር ስጠኝ ?  ›› በማለት ዘወትር በማልቀስ ይለምን ጀመር ፡፡ ሰሚ አልነበረውም ፡፡ አስር አመት ሲሞላው ራሱን ውሃ ውስጥ አስምጦ  ለመግደል ሙከራ አደረገ ፡፡ ይሁንና በቤተሰቦቹ ጥረት ከሸፈ ፡፡ በአንድ ወቅት እናቱ አንድ አካል ጉዳተኛ እንዴት ህይወቱን እየመራ እንደሚገኝ የሚተርክ ጋዜጣ በማሳየት ታሪኩን አነበበችለት ፡፡ ይህ ታሪክ በዓለም ላይ ያለው አካለ ጉዳተኛ እሱ ብቻ አለመሆኑን አስገነዘበው ፡፡ ቀስ በቀስም እጅና እግር ያላቸው ልጆች የሚያደርጉትን ነገሮች በሙሉ ያለማንም አጋዥነት ማከናወን እንዳለበት በማመን ልምምዶችንና ጥረቶችን ቀጠለ ፡፡

ውጤቱ አስገራሚ ሆነ ፡፡ ጥርሶቹን ማጽዳት፣ ጸጉሮቹን ማበጠር፣ በኮምፒውተር መጻፍ ፣ መዋኘት ፣ ቴኒስ መጫወት፣ ሰልክ ማናገርና ሌሎችንም ያለ እጆችና እግሮች ማከናወን ቻለ ፡፡ ይህም እንደ ተረገመ ፍጥረት ሲመለከቱት የነበሩ ተማሪዋች አሁን እንደ መልዓክ እንዲመለከቱት አስቻለው ፡፡

 
ኒክ በአካውንቲንግና በፋይናንሻል ፕላኒንግ ሁለት ዲግሪዋችን ከያዘ በኃላ በ19 ዓመቱ የህይወቱን ውጣውረድ ለሌሎች የሚያካፍልበት የንግግር መድረኮችን ማዘጋጀት ጀመረ ፡፡ ለዚህ ይረዳው ዘንድም  life with out limbs  የተባለ አትራፊ ያልሆነ ድርጅት አቋቋመ ፡፡ ዛሬ በት/ቤቶች፣ በእምነት ተቋማት ፣ በድርጅቶች፣ በወላጅ አልባ ህጻናት ማሳደጊያዋች፣ በእስር ቤቶች፣ በሆስፒታሎችና በስታዲየሞች እየተገኘ ህይወቱንና ልምዱን በመሳጭ የንግግር ችሎታው ያካፍላል ፡፡ በአፍሪካ፣ ኤሽያ፣ ሰሜን አሜሪካ በሚገኙ ሃያ ሀገራት እየተዟዟረ አስተምሯል ፡፡

ኒክ የህይወትን ቀፋፊ ጎኖች በማሸነፍ የላቁ ሜዳሊያዋችን በየግዜው አጥልቋል ፡፡ በ2005 የአውስትራሊያን የዓመቱ ወጣቶች ሽልማት ያገኘ ሲሆን የራሱን ህይወትና እንቅስቃሴ የሚያሳይ የዲቪዲ ፊልም life is greater purpose በሚል ርዕስ ሰርቶ አሰራጭቷል ፡፡ በ2009   < No arms , No legs , No worries > የሚል መጽሀፍ ከማሳተሙ በተጨማሪ < The Butterfly Circus > በሚል ርዕስ በሰራው ፊልም በአጭር ፊልም የምርጥ አክተር ሽልማት ተቀብሎበታል ፡፡ < Some thing more > የሚል ሙዚቃም  ለቋል ፡፡ የካቲት 12 ቀን 2012 ካኔ ሚያራን የተባለች ቆንጆ አግብቶ ህይወቱን በመምራት ላይ ይገኛል ፡፡

‹‹  ፈጣሪን እጅና እግር በተዓምር ስጠኝ እያልኩ እንደዛ ስለምነው ቢሰጠኝ ኖሮ እንደማንኛውም ሰው የተለመደ ህይወት ነበር የምኖረው ፡፡  በወቅቱ ተዓምር ላገኝ አልቻልኩም ፤ አሁን ስረዳው ግን ለካስ ራሴ ተዓምር ነበርኩ ››  በማለት አድማጮቹን በሳቅ ያፈርሳል ፡፡

እንግዲህ የሰው ፍቅርን፣ ፍትህን፣ የህሊና ነጻነትና ሰላምን ሲመኝ የነበረው ኒክ ማለት ይህ ነው ፡፡
ሰው በስድቡ፣ ንቀቱና ማግለሉ ‹ ንክ › ይሆናል ብሎ ሲጠብቀው ‹ ልባቸው እንዲነካ › ያደረገው ኒክ ይህ ነው ፡፡
ያጣውን ሰላም ፣ ፍቅርና ነጻነት በራሱ የጀግና መንገድ የፈታው ኒክ ይህ ነው ፡፡
እንግዲህ ፍቅር፣ ሰላም፣ ነጻነት፣ ፍትህና እንጀራ የምንለምነው ‹‹ እኛም ›› ይኀው አለን ፡፡

ተቆጥረው የማያልቁት ችግሮቻችን እንደ ኩይሳ አድገው ጫፉ ላይ የታሰረው ሰንደቅ ከኩራት ይልቅ ተስፋ መቁረጥን እያውለበለበ ነው ፡፡ ይህ የኩይሳ ምሶሶ እየደነደነ ይሄድ ወይስ ይገርሰስ ? የሚለው መሰረታዊ ጥያቄ የመኖር ወይም ያለመኖር ምርጫ መሆኑ አያከራከርም ፡፡ እንዴት ?  ለሚለው ጥያቄ ነው እንግዲህ የጀግና መንገድ ያስፈልገናል የሚባለው ፡፡




Sunday, July 22, 2012

‎ጠ/ሚ/ር መለስ ሲመለሱ ….‎



መቼም ዓለም የተቃርኖ ሙሌት ናት፡፡ ብርሃን ስንል ጨለማ፣ ሰማይ ስንል ምድር፣ ጎፈር ስንል ዘውድ፣ ደስታ ስንል ሀዘን፣ ህይወት ስንል ሞት የሚባሉት የቁርጥ ቀን አዛማጆች በአእምሮአችን ሳይጠሩ ከተፍ ይላሉ ፡፡

ከዚህ እውነት አንወጣም ፡፡

እንደሚታወቀው ጠ/ሚ/ር መለስ ዜናዊ ታመው ህክምና በመከታተል ላይ ናቸው ፡፡ እሳቸው ባይናገሩም ሌሎች ግን ስለሳቸው ከላይ በተገለጸው እውነት መሰረት ሀሳባቸውን ይሰነዝራሉ ፡፡ የመንግስት ኃላፊዋች ድነው ይመለሳሉ ሲሉ ሌላው ህመሙ አስጊ ስለሆነ አይተርፉም ይላል፡፡ ክርክሩ ይጡዝ እንጂ ነባራዊውን እውነት የሚዳኘው ፈጣሪ ነው፡፡ አሁንም አንዳንዶች ወሳኙ ሀኪሞች ናቸው ሊሉ ይችላሉ፡፡ ምክንያቱም ሁለቱ ጫፎች መሳሳብ ስላለባቸው ፡፡ ሁለቱ ጫፎች ለስነፍጥረትም ሆነ ለቴክኖሎጂው መሰረት መሆናቸውም ይታወቃል ፡፡

እኔም ሁለቱን ጫፍ ተንተርሼ በአቶ መለስ ዙሪያ ወግ ለመሰለቅ አሰብኩ ፡፡ አቶ መለስ ድነው ቢመለሱና አያድርግባቸውና አቶ መለስ ቢያርፉ በሚሉት ሀሳቦች ላይ ፡፡ ቆይቼ ሳስበው ‹ ቢያርፉ › የሚለው ሀሳብ ከይሲ ሆኖ ተሰማኝ ፡፡ ደግሞስ እኔ ማነኝና ይህን ለማወቅም ሆነ ለመገመት ስልጣን የተሰጠኝ ፡፡ ደግሞስ ግዜው ነው ወይ ? ሲል ውስጤ ሞገተኝ ፡፡ ስለዚህ ቀናውን ሞፈር ጨብጬ የወግ ማሳዬን መተርተር እንደሚሻል ወሰንኩ ፡፡

እነሆ ከጎፈር ዘውድን መረጥኩ / ስልጣን ስለሆነ / ፤ እነሆ ከሰማይ ምድርን ሻትኩ / መቼትን ስላስታወስኩ / ፤ እነሆ ከሞት ህይወትን ጠራሁ ፡፡ እናም አቶ መለስ በህይወት ሲመለሱ ምን ያደርጋሉ ? ምን እንሰማለን ? የሚሉ ምናባዊ ትንታኔዋችን እያነሳሁ እጥላለሁ ፡፡

ምዕራፍ አንድ የሚጀምረው አውሮፕላን ውስጥ ነውና አቶ መለስ በኢትዮጽያ አየር መንገድ ወደ አዲስ አበባ እየተመለሱ ነው፡፡ ሻምፓኝ ተከፍቶ እየተጠጣ ነው ፡፡ ጎምቱ ባለስልጣናት መለስን ከበው በማያስቀው ሁሉ ይስቃሉ ፡፡ አራት ቦታ የተቆረጠው ኬክ ገና አልታደለም ፡፡ በእያንዳንዱ ቁራጭ ላይ የሰፈሩት ጽሁፎች ሲገጣጠሙ ‹‹ ረጅም ዕድሜ ለመለስ ›› የሚል መልዕክት ያስተላልፋሉ ፡፡

ሲፈራ ሲቸር የቆየው የቴሌቪዥን ጋዜጠኛ ማይኩን ይዞ ወደ አቶ መለስ ጠጋ ሲል የሚያውካኩ ድምጾች መጥፋት ጀመሩ ፡፡
‹‹ እንኳን ለዚህ አበቃዋት ጠ/ሚ/ር ››
‹‹ አመሰግናለሁ ! ››

የጋዜጠኛው ድምጽ ባይሰማም  የሆነ ጥያቄ ወረወረ፡፡ ያው ከመልሱ እናገኘው የለ ?! መልሱም ተከተለ ፡፡

1 . እንደሚገባኝ የመታከሙ ተልዕኮ የተሳካ ነበር ማለት ይቻለል፡፡ ይህን አባባል በሶስት መልኩ መንዝሮ ማብራራት የተሻለ ሳይሆን አይቀርም ፡፡ ቁልፉና ማጠንጠኛው አንድ ሰው በተለይም አንድ የሀገር መሪ ታሞ መዳን መቻሉ ነው ፡፡ ይህን የመዳን ጥያቄ ደግሞ ጠንካራ የሚያደርገው የታማሚው መሪ ግለኛ ፍላጎት ብቻ ሳይሆን የታማሚውን መጨረሻ የሚጠብቁ ብዙ ሚሊዮን አይኖች መኖራቸው ነው ፡፡ ርግጥ ነው 90 ከመቶ ያህሉ ይህ በሽተኛ መሪ እንዲድን ለሚቀርበው ፈጣሪም ሆነ ጣዖት መለማመኑ ይጠበቃል ፡፡ አስር ከመቶው ግን ከቁጥሩ በላይ ያበጠ ፍላጎት እንደነበረው አምናለሁ ፡፡ በጣም የሚገርመው በዚሁ አሃዝ ውስጥ የሚካተተው ጥቂት ማህበረሰብ የሚናገረው ርግጠኛ የመሆኑ ጉዳይ ላይ ነው  ፡፡

ለምሳሌ ያህል  ‹ መለስ ከዳነ ከምላሴ ጸጉር ይነቀል › ብሎ ይነሳል ፡፡ በርግጠኝነት የሚያወራው ሞቱን ብቻ ሳይሆን የሕመሙንም መንስኤ ነው ፡፡ የያዘው የጭንቅላት ዕጢ የሚያፈነዳው እንጂ ለቀዶ ጥገና የሚመች አይደለም ብሎ ይደመድማል ፡፡ ወይ በሌላ ገጹ በድብቅ ያበሉት መርዝ ለጥቂት ግዜ ብቻ ነው የሚያላውሰው እንደሚል አይጠረጠርም ፡፡ ስለሆነም ጥቂቶች ካወሩት ሚሊዮን አሉባልታና ሚሊዮን ክፉ ምኞት አንጻር ህክምናው የተሳካ ነበር ለማለት ያስደፍራል ፡፡

በሁለተኛ ደረጃ መታየት ያለበት እኔን ሲያክሙና ሲንከባከቡ ከነበሩ ዶክተሮች አንጻር የሚተነተን ነው ፡፡ እንደምታውቀው መሪዋች ሲታከሙ ለማዳን የሚኖረውን ከፍተኛ ጥንቃቄ ያህል ከውስጥ በጣም ያረገዘ ነገር ግን የማይታይ ስጋት ይኖራል ፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች የተጠራቀመው ስጋት የሚጫነው ደግሞ ሀኪሞች ላይ ነው ፡፡ ሀኪሞች ሌላ ዓላማ ላነገቡ ሰዋች፣ ቡድኖች ወይም መንግስታት ማለት ይቻላል ተገዢ ወይም ተንበርካኪ ባይሆኑ እንኳን ኃላፊነታቸው በራሱ ስጋት ላይ ሊጥላቸው ይችላል፡፡ ከስጋትም አልፎ በጥቂት ነገር ሊሳሳቱ ይችላሉ ፡፡ ከተሳሳቱ ደግሞ ተበላሸህ ነው ፡፡ አለቀ ፡፡ ዛሬ ኤሪያል ሻሮን፣ ሙባረክና ሌሎች መሪዋች ምን ያህል ኮማ ውስጥ እንወደቁ ማየት ይቻላል ፡፡ እና ህክምናው ውስጥ ያለውን ጦርነት በድል ከመወጣት አንፃር ተልዕኮው የተሳካ ነበር ማለት እችላለሁ ፡፡

በሶስተኛ ደረጃ መቀመጥ ያለበት የተሞክሮ ቅመራ ወይም የቴክኖሎጂ ሽግግር ሂደት ነው ፡፡ የታከምኩበት ሀገር የምታራምደው ርዕዮት ምንም ይሁን ምን በህክምና ዘርፍ የደረሰችበት ደረጃ ከፍተኛ ነው ፡፡ ይህን ቴክኖሎጂ ወደ ሀገራችን እንዲገባ በማድረግ ተሞክሮውን በማጥናትና በመቀመር ማስፋፋት ይኖርብናል ፡፡ ይህን በማድረጋችን ለህክምና የምናወጣውን ከፍተኛ የውጪ ምንዛሬ ማዳን ይቻላል ፡፡ በሁለተኛ ደረጃ በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን የያዝነውን ዕቅድ ተግባራዊ ለማድረግ ተጨማሪ ምርኩዝ ይሆንልናል ፡፡

2. ጠ/ሚ/ር መለስ ቤተመንግስት ከገቡ በኃላ ከእንደገና በነገሮችና በሁኔታዋች ሊወጠሩ እንደሚችሉ ይገመታል ፡፡ የመጀመሪያ ተግባራቸው በየደረጃው መግለጫዋችን መስጠት ይሆናል ፡፡

ሀ . ለህዝብ ፤

አቶ መለስ ህዝቡ በሃሳብም ሆነ በጸሎት ላደረገላቸው ድጋፍ ከፍተኛ ምስጋና ያቀርባሉ የሚለውን እንደ አርእስተ ዜና እንውሰደው ፡፡ ድርጅቱ መራራውን የትጥቅ ትግል ሲያደርግ ከጎን እንደነበር ፣ ሰላም ሰፍኖ የልማት ግንባታው ከቀጠለ በኃላም አለኝታነቱን እንዳረጋገጠ ወደፊትም የኩሩውንና የቀናኢውን ህዝብ ድጋፍ እንደማይለያቸው አስረግጠው መናገራቸውን ደግሞ ርዕሱን የሚያፍታታው ዝርዝር ሃሳብ ይሆናል ፡፡ ምክንያቱም ብዙ ጅምሮች አሉና፡፡ ቢያንስ የአባይ ግድብ ማለቅ አለበት ፡፡ ቢያንስ ህዝቡ በቀን ሶስት ግዜ መብላት አለበት ፡፡ ስለዚህ ህዝቡ መሪውን  አሳፍሮ እንደማያውቅ የታሪክን ሰበዝ በማውጣት ንግግራቸውን ሊያጠናክሩት ይችላሉ ፡፡ ይህ ደግሞ የኃላ ታሪክ / Background / መሆኑ ነው ፡፡ ማለትም የአጼ ዮሀንስ  ‹ ሀገርህ እናትህ፣ ዘውድህ፣ ሚስትህ…  › የሚለው ገዳይ ጥቅስ የተዘጉ ልቦች ዳር እንዲንኳኳ ይደረጋል ፡፡ በሌላ በኩል የአጼ ሚኒሊክ ‹ ጉልበት ያለህ በጉልበት ርዳኝ … › የምትለው ትሁት ስንኝ ይጨመርበታል ፡፡ በላዩ ላይ ወርቅ የመሳሰሉ አዳዲስ መፈክሮች ጣል ይደረግበታል ‹‹ ጸረ ህዝብም ሆኑ ጸረ ጤንነቶች ከመንገዳችን አያደናቅፉንም ! ››

ለ . ለፓርቲ አባላት ፤

ጠንካራ ሀሳቦችና ጉዳዮች የሚመዘዙት በዚህ ክፍለ ግዜ እንደሚሆን ይጠበቃል ፡፡ ስብሰባውን ፈታ ለማድረግ በ ‹‹ ሞት ›› ላይ አንድ ሁለት ቀልዶችን ወርወር ማድረግ ማን ይከለክላቸዋል ፡፡ አሁን የታየው ውጥረት ከኢትዮ- ኤርትራ ጦርነት፣ ከህወኃት ክፍፍልና ከ97ቱ ምርጫ ቀጥሎ ሊቀመጥ የሚችል የፈተና ምዕራፍ በመሆኑ ትልቅ የጠቆረ ቦታ ይኖረዋል ፡፡ በመሆኑም በህወኃት ክፍፍል ግዜ የተባለውን ቁም ነገር በማስታወስ ‹‹ ሞት ለምሳ ሲያስበን ለቁርስ አድርገነዋል ›› ሊሉ ይችላሉ ፡፡ ካስፈለገ ደግሞ ከኢትዮ ኤርትራ ጦርነት የትዝታ ኮሮጆ ውስጥ የጄኔራል ሳሞራን ብሂል በማውጣት

 ‹‹ በሽታ አካልን ማገርጣትና ማሰቃየት ይችልበታል ፤
እኛ ደግሞ ሰንኮፉን በጽናት አስነቅለን ቆመን መሄድ እንችላለን ›› ቢሉ ወፈ ሰማይ ካድሬ እስከ ሻይ እረፍት አይስቅም ብሎ መከራከር አያዋጣም ፡፡ በርግጥ ሁሌም የሚጠራጠሩ አንዳንድ ሰዋች ከቀልዱ ጀርባ ምን ተደግሷል በሚል በመተርጎምና በመተንተን ቀኑን ሊያሳልፉት ይችላሉ ፡፡  ‹ በርግጥ ለምሳ ያሰቡ እነማን ናቸው ? …. ሰንኮፎቹስ ?  .. ›

አቶ መለስ በነካ እጃቸው ሰምና ወርቅ ያለው ምስጋና በማቅረብ የቤቱን ሙቀት ሊያግሉት ይችላሉ ፡፡ ‹‹ እዛ ድረስ መጥተው የጠየቁኝ የቁርጥ ቀን ወዳጆቼ አሉ ፡፡ ይህ ማለት ግን በስራ መብዛት ወይም የአውሮፕላን ወጪ በማጣት ያልመጡ ጓዶች ሁሉ እኔን አልጠየቁኝም ወይም ለእኔ አያስቡም ማለት አይደለም ! ››

‹ እዛ ድረስ ሄደው የጠየቁት በርግጥ አባካኝ ናቸው ወይስ የቁርጥ ቀን ልጆች ? አሁን ማን ይሙት የአውሮፕላን ወጪ የሚከብደው ኃላፊ የቱ ነው ? ጉድ ነው ይሄ ነገር ! … › ሌላ ምናባዊ ሀሳቦች ይፈለፈላሉ ፡፡ ይህን መሰል ፍም በራሱ ፓለቲካ ሰፈር ውስጥ መለኮስና እንዳይጠፋም በአባላቱ ምላስ እንዲርገበገብ ማድረግ ጠቃሚ ነው ፡፡ አስፈላጊ ከሆነ ተርከክ ያለው ፍም ላይ ‹ በቆሎ › ይጠበስበታል ፡፡ በቆሎ ከጠፋ እንኳን ሰብሰብ ብለው ወይ ተረት ወይ ትዝታን እያወሩ ይሞቁታል ፡፡

3 . የወ/ሮ አዜብ መስፍን ሹፌር ቤተመንግስት አካባቢ በተነሳው የስልጣን ሹክቻ በመስጋት በቱርክ አድርጎ ግሪክ መግባቱን አንዳንድ የመገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል ፡፡ ይህ ወሬ እውነት ከሆነ አቶ መለስ በቀጣይነት ለሚንደረደሩበት ርዕሰ ሀሳብ ጥሩ መረጃ ይሆናል ፡፡ ዜናው እውነት ካልሆነ ወደ ርዕሰ ጉዳዩ የሚያሰገባው መንገድ የተለየ መሆኑን ልብ ይሏል ፡፡ እናም አቶ መለስ የሾፌሩን ስም ጠርተው  ‹ ምን መሆኑ ነው ግን ? የኛ የስልጣን ሹክቻ የሚያሰጋው እሱ ባለስልጣን ነው እንዴ ? › የሚል ጥያቄ ወርወር ያደርጋሉ ፡፡ ወዲያው ደግሞ  ‹‹ የዚያች የጥንቸሏ ብጤ መሆኑ ነው ?!  ነብር ነው ዝሆን እየታደነ ይያዝ ሲባል እሷ እግሬ አውጪኝ ትላለች ፡፡ እንስሳትም ምን ሆነሽ ነው የምትፈረጥጪው ?  አዋጁ እንደሆነ አንቺን አይመለከትም ሲሏት ዝሆን አለመሆኔ እስኪረጋገጥ ለምን ፍዳዬን አያለሁ ነበር ያለችው ! ›› በማለት ላነሱት ጥያቄ ማብራሪያ ይሰጣሉ ፡፡ አቶ መለስ ፊታቸውን ከስከስ አድርገው ይቀጥላሉ ፡፡

‹‹ በርግጥ ሰው ወጣ ሲል የሰው በር ለማንኳኳት የቋመጡ ሰዋች እንደነበሩ ተሰምቷል ፡፡ የዉጪዋቹስ መቼም ግርግር ለሌባ ይመቻል ! የሚባለውን ብሂል አሁን ነው መጠቀም ያለብን ለማለት ነው ፡፡ በጣም የሚገርመው የቤታችን ጉድ ነው ! አንዳንዱ የተሰጠውን ስራ አድምቶ ሳይሰራ ነው ወደ ላይ መንጠልጠል የፈለገው ፡፡ አንዳንዱ ደግሞ ተገፍቶና ባዶ ተስፋ ተሸክሞ ነው ››

ከዚህ በኃላ የደፈረሰው ይጠራ ዘንድ፣ ለአቅመ ጠላ ያልደረሰው መጠጥ መቼ፣ እንዴትና በነማን እንደተጠነሰሰ ይታወቅ ዘንድ ተከታታይ ሂስና ግለሂሶች ይካሄዳሉ ፡፡ በመሃሉ የሚፈረጥጡ ጥንቸሎችም አይጠፉም ፡፡ ነገሩ ሀገሪቱ ውስጥ እንደሚወራው ጠንካራ ከሆነ ድርጅቱ ለፓለቲካ ጸበል ሁለት -  ሰባት  ‹ ሸንኮራ › መውረዱ አይቀርም ፡፡

እንግዲህ ይህ ሲያልቅ ነው አዳዲስ ነገሮች የሚፈልቁት ፡፡  በመጀመሪያ መግለጫው ፤

. ‹ ከናፋቂነት ተፈወስን ! › የሚል ሀሳብ ላይ ይሽከረከር ይሆናል ፡፡ ከዚህ በፊት ጠባቂነት፣ ተሃድሶ፣ መበስበስ ወዘተ የሚሉ ምጡቅ መግለጫዋች ስለነበሩ እንዳይደገሙ ጥንቃቄ ስለሚደረግ ማለት ነው ፡፡

. ውስጥ ለውስጥም ሆነ ይፋ በሆነ መግለጫ ሹም ሽሮች ሊከናወኑ ይችላሉ ፡፡ በሹም ሽሩ ከዚህ ቀደም በአቅም ማነስና በእጅ አመል ቀንዳቸውን የተመቱ ሁሉ አሁን የኤሊን ገጸ ባህሪ ወክለው ይጫወታሉ ፡፡

. የከፋ ነገር የተገኘባቸው / ለአብዮቱ ያልተመቹ / ደግሞ ፈጽሞ አልመው ወደማያውቁት የቃሊቲ ዓለም ይወረወራሉ ፡፡ ጎበዝ ከሆኑ ‹ ህይወት ከቪላ  በኃላ › ወይም  ‹ የአብዮታችን  ያልተገረዘ መጋዝ › በሚል አንድ አስደናቂ መጽሀፍ ሊደርሱ ይችላሉ ፡፡

4 . ከምስጋና ፣ መወቃቀስና ሹም ሽር በኃላ አዳዲስ ቃላቶችና አባባሎች የሚፈጠሩ ይመስለኛል ፡፡ እነ ተንበርካኪነት፣ 
ተስፋፊነት፣ ጠባቂነት፣ ተቸካይነት፣ ኪራይ ሰብሳቢነት፣ የልማት ሰራዊት እና የመሳሰሉት ተመሳሳያቸውን ወይም ተቃራኒያቸውን የሚያፈሩበት ሁኔታ ይኖራል ፡፡ ከዛም እንደ አካሄድ … እንደ አሰራር… ስብሰባ እንደ ስብሰባ … እያሉ ሃሎ ሃሎ መንፋት ነው ፡፡ በአነጋገር አንድ ዓይነት ልብስ የለበሰ  …

እስኪ  ያወራሁትን ምን ያህል እንደማውቀው ለማረጋገጥ የሆነ መልመጃ ልሞክር ፡፡ < ከላይ በተገለጹት ቃላቶችና የአሰራር ይትበሃሎች ቢያንስ ሁለት ቃላቶችን መስርት ? >

. በቃላት ራስን መቻል !
. የቃላት ሰራዊት ማፍራት !


Sunday, July 15, 2012

‎ፈሳዊ ጉዳያችን‎



ፈስ ሳይንሳዊ በሆነ አካሄድ ወጥ ትርጉም እንዳለው ይታወቃል ፡፡ ነገር ግን በወንዶችና ሴቶች ዓይን ነጥለን ካየነው ሁለት የተለያዩ ትርጉሞች መስጠቱ ግድ ነው ፡፡

ከሴት አኳያ --   አሳፋሪ ተረፈ ምርት
ከወንድ አኳያ --- ከወንድ ጋር የተቆራኘ፣ ራስን መግለጫና መጨረሻ የሌለው የመዝናኛ ምንጭ እንደሚሆን ጥርጥር የለውም፡፡

ፈስ ግዜና ቦታ አይመርጥም ፡፡ አንዳንድ ሰዋች ወንዶች ከሴቶች ይልቅ ብዙ ግዜ ይፈሳሉ ይላሉ ፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ወንዶች በስብሰባ ፣ ስራ ቦታ፣ በእምነት ተቋማት፣ በየመንገዱ ያለርህራሄ ይተኩሱታል ማለት ነው ፡፡ በሌላ በኩል ይህ አባባል እውነት ከሆነ ሴቶች ፈስን በጣም በመቆጠብ መጨረሻ ላይ ግን አስገምጋሚ ጋስ ያስወነጭፋሉ እንደ ማለት ነው ፡፡

የፈስ ሽታ የሚመጣው አነስተኛ መጠን ካላቸው የሃይድሮጅን ሰልፋይድ ጋስና መርካፕታን ከተባለው ንጥረ ነገር ድብልቅ ነው ፡፡ እነዚህ ድብልቆች ሰልፈርን ይዘዋል፡፡ ምግብ ውስጥ ብዙ ሰልፈር ካለ የፈስ ሽታም ጠንካራ እየሆነ ይሄዳል፡፡ አንድ ሰው በቀን በአማካኝ ግማሽ ሊትር የሚደርስ ፈስ ሊያመነጭ ይችላል፡፡ ፈስ ወደ ፈሺው አፍንጫ ቶሎ ከመድረስ ይልቅ ከ 13 እስከ 20 ሰከንድ ሊቆይ ይችላል፡፡ ፈስ በድምጽ ፍጥነት የሚጓዝ ቢሆን ኖሮ ሽታውንም ወዲያው ማጣጣም በተቻለ ነበር ፡፡

ልብ ብላችሁ ከሆነ በሴቶች ሽንት ቤት ውስጥ የፈስ ድምጽ የሚሰማው በእንግዳ ስሜት በጣም አልፎ አልፎ ነው፡፡ ፈስ ከተሰማ ይህን አድራጊዋ ፣ የሰሙ ሰዋች ከአካባቢው እስኪርቁ ድረስ እዛው ልትደበቅ ትችላለች፡፡ በወንዶች ሽንት ቤት ግን ፈስ የበዓል ማዳመቂያ ወይም የጀግንነት ምልክት ይመስል በከፍተኛ ድምጽ ሲንጓጓ ነው የሚውለው ፡፡

በነገራችን ላይ በየትኛውም የዓለም ማዕዘን የምትገኝ ሴት ብዙ የሚያበሳጫትና መታገስ የማትፈልገው ነገር አለ ከተባለ በፈስ ጉዳይ ነው ፡፡ በጥንት ዘመን ወንድ ልጆች አስር አመት ሲሞላቸው ያላቸውን ብቃትና ጥንካሬ ከሚለኩባቸው መንገዶች አንዱ የሚፈሱት ፈስ ምን ያህል ርቀት ድረስ ይሰማል የሚል ነበር ፡፡ አንዳንድ አካባቢ ፈስ በአደባባይ ቢፈሳም የሚያስጨንቅ ጉዳይ አይደለም ፤ አንዳንድ አካባቢ ደግሞ መሸማቀቅ ይስከትላል ፡፡ በአንድ ወቅት ፕሬዝዳንት ኦባማ ንግግር እያደረጉ ‹ ጠ ረ ረ ረ ር ር …. › የሚል ድምጽ ይሰማሉ ፡፡ ንግግራቸውን ገታ አድርገው ወደ ታች ካዩ በኃላ ‹‹ sorry for the gas ! ›› ብለው ንባባቸውን ቀጠሉ ፡፡ ወደ ታች ዝቅ ብለው ሲመለከቱ የሌላ ነገር ድምጽ ሳይመስላቸው  አልቀረም ፡፡ አንድ የኛ ሀገር መሪም ንግግር እያደረጉ ፈሳቸውን አንጣረሩት፡፡ ደንገጥም ሳይሉ ንግግራቸውን ቀጠሉ ፡፡ ምናልባት በለሆሳስ ነው የፈሳሁት ብለው አስበውም ይሆናል ፡፡ ግን ማይክራፎኑ ገዳዩን አጋኖ ቁጭ አደረገው ፡፡ ምናልባትም ከጆርጅ ቡሽ ጋ ጓደኝነት ይኖራቸው ይሆናል ፡፡ ቦብ ውድዋርድ የተባለ ጸሀፊም የቀድሞው ፕሬዝዳንት ጆርጅ ቡሽ በፈስ ነክ ቀልዶች በእጅጉ እንደሚንፈቀፈቁ ጽፏልና ፡፡

 
ዴይሊ ሜል የተባለው ጋዜጣ ደግሞ የሚላዊ ፕሬዝዳንት ቢንግዋ ሙታኒካ በየአደባባዩ መፍሳትን ህገ ወጥ ድርጊት በማድረግ ቅጣት እንዲጣል ሀሳብ ማቅረባቸውን ይነግረናል፡፡ እንደ ጋዜጣው አስተያየት ከሆነ ህጉ የተረቀቀው ህዝቡ ኃላፊነት የሚሰማውና በስነ ምግባር የታነጸ እንዲሆን ከማሰብ አንጻር ነው ፡፡

ሳቅ አለም አብራህ ትስቃለች፣ ፍሳ ለግዜውም ቢሆን ሁሉም ሳቃቸውን ያቆማሉ የሚል ቀልዳዊ አባባል አለ ፡፡ ወፍ የምትጮኀው እንዳገሯ ነውና ወደኛ ስንመጣ ፈስ በቀላሉ ‹‹ ፈሳም ! ›› የሚል ስድብ ያሰጣል፡፡ ‹‹ ይሄ ፈሳም ነው ! ›› ከተባለ ለቁም ነገር የማይበቃ፣ ፈሪና የሚናቅ መሆኑን  ሊጠቁም ይችላል ፡፡ እናም ለመፍሳት ግራና ቀኝ መመልከት ፣ ከተለቀቀም በኃላ ምን ያህል ይሸት ይሆን ? ብሎ አፍንጫን እንደ ውሻ ወደፊት መቀሰር ፣ ይታወቅብኝ ይሆን ? ብሎ አይንና ጆሮን ወደ ጎን ማሽሟጠጥ ይከተላል፡፡

ፈስን ጋስ ነው ብሎ የሚቀበል ትውልድ ገና አልመጣም ፡፡ ህጻናት እንኳን ፈሰኛን የሚያወግዙበት ስነ ግጥም አለቻቸው ፡፡
ፈስ ፈሶ ፈሳራራ
ቆርጦ ቆርጦ ደም ያሳራ
ደሙ ሲረጋ በለው ባለንጋ
አለንጋው ሲበጠስ
ምንቄው ይበጠስ ! / ምንቄ ግን ምንድነው ? /

ወደ አማራው ክልል ስንጓዝ ደግሞ ፈስ ሃይለኛ የጦር መሳሪያ ሆኖ ያገለግላል ፡፡ የቆሎ ተማሪዋችና ደብተራዋች ‹ የጎዳቸውን › ሰው ለማጥቃት በወፍ ቋንቋቸው ይደጋግማሉ ፡፡ ይህን ቋንቋ ከአዲስ ኪዳን ማውጫ ተውሰን  ‹‹ የደብተራ ወንጌል ›› ወይም  ‹‹ የደብተራ ስራ ›› ፤ አሊያም ከብሉይ ኪዳን ተነስተን  ‹‹ መጽሀፈ ደብተራ ›› ወይም  ‹‹ ትንቢተ ደብተራ ››  ለማለት እንኳን የሚያስቸግር ይመስለኛል ፡፡ ብቻ ከመጽሀፍ ቅዱስ ክልል ውጪ ቢሆንም የዋሉበት ድግምት አያሳፍራቸውም ነው የሚባለው ፡፡ ያ - በግዕዝ ቋንቋ የተቃመበት ሰው ታዲያ ቀኑን ሙሉ ለዚያውም ቦታ ሳይመርጥ እንደ አህያ ዘረጥ - ዘረጥ ሲያደርግ ይውላል፡፡ አቤት መሳቀቁ አይታያችሁም ፡፡

‹‹ ወይ ጉድ  ያ- የተበላሸ ባቄላ እኮ ነው ?! …
‹‹ አዬ አያ እንትና ያ - የማልወደውን ሻሜታ ግቶኝ ግቶኝ  !…
መጨረሻ ላይ እውነትን መካድ ሁሉ ሊመጣ ይችላል ፡፡ ‹‹ አይ ይህ ሆዴ … ሆዴ እኮ ነው እንዲህ የሚጮኀው ?  … ››
አህያ የሚለው ቃል የአለቃ ገብረሃና ቀልዶችን አስታወሰኝ ፡፡ ሴትየዋ በእንስራ ውሃ ተሸክማ ቁልቁል ትወርዳለች ፡፡ ቁልቁለቱ በጣም ያዘቀዘቀ በመሆኑ ዘጭ - ዘጭ እያለች በፍጥነት እንድትወርድ ያስገድዳታል ፡፡ በዚህ ግዜ ፈሷ ያመልጣትና ዛጥ ዛጥ ታደርገዋለች ፡፡ ይሄኔ ድምጽዋን ከፍ አድርጋ  ‹‹ አንተ ጊዮርጊስ አሁንስ እንደ አህዮቹ ልታደርገኝ ነው ? ›› ትላለች ፡፡
 ‹‹ እ.ህ.ህ ! … ›› እያለ ጉሮሮውን የሚጠራርግ ሰው ድምጽ ሰምታ ዘወር ስትል አለቃን አየች ፡፡
 ‹‹ ውይ አለቃ ! መቼ መጡ ? ›› አለች የምንተፍረቷን
‹‹ ጊዮርጊስ አህዮቹን ይዞ የወረደ ግዜ ! ›› ሲሉ ኩም አደረጓት

ለነገሩ በዚህ ረገድ አለቃም ኩም የሚሉበት አጋጣሚ ጥቂት አይደለም ፡፡ ልዩነቱ ሌሎቹን እንደሚተርቡ ሁሉ በራሳቸው ላይም መቀለድ መቻላቸው ነው ፡፡ አንድ ወቅት እንዲህ ሆነ ፡፡ የቅርብ ዘመዳቸው ስለሞተ አልቅሰው ፣ ቀብረው ቢደክማቸውም ወደ ቤታቸው መሄድ አልቻሉም ፡፡ ማታ ራት ተበልቶ ተጎዝጉዞ ከለቀስተኛ ጋር በመደዳ ይተኛሉ ፡፡ ትንሽ ቆይተው ግን ፈሳቸው መጣባቸው ፡፡ ይሄኔ ቀስ ብለው ያለ ድምጽ ሊፈሱ አስበው ቂጣቸውን በእጃቸው ከፍተው ቢለቁት ‹ ጠ ረ ረ ረ ር … ! › ብሎ አጋለጣቸው ፡፡ እናም ምነው አለቃ ትልቅ ሰው አይደሉም እንዴ ?! ወዘተ የሚሉ አፋጣጭ ጥያቄዋች ከመወርወራቸው በፊት            ‹‹ አዬ እድሌ መልግጌ አባስኩት አይደል ? ›› በማለት ለቀስተኛውን አሰፈገጉት ፡፡

 
በአንድ እጁ የጀግንነት በሌላኛው የፍርሃት ችቦ ለኩሶ የሚጓዘው ፈስ በተረብ፣ በተረት፣ በአባባል፣ በጥናትም የደለበ ነው ፡፡ የጥናቱን ካዝና ስንከፍተው 96.3 ከመቶ የሚደርሱት ወንዶች ፈስ እንደሚፈሱ ሲያምኑ የሴቶች ቁጥር 2.1 ከመቶ ብቻ መሆኑን እንረዳለን ፡፡ ወንዶች በአማካኝ በቀን 12 ግዜ በመፍሳታቸው ከ 1.5 እስከ 2.5 ሊትር ጋስ ያጣሉ ፡፡ ይህ መጠን አንድ አነስተኛ ፊኛን ለመሙላት በቂ ነው ፡፡ በሌላ በኩል ሴቶች በአማካኝ በቀን ሰባት ግዜ ሲፈሱ ከ 1 እስከ 1.5 ሊትር ጋስ ያስወጣሉ ፡፡

በዓለማችን ታዋቂ ፈሳም ተብሎ የተመዘገበው ጆሴፍ ፓጁል እ.ኤ.አ በ1892 በፓሪስ ከተማ የፈስ ትዕይንት ያቀርብ ነበር ፡፡ ድርጊቱን የሚጀምረው የሆነ ታሪክ እያወራ ሲሆን ይህንንም የተለያዩ ድምጾች ባሉት አሰገራሚ ፈሱ ማጀብ ይችላል፡፡ ይህ ሰው በላስቲክ ውስጥ ሲጋራ ካስገባ በኃላ ላስቲኩን በቂጡ ቀዳዳ ውስጥ በመጨመር ያጨሳል ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ዋሽንቱን ቂጡ ላይ ከሰካው ላስቲክ ጋር በማያያዝ የሀገሪቱን ብሄራዊ መዝሙር ይጫወታል ፡፡ በዚህ ድርጊቱ ከወንዶች ይልቅ ፈስ የሚጠሉት ሴቶች በጣም እንደሚስቁ ተዘግቧል፡፡ አንዳንዶች እንደውም ሳቅ በማብዛታቸው እየታመሙ ወደ ሆስፒታል እሰከመወሰድ ደርሰዋል ፡፡

ከፈስ ጋስ ውስጥ ከ 50 እስከ 60 ከመቶው ናይትሮጂን፣ ከ30 እስከ 40 ከመቶው ካርቦን ዳይኦክሳይድ እንዲሁም ከ 5 እሰከ 10 ከመቶው የሚደርሰው ሚቴን ነው ፡፡ ሚቴን ጋስ መሬት ውስጥ የተቀበረ ፈንጂ እንዲፈነዳ ምክንያት መሆኑ ይታወቃል ፡፡ አንድ ጥናት ብዙ ለመፍሳት ምክንያት ከሆኑ ጉዳዮች አንዱ በምግብ ግዜና ከምግብ ውጪ ብዙ ማውራት መሆኑ ታውቋል ይለናል፡፡ ፈስን በከፍተኛ ደረጃ በማመንጨት በኩል ትልቅ ሚና የሚጫወቱ ምግቦች የአበባ ጎመን፣ ሽንኩርት፣ ነጭ ሽንኩርት፣ ጎመን፣ ዳቦ፣ ባቄላ፣ ነጭ የወይን ጠጅ እና አትክልትና ፍራፍሬዋች ናቸው፡፡

በነገራችን ላይ ከከብቶችና ከበጎች ፈስ የሚወጣው የሚቴን ጋስ በመላው ዓለም 35 ከመቶ ያህል በመሆኑ የመሬት ሙቀት እንዲጨምር፣ የኦዞን ሌዪር ቀዳዳ እንዲሰፋ ትልቅ አስተዋጽኦ ያደርጋል ፡፡ በመሆኑም ለዓለማችን ትልቁ ስጋት አሸባሪነት ሳይሆን የላሞች ፈስ ሳይሆን አይቀርም ፡፡