Sunday, April 15, 2012

‎‹‹ ምግብ ለስራ ››‎



የሌለኝን የ IT ግንዛቤ ወደ አንድ ደረጃ ከፍ ለማድረግ እነሆ ደብረዘይት ከከተምኩ አስር ቀናት ሆኑኝ፡፡ ጓደኞቼ ሲደውሉልኝ ስራ አመራር ኢንስቲትዩት እንዳለሁ እገልጽ ነበር፡፡

‹‹ እህ ምግብ ለስራ ነሃ! ›› ነበር ቀጣይ ምላሻቸው
ይህን ስያሜ እንዴት ሳልሰማሁ ቀረሁ በሚል ተገረምኩ፡፡ ‹‹ ምግብ ለስራ ›› እና ‹‹ ስራ ለምግብ ›› የሚባሉ ቋንቋዋችን የማውቅበት መልኩ ሌላ ነበር፡፡

መቼም ለምቾት ሩብ ጉዳይ የቀረውን ይህን ግቢ ይህን ስያሜ ማሸከም ጡር ሳይሆን አይቀርም፡፡ ግቢው በሚያምሩ ዘንባባዋች፣ የተለያዩ የደን እጽዋትና ለአይን ማራኪ በሆኑ አበባዋች የተሞላ ነው፡፡ እነዚህ ደኖች ላይ በልጅነቴ ሳድን የነበርኳቸው ፒተር፣ ዋሽንት፣ ፍላይ ካውቸር፣ ግንደ ቆርቁር፣ ቀሳሚና ቢጮሌ የምንላቸው ወፎች ጣእመ ዜማቸውን እስከምሽቱ ድረስ ይለግሳሉ፡፡ ርግጠኛ ነኝ እንደ እኔ ስራዬ ብሎ የሚያጣጥማቸው ሰው የለም፡፡ ዘወትር ውሃ የሚረጩት ጎማዋች የሳሩ ገላ ትንቡኬ እንዲሆን አድርገውታል፡፡ ምናለፋችሁ ግቢው እንደ ህጻን ገላ የለሰለሰ፣ ሌላው ቀርቶ ልክ እንደ ህጻን ልጅ ዘወትር ሲስቅ የሚሰማ ነው፡፡

77 ደብልና 67 ሲንግል አልጋ የያዙ የሚያምሩ ቤቶችን ይዟል፡፡ በርካታ መማሪያ ክፍሎች፣ መሰብሰቢያ አዳራሾችና መወያያ ክፍሎች አሉት፡፡ ኮምፒውተርና አያሌ መጻህፍትን ያቀፈ ቤተ መጻህፍት፣ ሽንጠ ረጃጅም የምግብና የመዝናኛ አዳራሾች ከህንጻው ቁጥር ውስጥ የሚመደቡ ናቸው፡፡

የመዝናኛ ነገር ከተነሳ የቅርጫት ኳስ፣ የእጅ ኳሰና የቴኒስ መጫወቻ ሜዳዋች በሚያምሩ ጽዶችና ሳሮች ታጅበው ይቀበልዋታል፡፡ የኮኔክሽን ጉዳይ ገባ - ወጣ የማለት ችግር ቢኖርበትም ቤተመጻኅፍት ቁጭ ብለው ከኢንተርኔት ጋር ያወጋሉ፡፡ላፕቶፕ ከያዙ ደግሞ የተወሰነው የግቢ ክፍል ጋር ተሰይመው በገመድ አልባው ግንኙነት ሩቅ የሚገኝውን ሰርቨር መረጃ አንጣ በማለት ይኮረኩሩታል፡፡

ታዲያ የግቢው እድሜ ቀላል እንዳይመስሎት!! በተመድ የልማት ድርጅት ድጋፍ በ1949 አም ነው የተቋቋመው፡፡ በወቅቱ የተሰጠው ስም ፐብሊክ አድሚንስትሬሽን ኢንስቲትዬት የሚል ነበር፡፡ ‹‹ ስምን መልአክ ያወጣዋል ›› የሚል አባባል ነበር የማውቀው፡፡ ይህን ግቢ ሰይጣን ተተናኩሎት ነው መሰለኝ ከሃትሪክ በላይ አራት ግዜ ስሙን ፐዋውዞታል፡፡

በ1961 - የስራ አስኪያጆች ማሰልጠኛ ማእከል ተባለ
በ1962- የመርሀ ሙያ ማሻሻያና መመዘኛ ማእከል እንደሚገባው ተነገረው
በ1968- የስራ አመራር ማሰልጠኛ መካነ ጥናት እንደሚሻለው ተገለጸለት
ከ1977 በኋላ ደግሞ- የኢትዬጽያ ስራ አመራር ኢንስቲትዩት ተብሏል፡፡ በነዚህ ጊዜያት ሁሉ ተጠሪነቱና አላማው ለየቅል ነበር፡፡ አሁን ግን በአጭሩ ምርምር፣ ምክርና ስልጠናን በስፋት እየሰራበት ነው፡፡ የመ/ቤትዋን በጀት ይጭነቀው እንጂ ከሚሰጡት 51 አይነት አጫጭር ስልጠናዋች የፈለጉትን መውሰድ ይችላሉ፡፡

እና እላችኋለሁ ለምሳ 84፣ ለእራት 84፣ ለቁርስ 50፣ በቀን ሁለት ጊዜ ቡናና ሻይ 65 ፣ ለአልጋ 100 ብር ከተመደበ ሲበሉ መዋል ነው፡፡ ለካስ ምድረ ቀጭንና ወፍራም ባስስልጣን እንደ ቀስት እየተወረወረ ይህን ግቢ የሚወረው ለዚህ ነው - ወይ አለማወቅ ደጉ፡፡ መቼም የቡፌ አቀራረባቸው የሚታማ አይደለም፡፡ በሻይ ሰዓት የሚቀርቡ ኩኪሶች ራሱ ራሳቸውን የቻሉ ምሳና ራት መሆን የሚችሉ ናቸው፡፡ እዚህ ግቢ ከመጣው ጀምሮ የኑሮም ሆነ የኢኮኖሚ ኢንፍሌሽንና ዲፍሌሽን ትዝ ብለውኝ አያውቁም ፡፡ ‹‹  ሆድ ፕላስቲኩ! ከአምስት ቀናት በኋላ ደግሞ እንደ አሪፍ ፓለቲከኛ ሽብልል ብለህ ወደ ቀድሞህ ይዞታህ መመለስን ትችልበታለህ ›› ስል ወቀሳ ቢጤ አቀረብኩለት፡፡

 የመንግስት ሰራተኛው ይህን ምርጥ ግቢ ‹‹ ምግብ ለስራ ›› ሲል የሰየመው እንድም ወቅታዊ የምግብ ጥያቄን ስለሚያስረሳ በሌላ በኩል ደግሞ ወደዚህ ስልጠና የተላከ ሰራተኛ የኪስ አበል ስለማያገኝ ነው ፡፡ የሞላውን ሆድ በቢራ ለመሸርሸር አይቻልም ማለት ነው፡፡

ኢንፍሌሽን በየት ዞሮ መጣ !!! እንደ ቀስት ተወርውሬ አመልጠው ይሆን ??

‎‹‹ አንደኛው ዝሆን ››‎





ሰሞኑን ጎን ለጎን ሳነባቸው ከነበሩት መጽሀፍት መካካል ሁለቱን አጠናቀቅኩ፡፡ የአቶ ስዬ አብርሃ እና የዶ/ር ያእቆብ ሃይለማርያምን፡፡ የአቶ ስዬ መጽሀፍ ‹‹ ነጻነት እና ዳኝነት በኢትዮጽያ ›› ይሰኛል ርእሱ፡፡ ባለ 440 ገጽ ሲሆን ዋጋው 70 ብር ነው፡፡

አቶ ስዬ ከፍተኛ የመንግስት አመራር ከመሆናቸው ውጪ የተዘረዘረ ስብዕናቸውን / የአንድ ወገን መረጃ ቢሆንም / በከፊል እንዳውቅ ያደረጉኝ የተስፋዬ ገ/አብ መጽሀፍት ናቸው፡፡ በተለይም በደራሲው ማስታወሻ ላይ ‹‹ ሁለቱ ዝሆኖች ›› በሚል ርዕስ በቀረበው ጽሁፍ፡፡

በጽሁፉ ላይ አቶ ስዬ ወይም ‹‹ አንደኛው ዝሆን ›› ለስልጣን የሚተጉ፣ ጠብ አፍቃሪ፣ የህክምናን ሙያን በከፊል ያጠኑ፣ ዲፕሎማሲ የማያውቁ፣ ተቆጪ፣ ሰውን የሚንቁ፣ ወታደራዊ ብቃት ያላቸው፣ ለይቅርታ የራቁ፣ በምንወደው የቶም ኤንድ ጄሪ ፊልም ላይ እንደ ቶም የተወከሉ መሆናቸውን እናነባለን፡፡

ይህ መነሻ የሚሰጠው አንድ ደራሲ ምናልባት ጥቂት ለየት ያሉ ነገሮችን ጨማምሮበት በአንድ መጽሀፍ ወይም ቴአትር ውስጥ አሪፍ ገጸባህሪ መሳል ይችላል፡፡ እንግዲህ እኔም ይህን ቀመር እያስታወስኩ ነበር ከላይ የተጠቀሰውን መጽሀፍ ማንበብ የጀመርኩት፡፡

በኮሌጅ ቆይታ ወቅት የመጽሀፉን አጠቃላይ ጭብጥ በአንድ ወይም ሁለት መስመር አስረዳ ? የምትል ጥያቄ እንጠየቅ ነበር፡፡ ይህን ጥያቄ አሁን ተውሼ የአቶ ስዬን መጽሀፍ ባስረዳ ‹‹ እኔ የታሰርኩት በሙስና ሳይሆን ከጠ/ሚ/ር መለስ ጋር በነበረኝ የፓለቲካ መስመር ልዬነት ነው፡፡ ፍ/ቤቱም ሙሰኛ መሆኔን በበቂ ሁኔታ ሊያሳይ አይችልም ›› የሚል መልእክት እናገኛለን፡፡
በርግጥ ይህ ቱባ መልእክት የተገኘው በየምዕራፉ ሀሳቡን ለማዳበር በተጠነጠኑ ቀጫጭን ድውሮች ድምርነት ነው፡፡ አቶ  ስዬ በየምእራፉ ሰለማስረጃ፣ መቃወሚያ መግለጫ፣ የመከላከያ ማስረጃ፣ የሰነድ ማስረጃ፣ የሰዋች ምስክርነትና የቅጣት ውሳኔ አካሄድ ደረጃ በደረጃ ለማሳየት ሞክረዋል፡፡

ወታደራዊ ስብዕናው ጎልቶ ከሚነገርለት አንድ ሰው ይህ መጽሀፍ መመረቱ ያስገርማል፡፡ የሚገርመው አንድም ያልተጠበቀ በመሆኑ ሲሆን በዋናነት ግን መጽሀፉን ጅማት ሆነው ሊያቆሙት የቻሉት እውነታዋች ናቸው፡፡ እነዚህ እውነታዋች የአቶ ስዬ የማስታወስ ብቃት፣ ማስታወሻ የመያዝና መረጃዋችን ስብስቦ እንዳግባቡ የመስፋት፣ ለህግ ያላቸው ግንዛቤ የማይናቅ መሆኑና ብዙም ሊታማ የማይችለው የትረካ አቀራረባቸው በግልጽ መታየታቸው ናቸው፡፡

ዝሆን እጅግ አደገኛ በሆኑት አንበሳና አዞ ፊት እንኳ የተለየ ድፍረት የሚያሳይ እንሰሳ ነው፡፡ የራበው አዞም ሆነ አንበሳ ግን አዘናግቶና ልዬ ስልት ተጠቅሞ ገቢ ሊያደርገው ይችላል፡፡ አቶ ስዬ የሚያስቡትን ሁሉ ያለ ፍርሃት ይናገራሉ፡፡ በፍ/ቤት ከዋናው ርዕስ በመውጣት የፓለቲካ ጉዳዬች ሲናገሩ በዳኞች በተደጋጋሚ እየተገሰጹ ያስቆሟቸው እንደነበር እናነባለን - በርግጥም እኔም በአንድ የግል ጋዜጣ ውስጥ ስሰራና ጉዳዩን ለመዘገብ ስከታተል ይህን አይቻለሁ፡፡

ከድፍረቱ በተጨማሪ እንደ ቶም ሳይሆን እንደ ጄሪ ብልጠት የተላበሰ የአዳኝ - ታዳኝ ስልት ይከተሉ ነበር፡፡ ለአብነት ያህል በፍ/ቤት ባገኙት የመናገር አጋጣሚ  ክሱ የፓለቲካ መሆኑን ሳይጠቁሙ አያልፉም፡፡ ጎን ለጎን ግን የሚቀርብባቸውን የተለያዬ ክሶች ሁሉ  በሰውና በጽሁፍ ማስረጃዋች ለመከላከል ከፍተኛ ትግል ሲያካሄዱ ይታያል፡፡ ጉዳዩ የፓለቲካ ከሆነ ያለቀለት በመሆኑ መልፋት ላይስፈልግ ይችላልና፡፡

አቶ ስዬ በመጽሀፋቸው ደጋግመው ሲያደንቁት የተሰማ ተቋምም አለ፡፡ እንደውም ‹‹ መተኪያ የሌላቸው ተቋማት ›› በማለት ነው የግሉን ፕሬስ ሚና የገለጹት፡፡ ምናልባትም ቀድሞ ከነበራቸው አመለካከት አንጻር የሚፈተሸ ከሆነ ወደ ‹ ይቅርባይነት › ወይም ‹ አድናቂነት › ተሸጋግረዋል ማለት ነው፡፡ በርግጥ ወደዚህ አቅጣጫ ለማምራት የሚያስችሉ በርካታ ውስጣዊና ውጫዊ ተጽእኖዋች መኖራቸው እንደተጠበቀ ሆኖ፡፡

ከዋና ጉዳያቸው ጎን ለጎን ስለዳኝነትና ፓሊስ አሰራር፣ ስለፍትህ መጎደል፣ ስለምርጫ ቦርድ ነገር፣ ስለእስረኞች አያያዝ፣ ስለ ምርጫ 97 አንድምታዋች፣ ህወሃትን ጨምሮ ስለ ፓለቲካ ድርጅቶች ድክመትና ጥንካሬ ቀደም ብሎ በተገለጸው ‹‹ ዝሆናዊ ›› መንገድ እምነታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በጥቅሉ ወንድ ልጅ ሀዘናዊ ስሜትን ደብቆ መያዝ ይችላል ይባላል፡፡ በተናጥል ስናይ ደግሞ ፓለቲከኞችና ወታደሮች ልበ ደንዳኖች እንደሆኑ ይታመናል፡፡ ለሞትና ለሌሎች ውጣ ውረዶች ቅርብ በመሆናቸውና ጉዳዩን በመለማመዳቸው ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ ሀሳብ ግን ሁልግዜ ትክክል አይደለም፡፡ ለምሳሌ አቶ ታምራት ላይኔ ከእስር ከተፈቱ በኋላ በአንድ የእምነት አዳራሽ ተገኝተው ስለ ፈጣሪ ቃል ያስተምሩ ነበር፡፡ ቪዲዮውን የተመለከትኩ ግዜ እጅግ ብዙ ነገሮች አስገርመውኝ ነበር፡፡ የገረመኝ ሰሜን ዋልታ ይገኝ የነበረ አንድ አለማዊ ፓለቲከኛ በምንም ወደ ማይዋሰነው ሃይማኖታዊ የደቡብ ጫፍ የመምጣቱ ገዳይ አልነበረም፡፡ የገረመኝ የአቶ ታምራት ምላስና እንባ ጣፋጭ መሆናቸው ነበር፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል የሚሰብከው አንደበታቸውና በተወሰነ ርቀት ከአይናቸው የሚወርደው መጠነ ሰፊ እንባ በእጅጉ የተናበቡ ነበር የሚመስሉት፡፡ ንግግራቸው የትምክህትን ኮፍያ ያወለቀ ነበር፡፡ አንደበታቸው  ይቅርታን ወደ ነፍሳቸው ለማስገባት የሚካድም ነበር፡፡ አንደበታቸው ታላቅ ‹ ፈጣሪ › መሆኑን፣ በምድር ላይም የሰው ታላቅ ካለ  በ ‹ግዜ › ድጋፍ የቆመ ብቻ መሆኑን የሚያስረዳ ነበር፡፡ እናም ይህን አንደበታቸውን ሲያስፈልግ በጥያቄ ምልክት፣ ሲያስፈልግ በቃለ አጋኖ፣ ሲያስፈልግ በትምህርተ ጥቅስ፣ ሲያስፈልግ እንደ አራት ነጥብ ሆኖ ሲያስረዳ የነበረው እንባቸው ነበር፡፡ በቃ ! ስሜት የሚንጥ ንግግር ሰፈልቅ….የሌሎችን ስሜት የሚያሸብር እንባ ይከተላል ፤ እስከማስታውሰው ድረስ ፍሰቱ እንዲህ ነበር፡፡ አቤት እንዴት ነበር የሚወርደው ? የወንድ ልጅ ለዚያውም የፓለቲከኛ፣ ለዚያውም የወታደር…

በአቶ ስዬ መጽሀፍ ውስጥ ግልጽ እንባ ባይታይም ለቤተሰባቸው ያለቸውን ጥልቅ ፍቅርና ስስ ነፍስ እንመለከታለን፡፡ እሳቸው እስር ቤት ገብተው ሲጨነቁ የሚታዩት ለወንድሞቻቸውና ለእህታቸው ነበር፡፡ምን ሆነው ይሆን ? በማለት ብዙ ይቆዝማሉ፡፡ ለእናታቸው የነበራቸው ስስትና ፍቅር ደግሞ የተለየ ይመስላል፡፡ በልጆቹ የእስር ምክንያት ህይወታቸው አደጋ ላይ እንዳይወድቅ ስጋታቸውን፣ ፍርሃታቸውን፣ የውስጥ ጩኅታቸውን ሳይቀር በእንባ ሳይሆን በቃላት በመግለጽ ለአንባቢ ሲያጋቡት ይታያል፡፡
በአቶ ስዬ መጽሀፍ ውስጥ ያልታየ ጉዳይ አለ ከተባለ አውቀውም ሆነ በስራ ስህተት ምክንያት ያጠፉትን ወይም ካነሱት ትልቅ ርእስ አንጻር የእሳቸውን  አሉታዊ አስተዋጽኦ አለመጠቆማቸው ነው፡፡

በማጠቃለያ ምዕራፍ ያቀረቧቸው ሀሳቦች የተነሱበትን የዳኝነት ነጻነት /ነጻነትና ዳኝነት የሚለው የእሳቸው ርዕስ በተለይም ነጻነት ሰፊ ሃሳብ በመሆኑ ለኔ አልተመቸኝም / መርሆዋች እውን ለማድረግ የምሶሶ ያህል የሚጠቅሙ ናቸው፡፡ ችግሩ እነዚህን ጸጋዋች እንዴትና በነማን እናግኝ የሚለው ነው፡፡በቅድሚያ እነማን መስዋእትነት ይክፈሉ ነው፡፡ ቢፒአር የተማሩ ትናንሽና ትላልቅ መሪዋችም በሙሉ የሚከተለውን የሃሪ ትሩማን ጥቅስ ሰምተውታል  << A leader is a person who knows the road, who can keep a head, and who can pull others after him. >>

በርግጥ ይህን መሰረታዊ መመሪያ ለማስፈጸም ብዙ፣ ምናበ ሰፊና ሰላማዊ ዝሆኖች ያስፈልጉናል፡፡




‎ዳንዲ የነጋሶ መንገድ‎



‹ዳንዲ የነጋሶ መንገድ›› በዳንኤል ተፈራ የተዘጋጀ ፣በዶክተር ነጋሶ ህይወት ዙሪያ የሚያጠነጥን ፓለቲካ ቀመስ መጽሀፍ ነው፡፡ በመጽሀፉ ትረካ መሰረት የምናስብ ከሆነ ዶክተሩ ምስኪን ወይም ታማኝ ፓለቲከኛ መስለው ይታዩናል፡፡ በርግጥ ታማኝነት እንዴትና ለማን የሚሉ መሰረታዊ ጥቄዋችን መመለስ ይኖርብናል፡፡ ዶክተሩ በፍጹም ብልጣብልጥ አይደሉም፣ ዲፕሎማት አይደሉም፣ ብዙ ግዜ ፓለቲካ የሚጠይቀውን አስመሳይነት፣ ፈጣጣነት፣ ዋሾነትና ጨካኝነት ዕውን የሚያደርግ ነፍስ የላቸውም፡፡ ታዲያ እንዴት ፓለቲከኛ ሆኑ? ይህን ስራ እንደማይተውም ይናገራሉ- እንዴት ይዘልቁት ይሆን? ለግዜው ቅርብ የሆነው መልስ እንጃ በመሆኑ እንጃ ብያለሁ እኔም፡፡ ለማንኛውም አንዳንድ ሀሳባቸውን እነሆ…….የነጋሶ መንገድ…..

ሲጋራ እንዴት እንደጀመሩ

በእደ ማርያም አዳሪ ትምህርት ቤት ተደራራቢ አልጋ ላይ ተኝተን አለማየሁ ከታች ሆኖ ቫይስሮይውን ሲያቦነው እኔ ከላይ ሆኜ አሸታለሁ፡፡ በኋላ ‹‹ እንካ እስኪ ሞክረው›› ብሎ ይሰጠኝና ስሞክረው ጣመኝ፡፡ በዚያው አጫሽ ሆንኩ፡፡ ‹‹ እንካ አጭስ›› ሲለኝ የነበረው በኋላ ‹‹ እኔ አልሰጥህም እራስህ ግዛና አጭስ›› ማለት ጀመረ፡፡ በኋላ ኒያላ መጣ፡፡ ኒያላ መመረት ከጀመረ አንስቶ ነው ደንበኛ አጫሽ የሆንኩት፡፡ ባለቤቴም ከኒያላ ሌላ አጢሳ አትውቅም

የብሔር ጭቆና አጀማመር

አጼ ምኒሊክ ይከተሉት የነበረው ስርዓት ባላባታዊ ነው፡፡ ይህ ገዥ መደብ የመጣው አማርኛ ተናጋሪ ከሆኑ ህዝቦች ነው፡፡ የኦርቶዶክስ ሃይማኖት የበላይነትን እንዲያገኝ ክርስትያን ያልሆኑትን ሁሉ በግድ ያጠምቁ ነበር፡፡የአስተዳደሩ ቋንቋ አማርኛ እንዲሆን ተደርጓል፡፡ ሌሎች ሃይማኖታቸውን፣ባህላቸውንና ቋንቋቸውን እንዲተው የተደረገበት ሁኔታ ነበር፡፡ በኢትዮጽያ የብሄር ጭቆና የተጀመረው ያን ጊዜ ይመስለኛል፡፡

የተቃውሞ ሰልፍ እንዴት ይበተን ነበር?

ያኔ ተቃውሞን ለመከላከል በጣም ከበዛባቸው አንዳንድ ተማሪዋችን ያስራሉ፡፡ ከዚያ ባለፈ ግን ከኛ ጋር ግብግብ በመግጠም ወይ በጭስ ነበር የሚበትኑት፡፡ አሁን ግን ተቃዋሚ ሰልፈኞች በጥይት ተቆልተዉ የሚበተኑበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ያውም በዚህ ዘመን…

መንግስት ህዝብን ይፈራ/ያከብር ነበር?!

ዙምባቤ ነጻ ትውጣ በማለት እንግሊዝ ኤምባሲ ፊት ለፊት ተሰለፍን፡፡ ያኔም ከፓሊስ ጋር ተጋጭተናል፡፡ እነዋለልኝን አስረዋቸው ነበር፡፡ እኛ ደግሞ እነዋለልኝ ይፈቱ ብለን ሰልፍ ወጣን፡፡ አፍሰው ወደ ሰንሳፋ ሲወስዱን ኮተቤ ላይ ስንደርስ አንድ ልጅ ከመኪና ላይ ወድቆ ይሞታል፡፡ ወሪው በአዲስ አበባ ይዛመትና ከተማዋ ቀውጢ ሆነች፡፡ ፈርተው በማግስቱ ፈቱን፡፡

ሚሲዮኖች በወለጋ እንዴት በዙ?

ሚሲዮኖች ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሸዋ መጥተው ለመንቀሳቀስ አጼ ሚኒሊክን ፈቃድ እንዲሰጧቸው ሲጠይቋቸው እሳቸውም ‹‹ ሸዋ፣አርሲ፣ሀረርና ጅማ ክርስቲያኖችና እስላሞች ስለሆኑ የሚሲዮን ትምህርት አያስፈልጋቸውም እናንተ መሄድ ያለባችሁ ገና ወዳልሰለጠነውና አሁንም አረመኔ ወደሆነው ጠረፍ አካባቢ ነው አሏቸው፡፡ በዚህም ምክንያት ወደ ወለጋ ሄደው አስተማሩ

የመጀመሪያው የኦሮሞ የትግል እንቅስቃሴ

የኦሮሞን ህዝብ እግዚሀብሄር ከሰማይ መጥቶ አይታደገውም ስለዚህ ራሱ ተደራጅቶ ለመብቱ መታገል አለበት…. የሚል አቋም ይዘን መቀስቀስ አለብን፡፡ ለዚህ ደግሞ ጽሁፎችን ማዘጋጀት ይኖርብናል ብለን ርዕሰ ጉዳይ ተከፋፍለን መጽሔት ለማዘጋጀት በቃን፡፡ መጽሔቱ ‹‹ oromo voice against tyranny›› የሚል ነበር፡፡ በኋላ በአማርኛና በኦሮምኛ ተተርጉማ  ቀርባለች፡፡ የሚያሳዝነው በመጽሔቷ የተነሳ ብዙዋች ለእስር ተዳርገው ነበር፡፡

የመጀመሪያ ፍቅር

በ13 ዓመቴ ከሚዛን ወደ ደምቢዶሎ የተባረርኩት በፍቅር ምክንያት ነው፡፡ ከበቡሽ ሀብት ይመር የምትባል የመንደራችን ልጅ እና እኔ በጣም እንወደድ ነበር፡፡ የ18 ዓመት ልጅ ነበረች፡፡ አቶ ከበደ ጨብራሻ አገባት፡፡ ስታገባ ድንግል አልነበረችም፡፡ ለካ የአካባቢው ሰው ድንግልናዋን የወሰደው ነጋሶ ነው ብለው ያሙኝ ኖሯል፡፡ እኔና አቶ ከበደ ኳስ ሜዳ የተጣላን ጊዜ በዚህ ምክንያት ነው ብለው ሰዋች ለአባቴ ሲነግሯቸው ‹‹ ይሄንን አድርጎ ከሆነ እቀጣዋለሁ›› ብለው ወደ ደምቢዶሎ መለሱኝ፡፡

የመጀመሪያው ትዳር

በ1964 ዓም ክረምት ላይ ደሲቱን አገባሁ፡፡ በዓመቱ በ1965 ኢብሳ ተወለደ፡፡ ኢብሳ ያልንበት ምክንያት ለሁለት ሳምንት ተቋርጦ የነበረው መብራት ልክ እሱ በተወለደ ማታ ስለበራ ነው፡፡ ኢብሳ ማለት ደግሞ የሚያበራ ማለት ነው፡፡ ሁለተኛዋ ልጃችን ጃለሌ ናት…
የኦነግ መቋቋም

እዚህ በነበርኩ ጊዜ አዲሱ፣ ጸጋዬ፣ዮሀንስ፣ለታና ዮሀንስ ኖጎ የሚባሉ የድሮ ጓደኞቼን አግኝቻቸው አወራን፡፡ ማታ ማታ ይጠፋሉ፡፡ ‹‹ ማታ የት ሄዳችሁ?›› ስላቸው ‹‹ ስበሰባ ነበረን›› ይሉኛል፡፡ ለካ ኦነግን እያቋቋሙ ነበር፡፡ እኔን ግን ስብሰባቸው ላይ አይጠሩኝም፡፡ በህብዑ ነበር የሚሰሩት፡፡ በዚህ እንቅስቃሴ ውስጥ እነ ባሮ ቱምሳ ፣ጄኔራል ታደሰ ብሩ፣ ዲማ ነጋዋ፣ ዮሀንስ ለታ ዮሀንስ ኖጎ እና አዲሱ ቶሎሳ አዲስ ፕሮግራም በማዘጋጀት ስራ ላይ ተጠምደው ነበር፡፡

ታሪክ ሰሪው ሌንጮ

በ1967 ዓም መጀመሪያ ንጉሱ ከተወገዱ በኋላ ሰላማዊ ሰልፍ በተደረገ በሳምንቱ ወደ ጀርመን ሄድኩ፡፡ ሌንጮ/ዮሀንስ ለታ ወደ ጀርመን እሄዳለሁ ብዮው ሲሸኘኝ፣
‹‹ ምን ለመማር ነው የምትሄደው?›› አለኝ
‹‹ ታሪክ››
‹‹ አንተ ሄደህ ታሪክ ተማር፣ እኛ እዚህ ታሪክ እንሰራለን!›› ብሎ አሾፈብኝ

ለዶክትሬትዲግሪ ያቀረቡት የመመረቂያ ጽሁፍ

<<The history of seyyoo oromo of south western wallaga, Ethiopia from 1730 to 1986>>
ዲግሪውን ያገኙት በ1977 ዓም ነው፡፡

የአልማዝ መኮ/የፓለቲከኞች/ ሁለት መልክ

አልማዝ ኦሮሞ ስለሆነች የኦህዴድ አባል እንድትሆን ለማግባባት ሞክሬ ነበር፡፡ እምቢ አለች፡፡ ቆይቶ የኦሮሚያ አስተዳደር ስራ አስፈጻሚዋች፣ የኦሮሚያ ሴቶች ቢሮ ሃላፊ ሆና አየኋት፡፡ ሰኔ 15 ቀን 1993 ዓም እኔ ከኢህአዴግ ስብሰባ በለቀቅኩ ዕለት ታዲያ ለኢህአዴግ ተቆርቋሪ ሆና ‹‹ ነጋሶ ሂሳቡን ሳያወራርድ እንዴት ይወጣል?›› ብላ ትችት ሰነዘረች፡፡ የሚገርመው ይህን ባለች በሳምንቱ ለስብሰባ ወደ ብራዚል ተልካ፣ በኒውዬርክ ስታልፍ እዛው ጥገኝነት ጠይቃ መቅረቷን ሰማን፡፡ ብዙም ሳትቆይ የኦነግ አባል መሆኗ ተወራ፡፡

የደስታ እንባ?

ኢህአዴግ አዲስ አበባን የተቆጣጠረ ጊዜ መለስ ለንደን ሆኖ ምን እንደተሰማው የነገረኝን አስታውሳለሁ፡፡ ‹‹ አሜሪካኖች ‹ኢህአዴግ አዲስ አበባን ተቆጣጠረ› ሲሉን ከደስታዬ ብዛት አለቀስኩ!›› ነበር ያለኝ

ማስተከከያ

በኤርትራ ሪፈረንደሙ በሚካሄድ
በት ጊዜ ድምጽ መስጫው ‹‹ ባርነት ወይስ ነጻነት›› የሚል ነው ተብሎ የተወራው ትክክል አይደለም፡፡ የድምጽ መስጫው ‹‹ ነጻነት ትፈልጋለህ ወይስ አትፈልግም;› ›› የሚል ምርጫ ነበር፡፡

ሽርሽር በነጠላ ጫማ

የነጻነትቸው ቀን ሲከበር መለስ ኤርትራ ሄዶ በትግርኛ ንግግር ሲያደርግ  እኔም ነበርኩ፡፡ እኔ፣ መለስና ኢሳያስ / ስሊፐር ጫማ አድርጎ/ ከተማ ውስጥ ዞረናል፡፡ በእውነት ትልቅ ነጻነት ነበር የተሰማኝ፡፡ ሱቅ እየገባን፣ ማታ ማታ እየዞርን አንድ ሁለት ቦታ መጠጥ እየተጎነጨን ተዝናንተናል፡፡ ያረፍነው በራሰው ካሳ ቤት ውስጥ ነበር፡፡

የመምሪያ ሃላፊዋቹ እንዴት ተባረሩ?

ኢህአዴግ በ1983 ዓም ሀገሪቱን ሲቆጣጠር ከማስታወቂያ ሚኒስትሩ ዲማ ነጋዋ በቀር የመምሪያ ሃላፊዋች በሙሉ  የኢህአዴግ ታጋዬች ነበሩ፡፡ የፕሬስ መምሪያ ተስፋዬ ገብረአብ፣ የቴሌቪዥን አማረ አረጋዊ፣ የኢዚአ መዝሙር ፋንቴ፣ የኦሮምኛ ፕሮግራም ሃላፊ ደግፌ ቡላ እና የኦሮምኛ ራዲዬ ፕሮግራም ሱሌይማን ደደፎ ነበሩ፡፡…. ታዲያ ባደረግናቸው ግምገማዋች አንዳንዶቹ የአቅም ፣ ሌሎቹ የሙያ ፣ ቀሪዋቹ ደግሞ የስነምግባር ችግር ነበረባቸው፡፡ ለምሳሌ ሙስናን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ለዜና ስራ አበልና መኪና ተመድቦላቸው እነሱ ማስታወቂያ ይሰራሉ፡፡ በሰራተኛው ላይ አምባገነን የመሆንና ሌሎች ችግሮችንም ይፈጥራሉ፡፡ ሴቶችን ያመናጭቃሉ፣ በዘመድ ይሰራሉ፡፡ የአመለከከትም ችግር ነበረባቸው፡፡ ለስሙ የኢህአዴግን ነገር ያስቀድማሉ፣ የብሄሮችን መብት በተመለከተ ግን ትምክህተኝነትና ጠባብነት የሚያራምዱ ነበሩ፡፡ በነዚህ ምክንያቶች ሁሉንም እንዲለቁ አድርገናል፡፡ በዙዋችን ወደ ኢህአዴግ ተቋማት -ፋና፣ ዋልታ፣ ሲዛወሩ ተስፋዬ ገብረአብ ወደ እፎይታ መጽሄት ተልኳል፡፡ ከነአካቴው እንዳይባረሩ ደግሞ ሁሉም ታጋዬች ናቸው፡፡

ዝነኛው አንቀጽ 39

እኔና ዳዊት አንቀጽ 39 መኖር አለበት፣ መሬትም መሸጥ መለወጥ የለበትም የሚል አቋም ይዘን ተከራክረናል፡፡ የብሄር ጥያቄን በተመለከተ የኦሮሞ ህዝብ የራሱን እድል በራሱ የመወሰን መብቱ እስከመገንጠል መከበር አለበት የሚል ነበር አቋሜ፡፡ እዚህ ጋ መገንጠል አለበት ማለትና የመገንጠል መብቱ ይከበርለት ማለት ልዩነት እንዳለው ልብ ማለት ያሻል፡፡ አሁንም የህዝቡ የራሱን ዕድል በራስ የመወሰን መብቱ መከበር ትክክለኛ ነው፣ ዴሞክራሲያዊም ነው እላለሁ፡፡

የፕሬዝዳንቱ ቤት

ይገርምሃል ! ሌላ ሀገር አንድ ርዕሰ- ብሄርን እንዲህ አድርገው ይይዛሉ? አላውቅም፡፡ እነዛ አሮጌ ቤቶች በራቸው ሲዘጋ ከስር አይጦች ያስገባ ነበር፡፡

እጅ መንሻ

ባለስልጣኖች ጉብኝት በሚያደርጉበት ጊዜ የአካባቢው ትናንሽ ባለስጣናት ከአካባቢው ነዋሪዋች ላይ ቅቤ፣ በግ፣ ከብት እና ሌላም ሌላ ነገር እየሰበሰቡ ሲሰጧቸው ታዝቤያለሁ፡፡ በእኔ ስም ይዘው እንዳይመጡ በጥበቅ አስጠነቅቃቸው ነበር፡፡ አንድ ጊዜ ግን ከባሌ አገልግል ጭነው ይዘውልኝ እንደመጡ አስታውሳለሁ፡፡ አሁን እነ አባዱላና እነ መለስ በየአካባቢው አንዴ ጋቢ፣ሌላ ጊዜ በሬ ተበረከተላቸው የሚባለውን ስሰማ ‹‹ ወዴት እየሄድን ነው? ›› እላለሁ፡፡ እንደኔ እንደኔ ትክክል አይደለም፡፡

የግም-ገማ ጣጣ

የፋይናንስ ቢሮን  ይመራ የነበረውን አቶ አለማየሁ ደሳለኝን ስንገመግም ቆይተን ሳንጨርስ ለምሳ ወጣን፡፡ ከምሳ ስንመለስ አለማየሁ ቤተመንግስት  ግቢ ውስጥ  ራሱን በሽጉጥ ገደለ፡፡ የሚያሳዝነው አለማየሁ በግምገማው ምንም አልተገኘበትም፣ ንጽህነቱን ልንነግረው ነበር፡፡ ግምገማው እጅግ ከባድ ስለሆነ የሚያለቅሱና እንደ እብድ  የሚያደርጋቸው ነበሩ፡፡

በሰው ልክ የሚሰፉ አዋጆች

አቶ ስዬ አብርሃ ተከስሶ ፍርድ ቤት በቀረበ ጊዜ ፣ የከፍተኛ ፍርድ ቤት ዳኛ የነበረችው ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ በዋስ ልትለቀው እንደሆነ ታወቀ፡፡ ይሔኔ ‹‹ አቶ ስዬ በዋስ እንዳይለቀቅ ቶሎ አዋጅ መውጣት አለበት›› ተባለና የወቅቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተፈራ ዋልዋ ደወለልኝና ‹‹ እባክህ በፓርላማ በኩል ጸድቆ የመጣውን አዋጅ ቶሎ ፈርምልን›› አለኝ

የአልጀርሱ ስምምነት

የአልጀርሱን ስምምነት ለመፈረም በተስማማንበት ወቅት አዲሱ ለገሰ መናደዱ ትዝ ይለኛል፡፡ ‹‹ ከዚህ በኋላ በሻዕቢያና በህውኀት መካከል ችግር ተፈጥሮ ወደ ጦርነት የምንገባ ከሆነ የኛን ህዝብ ሂዱና ተዋጉ ብዬ አልቀሰቅስም!›› አለ፡፡ የሆኖ ሆኖ የአልጀርሱ ስምምነት በፓርላማ ጸድቀ፡፡ እኔም በስነስርዓቱ መሰረት ፈርሜያለሁ፡፡ ‹‹ ያለ ቅድመ ሁኔታ የአልጀርሱን ስምምነት እንቀበላለን›› ብለን ለመፈረም መወሰናችን ትልቅ ስህተት ነበር፡፡

የነስዩም ስህተት

ስዬም መስፍንና አሊ አብዶ ህዝቡን አስወጥተው ‹‹ ባድሜ ለኛ ተፈረደ›› ብለው ሲያውጁና ሲያስጨፍሩ እኔ ወለጋ ነበርኩ፡፡ እነሱ ያደረጉት ትክክል አልነበረም፡፡….. እኛን በሚጎዳ መልኩ መወሰኑን ተገንዝቤያለሁ፡፡

የመለስ ደብዳቤ

በክፍፍሉ ወቅት መለስ ለኦህዴድ ደብዳቤ ሲጽፍ የኢህአዴግ ማህተሞች በውህዳኑ እጅ ስለነበሩ በህወሃት ማህተም ይጠቀም ነበር፡፡ ይሄን በተመለከተ በደብዳቤው መጨረሻ ያሰፈረው ሃሳብ ዘና የሚያደርግ ነው፡፡ ‹‹ አንጃው ማህተሞቹን ህገወጥ በሆነ መንገድ ስለዘረፈ የኢህአዴግን ማህተም ላሰፍር አልቻልኩም›› ይልና ‹‹ የመንግስት ማህተም ያለበት ደብዳቤ ከዚህ ቀደም ጽፌ በናንተ በኩል ሂስ ስለቀረበብኝ ፣ ማህተም የሌለው ደብዳቤ መጻፍም የሚያስከትለውን ችግር ግምት ውስጥ በማስገባት በኢህአዴግ ሊቀመንበርነቴ በምጽፈው ደብዳቤ ላይ የማሰፍረው ማህተም በማጣቴ፣ በህወሀት ማህተም ለመጠቀም ተገድጃለሁ››

ነጭ ካፒታሊዝም

ከሁሉም በላይ ግን ከዚህ ድርጅት ጋር መቀጠል የለብኝም ብዬ እንድወስን ያስገደደኝ ፣ ኢህአዴግ የሚመራበትን ርዕዮተ ዓለም እንደቀየረ በተገለጸ ጊዜ ነው፡፡ በስብሰባው ‹‹ ማርክሲስት ሌኒኒስት አለ ወይ?›› የሚል ጥያቄ ቀርቦ ነበር፡፡ ‹‹ የሶሻሊዝም ጉዳይ ቀረ ወይ?>>
‹‹ ማርክሲስት ሌኒንስት ከ1983 ዓም ጀምሮ የለም፡፡ ሰዋች ቢኖሩም እንደ ቡድን ኢህአዴግን የሚመራ ርዕዬተ ዓለም መሆኑ ቀርቷል፡፡ ሶሻሊዝምን በተመለከተ ከ1983 ጀምሮ ጠረጼዛ ስር ደብቀነዋል፡፡ ከምዕራባዊያን ድጋፍ ለማግኝትና የኢትጽያ ሀዝብ በደርግ የተነሳ ስለጠላው ነጭ ካፒታሊዝም ነው የምናራምደው›› አለ መለስ
‹‹ እስከ መቼ››
‹‹ ይሄ የኔ ጉዳይ አይደለም፡፡ እስከ ልጅ ልጅ ሊዘልቅ ይችላል፡፡ ምናልባት በልጆቼና በልጅ ልጆቼ ዘመን ሊሆን ይችላል፡፡›› አለ መለስ ሲመልስ
‹‹ ይሄን መቼ ወሰናችሁ?›› ተብሎ ሲጠየቅ ደግሞ ‹‹ ከ1983 ዓም ጀምሮ ነው›› አለ፡፡ ብዙ ሰው ነው ብግን ያለው፣ ምክንያቱም የኢህአዴግ ፕሮግራም እንዲህ አይልማ፡፡ እኔማ ቅ-ጥ-ል አልኩ፡፡ ለካ አስር አመት ሙሉ አታሎን ነበር፡፡



‎የእኛ የእያሱና የመንግስት ‹‹ ቲፕ ››‎






ቲፕ ይሰጣሉ ? ከሰጡ ውስጥዋ የሚቀር አሳማኝ ምክንያት አለ ? ወይስ ስለዚህ ጉዳይ በአንክሮ አስበው አያውቁም ፡፡ ምናልባት አንዳንድ ምክንያቶቸን ላስታውስዋ….

1 . አስተናጋጆች አነስተኛ ደመወዝ ስለሚከፈላቸው
2 . አስተናጋጆች መልሱን በዕቃ ስለሚያቀርብልዋትና የዕቃው ራቁትነት ስለሚያሳፍርዋት
3 . ለሚያገኙት ሸጋ መስተንገዶ ክብር መግለጫነት
4 . ለትውውቅ ወይም ለጠበሳ
5 . ሌሉች ሰዋች ስለሚያደርጉት
6 . ክፉ አይደለሁም የሚል ማስታወቂያ ለማሰራት
7 . ሃይማኖታዊ መርህን ለማስከበር

በርግጥ ከዚህ የተለየም  ምክንያት ሊኖርዋት ይችላል፡፡ ቲፕ ቅርጽና ይዘቱን ሳናወዳድር ጥንትም እንደነበር አንዳንድ ድርሳናት ያስረዳሉ፡፡ የእቴጌ ምንትዋብ ልጅ የሆነው ዳግማዊ እያሱ በስልጣን ዘመኑ ትምህርትን የተመለከተ ቲፕ ነበረው፡፡
ዳግማዊ እያሱ በአንድ ወቅት ‹‹ መማር የሚፈልግ ሁሉ በነጻ ከቤተመንግስት መመገብ ይችላል ›› የሚል አዋጅ አስነገረ ፡፡

ለመሆኑ እያሱ ቲፕ ለመስጠት ምን አሳሰበው?
መመዘኛው ምንድነው?
ቲፑን ለነማን ሰጠው?
እነሆ እያሱ እንደሚከተለው ተናገረ ፤

 ማንም ሰው በትምህርቱ ወደፊት ገፍቶ ከተወሰነ ደረጃ ላይ ሲደርስ፣ ይበልጥ በተሟላ ገበታ ላይ በክብር ተቀምጦ  መመገብ ይፈቀድለታል !!!

 ተራ ምግብ የሚሰጣቸው ማንበብና መጻፍ ብቻ የሚችሉ ናቸው !!!


በሳይንሳዊ ጥናቱ  ቀጥሎ ወዳለው ደረጃ የተሸጋገረ ሁሉ ከመደበኛው ማዕድ ጋር ጠላ ይሰጠዋል !!!

ነገር ግን በእውቀቱ ከላቀ ደረጃ ላይ የደረሰ ሰው፣ ለምሳሌ ቅኔ ከተቀኝ፣ ከምግብ ጋር ጠጅ ይቀርብለታል !!!

የቅኔን ሳይንስ ጨርሶ ወደ መጻህፍት ጥናት የተሸጋገረ ሁሉ የመጨረሻው ምርጥ ማዕድ ይቀርብለታል !!!

እንደሚታወቀው በቀድሞው  የኢትዬጽያ ባህል መሰረት ጠጅ ለመጠጣት የሚፈቀድላቸው በህብረተሰቡ ውስጥ ከፍ ካለ የታዋቂነት ደረጃ ላይ የሚገኙ ብቻ ናቸው፡፡

ባለንበት ዘመንም ጥሩ የሰራ ይሸለማል የሚል መፈክርን የያዙ ቲፕ መሰል ጥናቶች ብዙ ጊዜ ይፋ ሆነዋል፡፡ በጣም ጥቂቶቹ ይጠቀሱ ቢባል እንኳን ወንድማማቾቹን ቢፒአርና ቢኤስሲን እማኝ ማድረግ ይቻላል፡፡
እነሆ መንግስት እንደሚከተለው ተናገረ፤

የውጤት ተኮር ስርዓትን ያለምንም ማበረታቻ ተግባራዊ ለማድረግ መሞከር የሰራተኛውን ተነሳሽነት የሚያዳክምና የተቋሙን አፈጻጸም የሚጎዳ ነው፡፡ በዚሁ መሰረት ከአማካኝ አፈጻጸምና በላይ የሚገኙ ሰራተኞች የተለያዩ መጠን ያለው ማበረታቻ ክፍያ ያገኛሉ፡፡ ቢኤስሲ መ/ቤቶችን ያጥለቀለቀ ቢሆንም ትጉሃን ግን እስካሁን አልተሸለሙም ፡፡

ለመሆኑ መንግስት ቲፕ ይውቃል ?
ካወቀ ቲፕ ይሰጣል ?
ከሰጠ መቼ ይሰጣል ?
እረ ለመሆኑ እንዴት ይሰጣል ?
እኮ ለነማን ይሰጣል ?
ውስጡ ያለው አሳማኝ ምክንያት ምንድነው ?
ልክ ከላይ በዝርዝር እንደገለጽነው ‹‹ እንደ እኛ ›› እያነጻጸራችሁ የምትመልሱ ከሆነ ብዙ ፈገግታ አጫሪ ምላሾች ብቅ ጥልቅ እንደሚሉባችሁ አሰብኩ፡፡

ለምሳሌ በተራ ቁጥር 4 ዓይን ካሰባችሁ ‹‹ ሰዋች እሱን መስለው ሲተዋወቁት ወይም ሲጠብሱት ›› የሚል ምላሽ ታገኛላችሁ፡፡ ከፈለጋችሁ በዚሁ ስሌት ቀጥሉ…….

እረ የቲፕ ያለህ !!!!
እረ የጠላ ያለህ !!!!
እረ የጠጅ ያለህ !!!!
እረ የማዕድ ያለህ !!!!
ለመሆኑ ቲፕ ምንድነው ???????????????????????