Tuesday, March 25, 2014

ወደ ባልዲው ነዎት ወደ ተራራ ?


እህል ውሃዬ አዲስ ዘመን በነበረ አንድ ቀን ድድ ማስጫ የምንላት ቦታ ላይ ገሚሳችን የተበላሹ ሞተር ሳይክሎች ወገብ ላይ ፊጥ ብለን  ሌሎች እንደቆሙ ክፉ ደጉን እንቀድ ነበር ። አንዱ ደራሲ ወደቢሮ እየመጣ ነው ። ቢሮ ለመግባት ድድ ማሰጫውን ማለፍ አለበት ። ለካስ አንዱ ደራሲ አትኩሮ እየተመለከተው ኖሯል « እዩት እስኪ » አለን በአገጩ ወደ ሰውየው እየጠቆመን « የተገለበጠ ኤሊ አይመስልም ? » ያልጠበቅነውን ተረብ መሃላችን ዘረገፈው ። በአንድ በኩል ድንጋጤ ቢወረንም በአካባቢው ታላቅ ነውጥ የፈጠረውን ሳቅ መቆጣጠር አልቻልንም ። የተበላሹት ሞተሮቹ ሳይቀሩ ሲንተፋተፉ ተሰማ ።
እኔን በወቅቱ የገረመኝ እንዴት አሰበው ? የሚለው ጥያቄ ነበር ። መጀመሪያ ኤሊዋን አመጣት ፣ ይህ አልበቃው ብሎት ገለበጣት ። የተረገመ ! ከዚያ በኃላማ ለተወሰነ ግዜ ተቸግሬ ነበር - ሰውየውን ባየሁት ቁጥር ምስሉ እየመጣብኝ ። ዛሬ አንደኛው በኢትዮጽያ ምድር የለም ፣ ሌላኛው በመላው ዓለም አይገኝም ። ፓ ! ሁለቱም ታዲያ ምርጦች ነበሩ ።
አዲስ ዘመንን « የስጋ መጠቅለያ » እያሉ ቁምስቅሉን የሚያሳዩት ጸሀፊዎጭ ይኀው ተረብ አላጠግብ ብሏቸው አንዱን ደራሲና ባልደረባችንን « ወደ ስምንተኛው ገጽ ይዞራል ፊት » ማለታቸውን የሰማንና ያነበብን ግዜም እንዲሁ ለአንድ ሳምንት በሳቅ ተንፈቅፍቀናል - ሞራል ቢገርፍም መሳቅ ጥሩ ነው በሚል ። የጥንት ቻይናዊያን የሰው ልጆችን ፊት በመመልከት መተረብ ብቻ ሳይሆን ውስጣዊና ውጫዊ ባህሪያትንም ይተነትኑበት ነበር ። ንጉስ ሲን - ቺ - ዋንግ / 221 BC / ፊትን የማንበብ ጥበብ ተጽዕኖ አሳድሮበት እንደነበር ድርሳናት ያስረዳሉ ። የፈት ቅርጾች በስያሜ ተከፋፍለው የተቀመጡ ሲሆን አጠቃላይ የሆነ ምንባብም አላቸው ። ይህ አጠቃላይ ምንባብ የሚዘረዘረው ደግሞ ፊት ላይ ያሉት አነስተኛ አካላት ሲመረመሩ ነው ። በዚህ ረገድ ግንባር ፣ ሽፋሽፍት፣ አይን ፣ አፍንጫ፣ ጥርስ ፣ ጉንጭ ፣ ከንፈር ፣ ጀሮና አገጭ ምን ሲመስሉ ምን እንደሆኑ የሚያብራሩ ብይኖች ተቀምጠዋል ። ለምሳሌ በጋዜጠኞችም ሆነ በኪነጥበብ ሰዋች ብዙ ያልተዘመረለት ሽፋሽፍት ስስ ሲሆን ምን ማለት ነው ...  ወፍራም ሲሆንስ ? ሲራራቅ ... ሲገጥም ? የጨረቃ ቅርጽ ሲይዝ ... ትሪያንግል ሲመስል ? ቀጥ ሲል ... ሲንጨባረር ? ወደላይ ሲሰቀል ... ወደታች ሲደፋ ? አንድም እንዲህ የሆነበት አንድም ያዘለውን ትርጉም ለቀቅ ባለ መልኩ ያጫውቱናል ። ሌሎቹንም እንዲሁ ።
ይሄን ሁሉ የሚያወራውን መጽሀፍ  ያነበብኩት ባለፈው ሳምንት ነው ። ከዚያ በፊት ቤንጃሚን ዚፋኒያ የተባለ ጸሀፊ የኤርትራና ኢትዮጽያ ዜግነት ያለው የአንድ ቤተሰብ ቡድን በባድመ ጦርነት በሁለቱም ሀገሮች መንግስትና ህዝብ የደረሰበትን ድርብ ሰቆቃና ፈታኝ ህይወት በሚያስተክዝ መልኩ Refugee Boy በሚል ርዕስ ጽፎት አንብቤው ድብርት ወስጥ ነበርኩ - ግሩም ስራ ነው ።  ቀጣዩ መጽሀፍ ይህን የሚኮሰኩስ ስሜት ነበር በፈገግታ ብሩሽ ማሰማመር የቻለው « The Secret Language of Your Face » ይባላል ። ፈልገው ቢያነቡት ይዝናኑበታል ። ራስዎትንና ጔደኞችዎን መስታውት ውስጥ በማስገባትም ማነጻጸር ይችላሉ ። ያለማመን መብትዎ እንደተጠበቀ ሆኖ ማለት ነው ። ለዛሬ ግን መጽሀፉ ስለፊታችን የሚለውን ብናነብስ ?
ጨረቃ ፊት ፣

ትልቅና ክብ ጭንቅላት አላቸው ። የጨረቃ ፊት ያላቸው ሰዎች ልፍስፍነት ፣ ንቁ ተሳታፊ ያለመሆንና እንደነገሩ መልበስ ይታይባቸዋል ። ብዙ በመብላትና በመጠጣት ደስታን መፍጠር ይፈልጋሉ ። ደረጃቸው ዝቅ ያሉ ምግቦችን ሁሉ በመውሰድ የሚታወቁ መሆኑ ብዙ ሊያስገርም አይችልም ። ያገኙትን ገቢ በማድረጋቸው የኃላ ኃላ ለአስቸጋሪ ክብደት መጨመርና ዘርጣጣነት  ይዳረጋሉ ።
ልዩ ክህሎታቸው ከሰዎች ጋር በሚያደርጉት ግንኙነት ዲፕሎማት ሆነው መፈጠራቸው ነው ። በስራ ረገድ ወንዱ ጨረቃ ፊት ጥሩ የንግድ ሰው ይወጣዋል ። ፈጣን የገበያ ልውውጥና ውጤት በሚያሳዩት አይነቶቹ ስራ ላይ እንጂ ትላልቅ ስራዎች ውስጥ ኃላፊነት ወስደው ለመግባት ጠርጣራ ናቸው ። ሴቷ ጨረቃ ፊት በስራ ረገድ ግዴለሽነት ይታይባታል ። ጥቅሞቿን በመከታተልና በመቆጣጠር ረገድ ዝንጉ ናት ፣ የዚህም ዋናው ምክንያቱ ስለራሷ ለማሰብ ረጅም ግዜ የምታጠፋ በመሆኑ ነው ። ስለሆነም ከፍ ባለ አስተዳደራዊ ስራ ላይ ለመገኘት አትችልም ።
ከግል ህይወት አንጻር የተናጥል ኑሮን መምራት ያስደስታቸዋል ። ወንዶቹም ሆነ ሴቶቹ እስከ አርባዎቹ ድረስ ትዳር ላይዙ ይችላሉ ። የዚህ መነሻው ደግሞ በወጣትነት ግዜያቸው ተቃራኒ ጾታን ችላ ብለው ማሳለፋቸው ነው ።
ብረት ፊት ፣
ሁለት አይነት ብረት ፊቶች አሉ ። አንደኞቹ አጭር ፊትና የሞላ ጉንጭ ያላቸው ናቸው ። አነዚህኞቹ ጤናቸው የማያስተማምን ሲሆን በተለይም በሆድ ችግር ይጠቃሉ ። ሁለተኞቹ ረጅም ፊት ያላቸው ሲሆን ቁመታቸውም ከስድስት ኢንች ሊበልጥ ይችላል ። በባህሪ ረገድ ራስ ወዳድነትና ከነገሮች ጋር አብሮ ያለመሄድ እንከን ይታይባቸዋል ። ብረት ፊቶች ለፍትህና ትክክል ነው ብለው ላለመኑበት ጉዳዮች መስዋዕትነት ከመክፈል ወደ ኃላ አይሉም ። ራሳቸውን እንደማስገረምና ማስደነቅ የሚያስደስታቸው ነገር የለም ። ሌላው ቢቀር ሰዎችን ሰብሰብ አድርገው በቀልዶቻቸው እንዲደሰቱ ማድረግ ያስፈነጥዛቸዋል ።
ጥሩ የሚባል እውቀት ቢኖራቸውም ራሳቸውን የሚመሩት በደመነፍስ ነው ጥሪታቸውን ያለስጋትና ፍርሃት እንዴት ማዋል እንደሚገባቸው ቢያውቁም አሁንም የሚያዳምጡት እውቀታቸውን ሳይሆን ደመነፍሳቸውን ነው   ፖለቲከኛና የህግ ሰው የመሆን ዝንባሌያቸው የላቀ ነው ። በአማካኙም ይህን የመሰለ ፊት ያላቸውን ሰዎች ፍርድ ቤቶችና ፓርላማ አካባቢ መታዘብ ቀላል ነው ።
ጄድ ፊት ፣

የተመጣጠነና አይን ግቡ የሆነ ገጽታ ያላቸው ሲሆን ጉንጫቸው አካባቢ የክብነት ቅርጽ ይታይባቸዋል ። ሴት ጄድ ፊቶች ከአንድ በላይ የሆነ መታጠቢያ ክፍል እንዲኖራቸው ቢፈልጉ አይገርምም ። ምክንያቱም ክፍሎቹ ቁንጅናና ስነውበትን የሚያደምቁ ቁሳቁሶች የሚሞሉበት ስለሆነ ።
እነዚህ ሰዎች ለህይወት ያላቸው አመለካከት ቀናማ ሲሆን ስሜታቸውን በፍጥነት ለማሳየት ወደኃላ አይሉም ። ሴቶቹ ትልቅ ትጋትና ጥረት ስላላቸው በማህበራዊ ህይወት ውስጥ ከፍ ያለ ቦታ ይደርሳሉ ። ይሁን እንጂ ማህበረሰቡ እብሪተኛ ወይም ይሉኝታ ቢስ በሚል ያልተገባ ሀሜት ያቆስላቸዋል ። ጄድ ፊቶች በስራ ረገድ ከፍተኛ ችግርና ውጤት ሲያጋጥማቸው እንኴ ተስፋ አይቆርጡም - እድሜ ለጠንካራ አቅማቸው ።
ወንድ ጄድ ፊቶች ከፍተኛ የሆነ የሀገር ፍቅር ስሜት አላቸው ። ለዚህም ይመስላል ብዙዎቹ በመከላከያ ሰራዊት ውስጥ የሚገኙት ። የፍቅር ግንኙነትን በተመለከተ ተጣማሪያቸው ከፍተኛ ፍቅርና እንክብካቤ እንዲያደርግላቸው ይሻሉ ። ይህ ፍቅራዊ ስሜት ካልተሟላ ሀዘናቸው ወዲያው ነው የሚታየው ።
ባልዲ ፊት ፣
 
ባልዲ ፊቶች ውሃ ፊትም በመባል ይታወቃሉ ። የሰፊ ግንባርና ትኩረት ሰራቂ አይን ባለቤት ናቸው ። ያላቸውን እውቀት በመጠቀም የሚከበር ውጤት ይጨብጣሉ ። ይሁን እንጂ በሀዘንና ትካዜ የተከበበ ህይወትም ይኖራሉ ፣ በዚህ ወቅት ውጤታማነታቸው በፍጥነት እያሽቆለቆለ ይወርዳል ። ከዚህ አሉታዊ ስሜት ውስጥ ለማውጣት የሚታገል ሰው ቢኖር እንኴ  ጥረቱ በቀላሉ እውን የሚሆን አይደለም ።
በቅርብ ጠጋ ብሎ ውስጣቸውን ለመረዳትም ረጅም ግዜያትን ይጠይቃል ። ባልዲ ፊቶች ብዙ ጔደኞች አሉን ብለው ቢያስቡም ይህን ጥበብ ወደላቀ ደረጃ ለማድረስ ከሌላቸው አቅም ጋር ብዙ ግዜ ይጋጭባቸዋል ። ሴቶቹም እንዲሁ የፈጣሪነት ጸጋ የተላበሱ ናቸው ። ይህን ጸጋ በትክክል መጠቀም ከቻሉ በተለይም መድረክ ላይ በሚሰሩ ስራዎች ስመጥር ሊሆኑ ይችላሉ ።
ፋየር ፊት ፣

እንቁላል የመሰለ ጭንቅላት ፣ ሰፊ ግንባርና የሾለ አገጭ አላቸው ። እውቀታቸው የላቀና አስገራሚ ነው ። ባህሪያቸውም ተለዋዋጭ ነው ። ብዙ ግዜም በበርካታ ሀሳቦች የሚንተከተኩ ሲሆን ወደ ተግባር ለመለወጥም ጥረት ያደርጋሉ ።
የበርካታ አዎንታዊ ዝንባሌ ባለቤቶች ቢሆኑም ሁልግዜም ከመጥፎ ሰዎች ጋር በጔደኝነት ይወድቃሉ ። ይህም የሚሆነው ሰዎችን የሚያነቡት በውጫዊ ገጽታቸው ብቻ በመሆኑ ነው ። ከፍተኛ ችግራቸው ግን እፍረት የማያውቀው የማጋነን ባህሪያቸው ነው ። ፈጣን ብቃት ቢኖራቸውም አንዳንዴ የስልጣን ረሃባቸውን በግልጽ እስከማየት ሊደርሱ ይችላሉ ።
ፋየር ፊቶች የፍቅር ስሜታቸውንና ምኞታቸውን በመግለጽ ረገድ ችግር ያጋጥማቸዋል ። ይህን በቅጡ ከመረዳት ይልቅ በፍቅር ህይወት ረጅም ግንኙነት የሚያሳልፉት ሌሎች ናቸው በማለት እድላቸውን ይወቅሳሉ ። ይሁን እንጂ ዘግይተውም ቢሆን ጥልቅ ፍቅር እንዲያጡ መሰረት የሚሆናቸው የራሳቸው ተጠራጣሪነት መሆኑን ይቀበላሉ ።
መሬት ፊት ፣


ግንባራቸው ጠበብ ብሎ ጉንጭ አካባቢ ሰፋ ይላሉ ። መሬት ፊቶች ምስቅልቅል ባለ አቌም የሚገለጹ ናቸው ። በመጠኑም ቢሆን በፍቅር እጦት ያደጉ በመሆኑ ሊሆን ይችላል ። አክብሮት የማያሳዩ ሲሆን ምላሽ የሚሰጡትም ስርዓትን በጣሰ መልኩ ነው ። አንዳንዴም ስድብንና ኃይልን ከመጠቀም ወደ ኃላ አይሉም ። በዚህም ምክንያት ብዙ ግዜ ጔደኝነትን ለመመስረት ይቸገራሉ ።
ሊጠቀስ የሚችለው አዎንታዊ ባህሪያቸው ታላቅ የእውቀት ጥማት ያለባቸው መሆኑና ይህን ችሎታ በተግባር ለማስደገፍ በትዕግስት የመጠበቅ ዝግጁነታቸው ነው ። መሬት ፊቶች ከተጣማሪያቸው ጋር ያላቸው ግንኙነት በግንፍልተኝነት የሚገለጽ ነው ።  ብዙ ግዜም በሰላም አውለኝን ከመግለጽ ይልቅ በቁጣ አለመስማማትን መግለጽ እለታዊ አጀንዳቸው ይመስላል ። ነገር ግን ሁለት ተቃራኒ መሬት ፊቶች በፍቅር የሚወድቁ ከሆነ አለምን ለመቀየር አያመነቱም ።
ግድግዳ ፊት ፣

ከግንባራቸው እስከ አገጫቸው ያለው ርቀት በጣም አጭር ነው ። ነገር ግን ፊታቸው ከጃልሜዳ ይዛመዳል - ሰፊና ደልዳላ ነው ። በል ያላቸው ግዜ ጠንክረው ይሰራሉ ። ነገር ግን ገልጃጃ የሚመስለው ጠባያቸው ወደ ስንፍናና ጭንቀት እንዲያመሩም ተጽዕኖ ይፈጥራል ። ለምሳሌ ጠንካራ ችግር በገጠማቸው ግዜ ራሳቸውን መቆጣጠር አይችሉም ። ይህም ነገሮችን ጠርጣሪዎች በመሆናቸው የሚፈጠር ሲሆን ትዕግስት አልባም ይሆናሉ ።
እንደዚህ አይነት ሰዎች ሃሳባቸውን ወደ ተግባር የመለወጥ ችሎታ ያንሳቸዋል ። ግድግዳ ፊቶች በፍጹም ባለስልጣን መሆናቸው ጥቅም የለውም ። ይሁን እንጂ በአንድ የሆነ ምክንያት ውስጣቸው ያለውን አቅም ጥቅም ላይ ማዋል ከቻሉ በጣም ታዋቂና የመገናኛ ብዙሃን ከከቦች ነው የሚሆኑት ።
በቤተሰብ ውስጥ ችግር ከተፈጠረ በአክብሮት የሚበረከተው ቀይ አበባም ሆነ ፍቅሩ እንዳይሞት የሚደረጉ ቃል የመግባት ስርዓቶች የተጋረጠውን አደጋ ፈቀቅ አያደርጉትም ። ግድግዳ ፊቶች ያለውን ግንኙነት ጠግኖ ወይም አጠናክሮ ጥቅም ላይ ከማዋል ይልቅ በእድላቸው በማለቃቀስ ሌላ ፍቅረኛ መፈለግን ይመርጣሉ ።
ተራራ ፊት ፣

ግንባራቸው ወደ ላይ እየጠበበ የሚወጣ ሲሆን በተቃራነው ጉንጫቸው ከመሬት ፊቶች የበለጠ ሰፊ ነው ። በወጣትነት ዘመን ያሳለፉት ግዜ ብዙም አርኪ ባለመሆኑ ፣ ከቤተሰብ ጋር የነበራቸው ቁርኝት ልል ስለነበር እንዲሁም በአቅም ውስንነታቸው ምክንያት የረባ ጔደኝነት ለመመስረት ሲያስቸግራቸው የቆየ ነው ።
ደካማ ጎናቸውን የሚቀበሉ ከሆነ ግን ውጤታማ ለመሆን ቅርብ ናቸው ። ለሚሰሩት እያንዳንዱ ነገር ክብርና ዋጋ ይፈልጋሉ ። ጠብ ጫሪታቸው ግን እንደ ማስታወቂያ አደባባይ የወጣ ነው ። በማህበራዊ ተሳትፎ ውስጥም የሚገኙት በጣም ውስን በሆነ ግዜ ነው ። ገለልተኛ መሆን ይፈልጋሉ ። በተለይም ሀሜትን ለመራቅ ጥረት ያደርጋሉ ። ተራራ ፊቶች ወደ ግንኙነት የሚገቡት በገንዘብ ድጋፍ ቃል ሲገባላቸው ብቻ ነው ።
ያልተመዛዘነ ፊት ፣

ብዙ ሰዎች ያልተመዛዘነ የፊት ገጽታ አላቸው ። ለምሳሌ ያህል ግማሹ የፊት ገጽታ ከሌላኛው ረጅም ወይም ሰፊ ሊሆን ይችላል ። ወይም ደግሞ አፍ ወይም አፍንጫ የተጣመመ ይሆናል ። ቻይናዎች ያልተመዛዘነ የፊት ቅርጽ ውጫዊ ማንነትን ብቻ ሳይሆን የውስጣዊ ገጽታችንም መስተዋት ነው ባዮች ናቸው ።
ያልተመዛዘነ ፊት ያላቸው ሰዎች ከፍተኛ የሆነ የፋሽን ፍላጎት አላቸው ። ገንዘብ ያባክናሉ ። ስራቸውን ግን በአግባቡ ያከናውናሉ ። የተዝናና የፍቅር ህይወት መምራት የትርፍ ግዜያቸው አቢይ ተግባር ይመስላል ። በቀላሉ ከተቃራኒ ጾታዎች ጋር መግባባት ይችላሉ ። አንዱ ቢያልቅ ወይም ባይሳካ እንኴ ቀጣዩን ለመያዝ ብዙ አይቸገሩም ። ደሞ ለሴት ... ደሞ ለወንድ የሚሉ አይነት መሆናቸው ነው ። ይሁን እንጂ ማንኛውም ሰው ሌላው ቀርቶ ራሳቸው ያልተመዛዘኑ ፊቶች ጋብቻ ለምን እንደማይሳካላቸው ወይም ለምን እንደማይስማማቸው አያውቁም ።
እህስ የለመዱትን አይነት ገደል ፊት ፣ ጅብ ፊት ፣ ጨ ፊት ፣ ፈረስ ፊት ወዘተ አላገኙትም ወይስ ተጠማዞ ነው የመጣው ? እስኪ ፊትዋን አትኩረው ይመልከቱት ... ማንም ቦሃቃ ፊት ተነስቶ ሽልጦ ወይም ተራራ ፊት ቢልዋት ፊትዋ ለራስዋ የማይጠገብና ውብ ነው ...


Tuesday, March 11, 2014

እረኞቹ ምን እያደረጉ ነው ?





ፓሰተር የሚለው ቃል ምንጩ ላቲን ሲሆን ትርጔሜውም ጠባቂ ወይም እረኛ ማለት ነው ። እረኛ የሚለው ቃል በመጽሀፍ ቅዱስ ውስጥ 27 ግዜ ተጠቅሷል ።
በሀዲስ ኪዳን መጻህፍት ውስጥም በተለይም ወደ ኦፌሶን ሰዎች/ 4 ፡ 11 / በሀዋርያት ስራ / 20 ፡ 28 / እና የጼጥሮስ መልዕክት / 5 ፡ 2/ ላይ ፓስተር የሚለው ቃል ከመምህርነት ጋር ተያይዞ ቀርቧል ማለት ያስደፍራል ። ለአብነት ያህል በሀዋርያት ስራ ላይ « የእግዚአብሄርን ቤተክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጻጻሳት አድርጎ ለሾመበት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ » የሚለውን ጥቅስ እናነባለን ። በሌሎቹ ጥቅሶች ላይ ደግሞ መንጋውን ጠብቁ የሚላቸው ሽማግሌዎችንና አስተማሪዎችን ነው ።
ዞሮ ዞሮ በፈጣሪ ትልቅ ቦታ የተሰጣቸው ቄሶችም እንበላቸው ፓስተሮች የእግዚአብሄርን መንጋ እንዲጠብቁ ከፍተኛ ኃላፊነት ተጥሎባቸዋል ። በጼጥሮስ መልዕክት ምዕራፍ 5 ላይ ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ የሚለውን ሀረግም ለዚህ አባባላችን ማጠናከሪያ መጠቀም እንችላለን ። ታዲያ እረኞቹ ምን እያደረጉ ነው ? እያስተማሩም እየተመራመሩም ... እያገዱም እያንጋደዱም ይመስላል ። በተለይ በአንዳንዶቹ ላይ
አፈንጋጭነት ፣
ራስን ቅዱስ አድርጎ መሾም
እና ያልተገባ ተግባር መፈጸም በተደጋጋሚ እየታየ ነው ። የጥቂት ወራቶችን ጥቂት አስገራሚ አብነቶችን እየመዘዝን ለምን ቆይታ አናደርግም ? በጣም ጥሩ ...
ደቡብ አፍሪካዊያኑን ፓስተር ሌሴጎ ዳንኤልን እንመልከት ። በቅርቡ « እግዚአብሄርን መቅረብ ከፈለጋችሁ ሳር ብሉ » የሚል ትዕዛዝ በማስተላለፉ ጉባኤተኛው ሳሩን ሲያሻምደው ውሏል ። አንዳንዶቹ ታመው ወደ ሆስፒታል ቢሄዱም አንዳንዶቹ የፓስተሩን ተግባር ደግፈው ሲከራከሩ ነበር « የፈጣሪ ኃያልነትን ማሳያ በመሆኑ ሳር በመብላታችን እንኮራለን ፣ ማንኛውንም ነገር እናደርጋለን » ብላለች አንዲት የህግ ተማሪ
እንግዲህ ይህ ፓስተር ትዕዛዙን የፈጸመው መንፈስ ቅዱስ በራዕይ ተገልጦለት መሆኑ ነው ። በከፋ የረሃብ ዘመን የሰው ልጆች ህይወታቸውን ለማቆየት ርስ በርስ ከመበላላት አልፎ ተሞክረው የማያውቁ ስራስሮችን ለጠኔ ማስታገሻነት ሙከራ አድርገዋል ። በመጽሀፍ ቅዱስ ታሪክም እንደ በሬ ሳር እንዲበላ የተፈረደበት ንጉስ ናቡከደነጾር ነበር ። እሱም ለዚህ ቅጣት ያደረሰው ስልሳ ክንድ የሚያህል የወርቅ ምስል አሰርቶ ለምስሉ እንዲሰግዱ የታዘዘውን አዋጅ የተላለፉ ሰዎችን በግፍ በእሳት በማቃጠሉ ነው ። ስለዚህ < ሳር > የቅጣት ምልክት እንጂ የፈጣሪ መቅረቢያ ስጦታ አይደለም ። የሰው ልጅ አንጀት ሊፈጨው የማይችለውና መጠነኛ መርዛማ ባህሪ ያለውን ሳር መመገብ ሳይንስም አይቀበለውም ።
ባለሁለት እግራሙ የሰው ልጅ ቀሪውን ሁለት እግር ከእጁ ተበድሮ እንደ በግ ሳር ሲግጥ ማየት ሞራላዊና ተፈጥሯዊ ውድቀት ነው ። በዚህ ስሌት ባልታሰበ ሰዓት ሽንት እያሸተተ እንደ በግ ሲያገጥና አባሮሽ ሲጫወት ማየት ይቻላል ። የፓስተሩ የፈጣሪ መቅረብ እሳቤ ሳርን ለአንድ ቀን እንደ ስለት ጧፍ አብርቶ ለማምኖ መለያየትን ብቻ የሚያሳይ አይመስልም ። ምናልባትም ከጥቂት ወራቶች በኃላ ደፋር ነውና  « በግ » ስለሆናችሁ ቤዛነትንም እንለማመድ ብሎ ካራ ሊያስታጥቅ ይችላል ። ይህን የሚደግፍ አንቀጽ ደግሞ አያጣም ። ኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ 22 ፡ 1 – 2  እንዲህ ይላል « የምትወደውን አንድ ልጅህን ይስሀቅን ይዘህ ወደ ሞሪያም ምድር ሂድ ፣ እኔም በምነግረህ በአንድ ተራራ ላይ በዚያ መስዋዕት አድርገህ ሰዋው » ፓስተር ሌሶጎ እኔ የአብርሃም እናንተ ደግሞ የይስሀቅ ምሳሌ መሆናችሁን አትዘንጉ ካለ የህግ ተማሪዋን ጨምሮ ሌሎቹም ድጋፍ ከመስጠት ወደ ኃላ አይሉም ማለት ነው ።
የኬንያው ፓስተር ኖሂ « ሃይማኖታዊ » ግኝት ደግሞ የሴቶች አለባበስ ላይ ያተኮረ ነው ። ፓስተሩ አንድ ቀን በ « lord ‘s propeller redemption church » የሚታደሙ ሴቶች በሙሉ ፓንት ማድረግ የለባቸውም ሲል ትዕዛዝ ሰጠ ። ምክንያት ሲባል ቅዱስ መንፈስን ለማቅረብ ፣ በአጠቃላይ አምልኮ ከጭንቅላትና ከሰውነት ነጻ ሆኖ ማሰብን ስለሚፈልግ የውስጥ ቁምጣቸውን ቤት ትተው መምጣት ይኖርባቸዋል ።
የፓስተሩን ግኝት የመነሻና መድረሻ ክር ይዤ ለማገናኘት ሌት ተቀን ብማስን ውሉን ማግኘት አልቻልኩም ።
ምን ለማለት ፈልጎ ነው ?
ከምን አንጻር ተመልክቶት ይሆን ? መንፈስ ቅዱስ የህሊናችንን በር ሲያንኴኴ ቶሎ የማናዳምጠው ፓንት መጥፎ ጋርድ እየሆነ ነው ? የሚል አስመስሎበታል ። ይህ ቦታ ከነስሙ « ሃፍረተ » እንጂ « ቤተልሄም » ወይም « ጎለጎታ » አይደለም ።
ታዲያ እንዴት መረጠው ? በጣም የሚያስደንቀው ደግሞ የፓንት ማውለቁ ትዕዛዝ ወንዶችን የማይመለከት መሆኑ ነው ።
ለነገሩ የአሜሪካዊውን ፓስተር አለን ፓርከር ግኝት ብናዳምጥ የላይኛውን « እረ ይሻላል » ማለታችን ይጠበቃል ። በቨርጂኒያ የ « white tail chapel » መሪ የሆኑት ፓስተር ትዕዛዝ ደግሞ ጉባኤተኛው ስብሰባውን ራቁቱን ሆኖ እንዲከታተል መገፋፋት ነው ።
የጼጥሮስ መልዕክት ምዕራፍ አምስት « ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ » ተፈጻሚ ይሆን ዘንድም ፓስተሩ ራቁታቸውን በመሆን ትምህርት ሰጥተዋል ። እረ ጥንዶችንም ለጋብቻ ራቁታቸውን  አማምለዋል ። ከተወለድን ከጥቂት ወራት በኃላ እረኞች ለክርስትናችን ውሃ ውስጥ ፣ እናቶች ለመጪው ህይወታችን ተድላ እንጀራ ላይ ሊያንከባልሉን እንደሚችሉ ነው መረጃው ያለን ። ይኀው ቃልኪዳንም የጸና ማህተም ይፈጥርልናል ብለን ነው ተስፋ የምናደርገው ። አድገን በውሃ የተረጨነውንም ሆነ እንጀራ ላይ « ግፍ » ሳይሆንብን የተንደባለልነውን ፎቶ ስንመለከት ያረካናል ። ራቁትነት የንጹህነት ፣ የፍጥረት መነሻነት ነው ብለን ልንወስደውም እንችላለን ። በትናንት ንጹህነትና በዛሬ ተጨባጭ ማንነታችን መሃል ያለውን አንድነትና ልዩነት ለማነጻጸርም ይረዳል ።
በጉርምስና እና በጉልምስና ወቅት ራቁታችንን የምንቀበለው ቃልኪዳን ልብስ ለብሰን ከምናደርገው ጋር በምን እንደሚለያይ ግልጽ አይደለም ። ተምሳሌትነቱም ስውር ወይም ድፍን ነው ። በራቁትነት ለመደናነቅ ከሆነ ባልና ሚስቱ በመኝታ ፣ በሻወር በወዘተ ግዜ የሚያገኙት ነው ። ይህን ለማድረግ ደግሞ አይተፋፈሩም ። ህግ የተላለፉት አዳምና ሄዋን የደረሰባቸውን የእፍረት መሸማቀቅ ይሄ ትውልድ ያካክሰዋል ነው የሚሉት - ፓስተሩ ? በጋብቻ ማግስት እየፈረሰ ያስቸገረውን ትዳር ለማጽናት ይሄኛውን ዘዴ እንሞክረው ነው የሚሉት - እረኛው ?
የኚህ ፓስተር ግኝት ሁለት መሰረታዊ ጉዳዮችን የሚዳስስ ነው ። የመጀመሪያው  ጉባኤተኛው ሁሉ ራቁቱን መማር ከቻለ ሁሉም የሰው ልጆች እኩል መሆናቸውን ያሳያል የሚል ነው ። ርግጥ ነው ሰዎች በሚለብሱት ፣ በሚያጌጡበትና በሚጠቀሙባቸው ዕለታዊ ቁሶች የኑሮ ደረጃቸው ሊገመት ይችላል ። ችግሩ ይኀው ጉዳይ የሰዎችን ውስጣዊ ማንነት ፣ ጥንካሬ ፣ ባህሪ ፣ አስተሳሰብ እና ፍልስፍና በፍጹም ሊያሳይ አለመቻሉን ፓስተሩ የተረዱ አለመምሰላቸው ነው ወይም ባላወቀ ተራምደው ማለፋቸውም ይሆናል ።
ሁለተኛው መነሻቸው ቤተክርስቲያን በምሳሌ ማስተማር ይኖርባታል ከሚል ሀሳብ ይመነጫል ። ክርስቶስ ሲወለድም ሲሰቀልም ራቁቱን ነበር ያሉት ፓስተሩ ፈጣሪ በዛ መልክ ካሳየን እኔ እንዴት ነው ስህተት የምሆነው በማለት ሲኤንኤንን ሞግተዋል ። በርግጥ እድሜ ለአዳምና ሄዋን እንጂ ዛሬ የሰው ዘር በሙሉ መላመላውን ነበር ታች ላይ የሚለው ። ሆኖም እንደ ፓስተር አለን በመምህርነቱ የሚታወቀው እየሱስ በገጠር ፣ በከተማ ፣ በመንደር ፣ በገበያ ስፍራና በመስበኪያ ቦታዎች ሁሉ እየተዘዋወረ ያስተማረው ራቁቱን ሆኖ አይደለም ።
ሌላው ችግር ራቁት ሆኖ ትምህርት መማርና ማስተማር ከባድ ፈተና ላይ በግድ የመውደቅ ያህል መቆጠሩ ነው ። አእምሮ ከምዕራፍና ቁጥሮች ይልቅ ቅርጽንና ከርቮችን ማጥናትና ማድነቅ ላይ ማተከሩ ሳይታለም የተፈታ ነው ። የአካል ንኪኪ ባይፈጠር እንኴ በሃሳብ መመኘትን ለማስቀረት ምን ዋስትና አለ ? እና ራቁትነት ከሌሎች ለመለየትና ጀብዱ ለመፍጠር ካልሆነ በስተቀር ዘለቄታዊ መፍትሄ ነው ብሎ መስበክ ወንዝ የሚያሻግር አይደለም ።
ናይጄሪያዊው ፓስተር ኬንዲ ቦሉዋጂ ያደረገው ምርምር ደግሞ ከፓንት ነጻ በሆነው የሴት ልጅ ብልት ላይ ነው ። ለምርምሩ የተጠቀመባቸው ቁሶች የተፈጨ ጨው ፣ መሃረብና ጸሎት / ድግምት / ናቸው ። የዚህ አይነቱ ፓሰተሮች የሚሰሩትን ውስብስብ ጥናት « pastorization » ብሎ መጥራት ሳይቻል አይቀርም ። ፓስቸራይዜሽን እና ፓስተራይዜሽን ይቀራረቡ እንጂ አይመሳሰሉም ። 
እንደሚታወቀው ፓስቸራይዜሽን ከፈረንሳዊው ቀማሚና ማይክሮ ባዮሎጂስት ሉዊስ ፓስተር ተግባር ጋር የተያያዘ ነው ። በክትባትና እርሾ ዙሪያ ትልቅ ስራ የፈጸመው ሉዊስ ወይን ፣ ቢራና ወትት እንዲቆመጥጥ በሚያደርገው ባክቴሪያ ላይም አንድ ግኝት አፍልቌል ። ባክቴሪያውን ለማጥፋት ፈሳሹን በጣም ማሞቅ ፣ ቀጥሎም በጣም ማቀዝቀዝ የሚለውን ሂደት ነበር ያበረከተው ። ይህም ሂደት « ፓስቸራይዜሽን » ለሚለው ሳይንሳዊ ቃል መወለድ ምክንያት ሆነ ።
ፓስተር ኬንዲም እንግዳ በሆነ መንፈስ የሚሰቃዩ ሴቶች በተለይም አግብተው መውለድ ካልቻሉ ያለግዜያቸው እንደሚሞቱ አወቀ ወይም ተገለጠለት ። መንፈሱ ደግሞ ባል እንዳይገኝ ደንቃራ ይሆናል ። በዚህ ስሌት ተጎድታለች ብሎ ላሰባት አንዲት የ22 ዓመት ወጣት ሴት ጉዳዩን ያጫውታትና መፍትሄውም በእጄ ነው ይላታል ። < ከፈጣሪ በታች እናንተን ነው የምናምነው በእርሶ መጀን > ትላለች ልጅት በልቧ ። ወዲያው ፓስተሩ
 < ያዝ እጇን
  ዝጋ ደጇን >
የተባለውን ኢትዮጽያዊ ዘፈን ተተርጉሞ የሰማው ይመስል ወጣቷን አስገብቶ ክፍሉን ይጠረቅምና  ለምርምሩ ይዘጋጃል ። በገቢር አንድ ልብስዋን አውልቃ እርቃኗን ቁጭ እንድትል ተደረገች ። በገቢር ሁለት ጸሎት ይሁን ድግምት ለደቂቃዎች ማንበልበል ቀጠለ  ። በክፍል ሶስት በነጭ መሃረብ ጨው ካወጣ በኃላ ብልቷ ውስጥ እንድታስገባው ይነግራታል ። ያልተለመደ ነገር ነውና ይተናነቃታል ፣ የሷ ፈራ ተባ ማለት ሂደቱን ሊያጔትተው ስለሚችልና ተግባሩን ለማፋጠን ይቻል ዘንድ ጣቱን ብልቷ ውስጥ ይጨምራል ። በዚህ የሚያበቃ ግን አልሆነም ። ከግራ ወደ ቀኝ ፣ ከቀኝ ወደ ግራ ማማሰል ይጀምራል ። ምናልባት ይኀው ተግባር እንደ ሊዊስ ፓስተር ባክቴሪያ ፣ ክፉ መንፈሱንም ይገድለው ይሆን ? አነጋጋሪ ጉዳይ ነው ። ግራም ነፈሰ ቀኝ  ይህ ሂደት « pastorization » ለሚለው መንፈሳዊ ቃል መወለድ ምክንያት ሆነ ብሎ መሳለቅ ይቻላል ። ዞሮ ዞሮ ፓስተር ኬንዲ ወደ ሌላ ምዕራፍ ከመሸጋገሩ በፊት በሩን ሲጠረቅም አይተው በተጠራጠሩ ሰዎች በቁጥጥር ስር መዋል ችሏል ።
አንዳንድ ፓስተሮችም ልክ እንደ እየሱስ ተዓምር መስራት እንችላለን በማለት አሳፋሪ ተግባር ከመስራት አይቆጠቡም ። በዚህ ረገድ ተጠቃሽ የሚሆነው ናይጄሪያዊው ፓስተር ፍራንክ ካቢሌ ነው ።
ራዕይ ስለታየኝ የተአምሩ ታዳሚ ሁኑ በማለት ደቀመዛምሩን ኮምቦ ሃይቅ ሰበሰበ ። ከዚያም ማቲዎስ ምዕራፍ 14ትን በመጠቃቀስ የሰው ልጅ በቂ እምነት ካለው እንደ እየሱስ በውሃ ላይ መራመድ እንደሚችል ማብራሪያ ሰጠ ። በተለምዶ ሃይቁን ለማቌረጥ የሃያ ደቂቃ የጀልባ ጉዞ ማድረግ አስፈላጊ ቢሆንም ፓስተሩ ርቀቱ አላሳሰበውም ።
መቼም በውሃ ላይ እንደባለሞተር ጀርባ እየነጠሩ መራመድ በእጅጉ አስደሳች ነገር መሆን አለበት ። ብዙዎቹ ቢሸበሩም አንዳንዶቹ መምህራቸው የውሃውን ጫፍ በጫማው ሶል እያነጠረ ብዙ ርቀት ሴሄድ ማለም ጀምረው ነበር ። ዞር እያለም እጁን ሲያውለበልብላቸው ለማጨብጨብ ፣ ለማፏጨትና እልልታቸውን ለማቅለጥ ተቁነጥነጥዋል ። ምናልባትም ጫፍ ደርሶ ከመጣ በኃላ ተሰብሳቢውን ለጉዞ ሲጋብዝ ፍርሃት በማየቱ « እናንተ እምነት የጎደላችሁ ስለምን ትጠራጠራላችሁ ? » እንደሚላቸውም ከማሰብ ወደ ኃላ አላሉም ።
እውነት ነው ፓሰተሩ ጉዞ ጀመረ ለማለት እንኴ ይከብዳል ። በሁለተኛው ርምጃ ሰውነቱ ሰመጠ - በፍጹም ወደ ደቀመዛምሩም አልተመለሰም ። ምዕመናኑ በድንጋጤ ተውጠው « RIP » ለማለት እንኴ አልታደሉም ነበር ። እኔ ግን አሁን ትዝ ያለኝ የእንግሊዛዊው ገጣሚ ዊሊያም ኮስሞ ሞንክሃውስ ግጥም ነበር ። ርዕሱ There was a young lady of niger ይሰኛል ። በአምስት ስንኞች ጣጣውን የጨረሰውን ግጥም እነሆ ብያለሁ
There was a young lady of niger
Who smiled as she rode on a tiger
They returned from the ride
With the lady inside ,
And the smile on the face of the tiger .
እውነት እረኞቹ ምን እየፈጸሙ ነው ? ወዴትስ እየተሄደ ነው ? ዮሀንስ ወንጌል 10 ፡ 11 ላይ እየሱስ መልካም እረኛ እኔ ነኝ ፣ መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል ይላል ። ይህ ምሳሌ በሌሎቹም ላይ እንዲጋባ ነበር የተፈለገው ። ግን የምናያቸውና የምንሰማቸው ነገሮች ተስፋ ከመስጠት ይልቅ የሚያስፈሩ እየሆኑ ነው ። ብዙ እረኞች ተኩላና ቀበሮ ለመሆን እየቸኮሉ ይመስላል ።

« መንጋውን ለሚተው ለምናምንቴ እረኛ ወዮለት  ! » የሚለው ቃል የትኛው ትንቢት ላይ ነበር የሚገኘው ?

Friday, February 28, 2014

የባለገሩ ስነቃልና የ « አቶ አለምነው ቤት »


ንደማንኛውም መጽሀፍ በትኩረት ላንብበው ብዬ አይደለም የገለጽኩት ። < እስኪ ትንሽ በአነጋገራችን ልዝናና > በማለት እንጂ ። ድንገት ከመሃሉ ገለጥ ሳደርገው < ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል > ከሚለው ንባብ ጋር ግጥምጥም አልኩ ። < ጎሽ ይዞልሃል > አልኩት በፈገግታ - የምሳሌያዊ አነጋገር መጽሀፉን ።
እናም ከ ሀ እስከ ታች የተዘረዘሩትን አነጋገሮች እንደ ፎቶ አልበም እያገላበጥኩ መጫወት ቀጠልኩ ። የገረሙኝን መቼ ይሆን የተነሱት ይቅርታ መቼ ይሆን የተነገሩት ፣ በየትኛው አካባቢ በማለት caption ብጤ እፈላልግ ነበር ። አንዳንዶቹ ሳይታዘዙ የሰው ብብትን ኮርኩረው በግድ ሳቅ መፍጠር የሚችሉ ናቸው ። ለምሳሌ ያህል ፣
< ለሰበበኛ ቂጥ መረቅ አታብዛበት ! >
< ቢያንጋልሏት ጡት የላት ፣ ቢደፏት ቂጥ የላት ! >
< ምንም ብትሞቺ ፣ እንዴት አደርሽ አንቺ ?! >
< እግዜር ሲቆጣ በዝናብ አር ያመጣ >
< ተደብቃ ትጸንሳለች ፣ ሰው ሰብስባ ትወልዳለች ! >
< አባቴ ትንሽ ነው ፣ ብልቴ ትልቅ ነው የሚል የለም ! >
< ልጅ አባቱን ገደለ ቢለው እረ የኔ ልጅ እንዳይሰማ አለው >
የሚሉት ጋ ስደርስ ከትከት ብያለሁ ።
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ አንዳንዶቹ አባባሎች ጥያቄ የሚያስነሱ ... እንደ መጽሀፍ ቅዱስ ቃል አስረጅ የሚፈልጉ ወይም ደግሞ ሃይለኛ ማስተካከያ የሚፈልጉ ሆነው ነው ያገኘኃቸው ።
ለአብነት ያህል < ነገሩ ነው እንጂ ጩቤ ሰው አይጎዳም ! > የሚለው አባባል ድሮ ጩቤ ከጎማ ወይም ከቆዳ የሚሰራ መሆኑን ነው የሚያመለክተው ። ካልሆነ ታዲያ በአሁኑ ግዜ እንቅፋት ፣ የበዛ ሀሳብ ፣ ድንጋጤና ትንታ እንኴን ሰው ለመግደል ፍቃድ አውጥተው እንዴት ሆኖ የሾለ ብረት ሰው ለመግደል የሚያንሰው ?
< ማን ይሙት ጠላት ፣ ማን ይኑር አባት ! >
የሚለው ስነቃል የተደረሰው የእንጀራ እናት ባሳደገችው ባላገር እንደሆነ ግምት አለኝ ። አሊያማ ከአባት በላቀ መልኩ እናቱንና ሀገሩን « እምዬ » የሚለው ኢትዮጽያዊ ተቆጥረው የማያልቁ የእናት ክብር መግለጫ ግጥሞችን እንደ ዝናር ታጥቆ አይደለም እንዴ የሚዞረው ? ድንገትም
< እናቱን ለናቀ ክብሯን ላዋረደው >
መሬት ትዙርበት ጸሃይ አትሙቀው » ብሎ ሊቆጣ እንደሚችል ሁሉ መች አጣችሁት ?
< ለሰው ሞት አነሰው ! >
የሚለው አባባልስ በምንድነው የተሰራው ? በዝሆን ሀሞት መሆን አለበት ። በዚህ ሀሞት እንጀራ ፈርፍረው በግድ ያጎረሱት አንድ ሰው ክፋትንና ጭካኔን ለመግለጽ  አክ - እንትፍ ያለው ሀረግ ይመስላል ። መቼም ሞት አነሰው የሚለን እድሜ ልክ በእስር ይበስብስ ለማለት አይደለም ። ምናልባት የሚረካው ከጀግናውና ሀገር ወዳዱ አጼ ቴዎድሮስ አንድ የጭካኔ ሰበዝ መዞ ሲተገብረው ሊሆን ይችላል ። አጼ ቴዎድሮስ በደግነትና ጭካኔ ተደባልቀው የተሰሩ ንጉስ ነበሩ ። ቁጣ የንዴታቸውን ጣሪያ በሚያግለው ግዜ የሚያቀዘቅዙት የሰው እጅና እግርን አስቆርጠው ነበር - ከዛ ቁራጭህን ይዘህ ሀገር ግባ ነው ። እግር እንደ ዛፍ የሚመለመልበት ዘመን ። ለነገሩ ይህ ዘመን አልፏል ። ዛሬም ግን ሰዎች በድንጋይ ተወግረው ይሞታሉ ፣ አንገታቸው በሻሞላ ይቀላል ፣ ሰውነታቸው ተቀብሮም ከብቶች በላያቸው ላይ ይነዳል ። እዛ ያሉት አጼ ልክም ነው ህግም ነው ይሉሃል - እኛ የምንለው ያዝልን መጀን ! ነው ።
 < ሙቅ ውሃና የሰው ገንዘብ አይጠቅምም  ! >
በመርህ ደረጃ ልክ ነው ። ዳሩ ግን ጂ+1 ውስጥ እየኖሩ ጂ+6 የሚያስገነቡት ፣ ሚሊየን በሚደፍር መኪና የሚንፈላሰሱት ፣ ለልደታቸው ወይ ዱባይ አሊያም አካፑልኮ ደርሰው የሚመጡት ፣ ይህ ካልተመቸ ከፓሪስ ኬክ የሚያሰጋግሩት ልማታዊ ሀብታሞች በኑሮ ሰረገላ ከአያት ተራራ እስከ እስከ ካራማራ የሚንፈላሰሱት ስፍር ቁጥር የሌለውን የሰው ገንዘብ በጥቂት ማግኔታዊ ላባቸው በመሰብሰብ አይደለም እንዴ ? መሰለኝ እንግዲህ !
< ልጅ ቢያስብ ምሳውን ፣ አዝማሪ ቢያስብ ጠላውን ! >
ይህች አባባል ገና ድሮ ጡረታ መውጣት ሲገባት ለሰዎች በተጨመረው የስራ ዘመን ፍዳዋን ትቆጥራለች ። ለማንኛውም የዛሬ ልጅ ከአባቱ የተረፈውን ሳይሆን ከአባቱ ጸሎት በፊት አስቀድሞ የሚጎርስ ፣ እንግዳ አክብሮ ጔዳ የሚሸሸግ ሳይሆን ልክ እንደ ርዕሰ ብሄር እንግዳውን በራሱ ክፍል ውስጥ ተቀብሎ የሚያነጋግር ፣ አንዲት ምሳውን ሳይሆን ለትምህርት ቤት ከሰኞ እስከ አርብ በሁለት ሳህን ስለሚያስቌጥራቸው የምግብ አይነቶች ከፈለገ ከአረብ ቻናል ፣ እንዳማራጭም ኢቢኤስን ቁጭ ብሎ በመቃኘት  መርሃ ግብር የሚነድፍ ነው ። ስለፍቅር ፣ ስለኑሮ ውድነት ፣ ነገር ስላሰከራቸው ጎረቤቶች ፣ ስለተሸራረፉ መብቶች ፣ ስለቀበሌም ሆነ ገዢው ፓርቲ አያውቅም ብለው ፊቱ ካወራችሁ ተሳስታችኃል - ምክንያቱም በሌላ ቀን እርስዎን እንደ ዋቢ ምንጭ በመጥቀስ ለጔደኛው ወይም ለጥቁሩ እንግዳ ገለጻ ሲያደርግ ሊሰሙ ይችላሉና ።
ስለሴትነት ብዙ ተብሏል ። ጥቂቱን ብቻ እንምዘዝ ።
< ሴትና አህያ በዱላ ! >
የወረደ ነው ወይስ የተጋነነ ንጽጽር የሚባለው ?
 < ሴት የወደደ ገሃነም እሳት ወረደ ! >
የመላከ ጊዮርጊስ ?! እናቴን ? እህቴን ? ልጄን ? ሚስቴን ? ያለው ማን ነበር ?
< ሴት ካልወለደች ቌንጣ አትጠብስም ! >
በጉዴ መጣ አሉ እትዬ ዘነቡ - ባለስልጣኗን አይደለም
< ሴት በማጀት ወንድ በችሎት ! >
ወቸው ጉድ ?! ይህን የማህበራዊና ባህላዊ ልምድ ጣጣ ነው ብሎ ማለፍ እንዴት ይቻላል ? ጠንካራ ፖለቲካም ጭምር እንጂ ። ቆይ ግን የወ/ሮ ዘነቡ መ/ቤት በተለይም ሴቶችን በተመለከተው ርዕሰ ጉዳይ ምን እያሰበ ነው ? ለነገሩ እሳቸው ሰሞኑን የግበረ ሶዶማዊያን አጀንዳ ላይ ናቸው ። ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ ጻጻስ ፍራንሲስ ስለ ጌይ ምን ይላሉ ሲባሉ « እኔ ማነኝ እና ነው ይህን የምዳኘው ? » የተመድ ዋና ጸሃፊ ባንኪሙን በበኩላቸው « ግብረ ሶዶማዊያን እንደ ሁለተኛ ዜጋ ብቻ ሳይሆን እንደ ወንጀለኛም እየተቆጠሩ ነው » በማለት ኡኡ ብለው ያውቃሉ  ። ፕሬዝዳንት ሮበርቱ ሙጋቤ በአንድ ወቅት “ ግብረሰዶማዊያን ከአሳማና ከውሾች የከፉ ናቸው » ማለታቸው አይዘነጋም  ። ሚኒስትር ዘነቡ ማን ከማን ያንሳል ብለው ምን ነበር አሉ የተባሉት ? መቼም ይሄ ሁሉ የስነቃል የቤት ስራ እያለባቸው እዛ ውስጥ ከገቡ የጉድ ነው ።
< በሽተኛ ያድርቅህ መጋኛ  ! >
አሁን ነው መሸሽ ። በደጉ ዘመን በነገር ወይም በቦክስ ገጭቶት አሁን ብድሩን የሚመልስ ሰው ይሆን ? ነው ህመምተኛው ሲያቃስት ከእንቅልፉ እየተቀሰቀሰ በቃሬዛ ጤና ኬላ ማመላለስ የሰለቸው አባወራ ? ለነገሩ የአቶ ቦጋለ መብራቱ እና የወ/ሮ ውድነሽ በጣሙ ዘመድም ሊሆን ይችላል ። አቶ ቦጋለ ወጥሮ የያዛቸው የተስቦ በሽታ ለሌላውም እንዳይተርፍ ለመጋኛ ስለት የሚያቀርብ ምስኪን ገበሬ ። ወይ አጨካከን ?! በሽተኛን ፈጣሪ ይዳብስህ በማለት ያጽናኑታል እንጂ እንዴት ይለጥፉበታል ። ግድየለም እንዲህ የሚናገሩት የሰው ልጆች ሳይሆኑ የሰው ገዢዎች መሆን አለባቸው ።
እነዚህን የመሳሰሉ አነጋጋሪ ፣ ተሻሻይ ወይም ተሰራዥ አባባሎች ጥቂት አለመሆናቸውን መገንዘብ ይቻላል ። ለዚህ ለዚህ የቀድሞው ባህል ሚኒስቴር ከተፎ ስራ ይሰራ ነበር ። የአሁኖቹ እንኴ በፍላጎትና በሞያ ሳይሆን በሹመትና ሽረት ብሎም በአንሚ ደረጃ የተወከሉ ናቸው ስለሚባል  ደረትን ለመንፋት የሚያስችል መሰረት መኖሩ ያጠራጥራል ። ለማንኛውም ግልባጩ ይድረሳቸው ።
ትልቁ እውነት ግን አብዛኛው አባባል ወይም ስነቃል ዘመን ተሻጋሪ መሆኑ ነው ። በነዚህ በርካታ ስነቃል ውስጥ ያልተዳሰሰ ማህበራዊ ፣ ፖለቲካዊ ፣ ኢኮኖሚያዊ ፣ ሃይማኖታዊ ፣ ባህላዊ ጉዳዮች አለ ለማለት ያስቸግራል ። ከማጣት እስከ ማግኘት ፣ ከስንፍና እስከ እውቀት ፣ ከጅልነት እስከ ብልሃት ፣ ከፍቅር እስከ ጥላቻ ፣ ከጉንዳን እስከ ዝሆን ፣ ከሸፍጥ እስከ ታማኝነት ፣ ከክብር እስከ ውርደት ፣ ከረሃብ እስከ ጥጋብ ፣ ከልጅ እስከ አባት ፣ ከልደት እስከ ሞት ፣ ከዲያቢሎስ እስከ ክርስቶስ ፣ ከሴት እስከ አማት ፣ ከሹመት እስከ ሽረት ፣ ከፍርሃት እስከ ጀግንነት ፣ ከነጻነት እስከ አምባገነንነት .... ምናለፋችሁ ጥላሁን ገሰሰ ያልዘፈነበት ባላገሩ ያልተቃኘበት ፍልስፍና የለም ብሎ እውቅና መስጠት እንደማጋነን የሚያስቆጥር አይመስለኝም ። እያንዳንዱን ርዕሰ ጉዳይ የሚመለከቱትን ስንኞች እዚህ ገጽ ላይ ፈሰስ ባደርጋቸው እደሰት ነበር ። ብዛታቸው ግን አስፈራኝ ። ማንን መርጦስ ማንን መተው ይቻላል ።
እውነት ይህን ሁሉ የደረሰው ብዙዎቻችን ቀለም አልዘለቀውም የምንለው ባላገር ከሆነ የ < ቀለም >ጉዳይ ማጠያየቁ አይቀርም ። እውነት ይህን ሁሉ ነባራዊ እውነት በቃላት ሸብልሎ ያጎረሰን ባላገር ከሆነ < ባገረስኩ ተነከስኩ > ቢል አይፈረድበትም ።
ማነው ነካሽ ?
አሁን በቅርቡ የሚያስተዳድሩትን ባላገር ያበሻቀጡትና ያዋረዱት የአማራው ክልል ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አለምነው እውነት ባላገሩን ያውቁታል ?  ካወቁትስ እንዴት ነው የመዘኑት ? ለማለት ስለምንገደድ ነው ። ለምሳሌ ያህል ሹሙ የእውቀትና የልምድ ሀብት የሚለካው ጫማ በማድረግና ባለማድረግ ነው ብለው የተነሱ አስመስሎባቸዋል ። ከዛው ክልል የተገኙት አጼ ቴዎድሮስ ሀብት ሳያንሳቸው ጫማና ኮፍያ ማድረግ አይወዱም ነበር ። ጀግንነትና የሀገር ፍቅር ከባዶ እግር ጋር አይያያዝም ። አበበ ቢቂላ በሮም የኦሎምፒክ ውድድር ያሸነፈው 11 ቁጥር ማሊያና ቁምጣ አድርጎ እንጂ ጫማ ተጫምቶ አልነበረም ። ማራቶን ከጽናትና ጥበብ ጋር እንጂ ከባዶ እግር ጋር ግንኙነት እንደሌለው ሌላ ማሳያ ሊሆን ይችላል ። ርግጥ መንገዱ በማይመችበት ቦታ ተጽዕኖ ሊፈጥር እንደሚችልም ግምት ውስጥ በማስገባት ።
እናም  < ባላገሩ ባዶ እግሩን እየሄደ የሚናገረው ግን መርዝ ነው  > ማለት አንድም ጭንቅላታቸው ውስጥ የሚውለበለብ የንቀት ባንዲራ መኖሩን በሌላ በኩል ደግሞ ያላዋቂነት መነሻ ይሆናል ። ይኀው መነሻ መድረሻ ይኖረው ዘንድ ደግሞ  < ትምህክተኛ ነው ፣ ለሃጫም ነው > እያሉ ልጥፉን ማወፈር በርግጥም ባዶ እግርን ሳይሆን የጎደለ ወይም በዘይት እጦት የሚንጣጣ ጭንቅላትን ወገግ አድርጎ የሚያሳይ ነው ።
በሀገራችን ታሪክ ትላልቅ ስራ የሰሩ በርካታ የሀገራችን ጀግኖች እንደተግባራቸው ስማቸው በክብር እንዲታወስ ተደርጔል ማለት አይቻልም ። ይሁን እንጂ የታደሉት ደግሞ ስንት የጀግንነት ተግባር ፈጽመው በስማቸው እውቅና አግኝተዋል ። ለምሳሌ ያህል አትሌት ኃይሌ  « ሃይሌ ገብረስላሴ ጎዳና »ን በስሙ ማግኘቱ ያንስበታል ።  አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ሆስፒታል አይደለም  ሰሞኑን ለደነገጠው አየር መንገድ ማስታወቂያ ብትሆን መሳ ለመሳ ናት ። ያም ማርሽ ይቀይራል - እሷም ዙሩ ሲሳሳ አዲስ አቦሸማኔ  ትሆናለች ። ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን የራሱን የአገጣጠም ስልት በመፍጠሩ « የጸጋዬ ቤት » የተባለ ስያሜ ተበርክቶለታል ። በዚሁ መሰረት በባዶ ጭንቅላት የሚመረቱ መረን የወጡ ስድቦችን « የአቶ አለምነው ቤት » ብሎ መጥራት  ተገቢ ይሆናል ።
ስራ ለሰሪው እሾህ ላጣሪው እንዲል ባላገሩ ።

Tuesday, February 11, 2014

የኢህአዴግ « እብዶች »






ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ
አክቲቪስት የኔ ሰው ገብሬ
ጋዜጠኛ አበበ ገላው


ፊልድ ማርሻል  ኦማር ሀሰን አልበሽር በታሪከኛው ባድመ የተቃቃሩትን ሁለት ሀገሮች ለማስታረቅ ደፋ ቀና እያሉ ነው ። በቅርቡም ጠ/ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝንና ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂን ካርቱም ጠርቼ እንዲነጋገሩ አደርጋለሁ ማለታቸው ተሰምቷል ።
ይህን ዜና ሳነብ ትዝ ያለኝ በጦርነቱ ዋዜማና ማግስት በኢህአዴጎች የተጻፈው የቃል መጽሀፍ ነብር ። ርዕሱ « ትዕቢተ ኢሳያስ » የሚል ሲሆን ዋናው ገጸባህሪ ከጥንቱ ኢያጎ ፣ ከዘመናዊው አሰናቀ / በኢቴቪ በመታየት ላይ ያለው የሰው ለሰው ድራማ ተዋናይ /
 በላቀ መልኩ እኩይነትን አሽሞንሙኖ ያሳየ ነበር ። ኢህአዴግ ጨካኝ ቢሆንም በፖለቲካው ሂሳብ አልተዋጣለትም ነው የሚለው ። በደራሲው አስገዳጅነት ማፊያ ፣ ወሮበላ፣ ጋጠወጥ፣ አምባገነን እና እብድ የተሰኙ ባህሪያትን በተናጠልም ሆነ በጋራ እንዲሸከማቸው ተደርጔል ።
በተለይ « እብዱ » የተሰኘው ስያሜ ፈገግ ማድረጉ ግድ ነበር ። ደግሞ በእብድና በአህያ ፈስ ይሳቃል እንዴ ? ካላችሁ « እብድና ብርድ ያስቃል በግድ » የሚባል ስነቃል እንዳለን ማስታወስ ግድ ይሆንብኛል ።
ዞሮ ዞሮ ፕሬዝዳንት ኢሳያስ የኢህአዴግ አንደኛው እብድ ነበሩ ። አቶ ሃይለማርያም በነገሱ በሶስተኛው ወራቸው በአልጀዚራ የቴሌቪዠን አድራሻ ከኢሳያስ አፈወርቂ ጋር የእንነጋገር ጥያቄ አቅርበው « አይቻልም » የተባሉትም « እብድ » ስለሆኑ ይሆናል ። ምክንያቱም « እብድና ዘመናይ የልቡን ይናገራል »
እነሆ ዛሬ ግን ከ « እብድ » ጋር ቁጭ ብሎ መወያየት ግድ ብሏል ። « እብድ ከወፈፍተኛ ቤት ያድራል » ይልሃል ነገረኛው ስነቃል ። በድርጅቱ የቃል መጽሀፍ ውስጥ « እብድ ቢጨምት እስከ አኩለ ቀን ነው » የሚል ምዕራፍ ባይኖርም የኢህአዴግ ሰዎች እቺን ካርድ መዘዝ ከማድረግ አይቆጠቡም ።
ሁለተኛው እብድ ነፍሱን ይማረውና የኔ ሰው ገብሬ ነው ። እንደ አንዳንድ መገናኛ ብዙሃን ዘገባ የ 29 አመቱ መምህር በዳውሮ ዞን ጣርቻ ከተማ ራሱን አቃጥሎ መስዋዕት የሆነው የፍትህና የነጻነት ጥያቄ በማንሳት ነው ።
ህብረተሰቡና ባለስልጣናት በተሰበሰቡበት አዳራሽ ያለጥፋታቸው ብቻ ሳይሆን ያለፍርድ የታሰሩት ወጣቶች ጉዳይ እንዲታይ እንዲሁም እንዲፈቱ ጠይቌል ነው የሚባለው ። በቂ ምላሽ ያላገኘው ወጣት ራሱ ላይ ቤንዚን አርከፍክፎ በብዙዎች ፊት ሲቃጠል ሶስት መሰረታዊ ጥያቄዎችን በጩኀት እያሰማ ነበር
ፍትህ
ነጻነት
ዴሞክራሲ
ቱኒዚያው መስዋዕት መሀመድ ቡአዚ ተግባር በየት መጣ ያለው ኢህአዴግ አሁን « ሳይቃጠል በቅጠል » የሚለው ጥቅስ ተመራጭ ሆኖ አገኘው ። የዳውሮ ዞንም ሆነ ሌላው ማህበረሰብ የኔ ሰውን « የኛ ሰው » ከማድረጉ በፊት ማንነቱን  እንዲያውቅ አደረገ ።
መንግስት በቴሌቪዥኑ  የኔ ሰው የአእምሮ ችግር ያለበት እንደነበር በእህቱና በአባቱ እንዲገለጽ አስደረገ  ። ምክንያቱም ስም ይወጣል ከቤት ይከተላል ጎረቤት ተፈጻሚ ይሆን ዘንድ ። በአናቱ ላይ ደግሞ « እብድ የያዘው መልክ አይበረክትም » ሲል ከንፈሩን እየመጠጠ አስተያየቱን በአየር ውስጥ ናኘው ።
እብድን ግን እንደ ሀገር ባህል ሰብሰብ ብላችሁ አትቅበሩ የሚል ህግም ሆነ ጥቅስ አለ እንዴ ? መስዋእቱ vs እብዱ የኔሰው በጥቂት ሹማምንቶች ብቻ ታጅቦ ነው አሉ የተቀበረው ። መቼም ሳይንስ እብደት የማይተላለፍ በሽታ መሆኑን ነው የሚመሰክረው ። ታዲያ ድርጅቱ ምን ነክቶት ነው የህብረተሰቡን የቀብር ባህል የተጋፋው ?  መቼም የሞተ ሰው አያስፈራም - የሟቹ እውነተኛ መንፈስ እንጂ ። 
« ስመሰክርልህ ስመሰክርልህ ዋልኩ ቢለው ስታዘብህ ስታዘብህ ዋልኩ አለ » ደገኛ
ሶስተኛው እብድ ጋዜጠኛ አበበ ገላው ነው ። አቶ መለስ በካምፕ ዴቪድ በተጋበዙበት የጂ - 8 ስብሰባ ላይ ተሞክሯቸውን በማቅረብ እሞገሳለሁ ብለው እንጂ እሰደባለሁ ብለው እንዴት ይጠብቃሉ ? « Meles Zenawi is dictator .... Don’t talk about food without  freedom » የሚል ወፍራም ቁጠኛ ድምጽ የአዳራሹን አየር ቀየረው ።
አበበ ገላው የሙንታዳር አልዛይድ ጔደኛ ነበር እንዴ ያሰኛል ። ሙንታዳር ትዝ አላችሁ ? ፕሬዝዳንት ቡሽ ባግዳድ ውስጥ ፕሬስ ኮንፈረንስ ሲያካሂዱ ጫማውን ወርውሮ ያስደነገጣቸው የአረብ ጋዜጠኛ ። በርግጥ ሙንታዳር ጫማ በመወርወሩ የመጀመሪያ አልሆነም ። ይህን የመሰለ ድርጊት በህንድ፣ አየርላንድ ፣ አውስትራሊያ ፣ ታይዋን ፣ ሆንግ ኮንግና ፓኪስታን ተደርጔልና ። እንዲህ ያደረገ ኢትዮጽያዊ ጋዜጠኛ ባለመኖሩ ግን አበበ የመጀመሪያ ድርጊቱ ደግሞ አስገራሚና አነጋጋሪ ሊሆን በቅቷል ። ጥቂት ቆይቶም አቶ መለስ በመሞታቸው
« አበበ ገላው መለስን በላው » የሚል ግጥም ተደረሰ ። ኢህአዴግና ደጋፊዎቹ « አበበ ገላው የአእምሮ በሽታ ያለበት ንክ ሰው ነው » በማለት ጉዳዩን ተራ ለማድረግ የመልስ ምት ሰጥተዋል ።
« አበበ ገላው በነካ እጅህ እገሌ የተባለውን ሚኒስትር አስደንግጥልን » የሚለው የፌስ ቡክ ጥያቄ ቀላል አልነበረም ። ኢህአዴግ ግን ለመጀመሪያ ግዜ እብድን ንቆ ወይም ስቆ ለመተው ተቸገረ ። የኢህአዴግ ሰዎች « እንኴን ለገንፎ ለሙቅም አልደነግጥ » የሚል ጥቅስ መኖሩን ዘንግተው ይሆን ?
የጋዜጠኛውን መንገድ የሚከታተሉ ፣ ንግግሩን የሚቀርጹ ፣ ቆይ ጠብቅ አሳይሃለሁ ወይም እገድልሃለሁ የሚሉ ማስፈራሪያዎች ግን እንደ እድገታችን በሁለት አሃዝ እያደጉ ነው ።
ተንጋለው ቢተፉ ተመልሶ ባፉ እንዲሉ አበው ።

Saturday, January 18, 2014

የቴዲ አፍሮ አዝመራ ...

 


ለእኔ ቴዲ አፍሮ የቲፎዞ ግፊያ ወይም የአጋጣሚ አውሎ ንፋስ ድንገት እሽኮኮ አድርጎት ከፍ ካለው ማማ ላይ ከሰቀለው በኃላ ሳያጣራ ለማድነቅ ወይም ለመውቀስ በሚቸኩለው የትየለሌ አበሻ ዘንድ እልልታን በወደቀ ዋጋ የሸመተ ሰው አይደለም ። ቴዲ አይን ፣ ህሊናና ልቦና ተነጣጥለው ሳይሆን ተዛምደው በሚያዩትና በሚሰማቸው ጥልቅ ትዕይንት የሚመሰጡበትና የሚደነቁበት የጥበብ ማሳ ነው ።
ማሳው ቸልተኛና ቀሽም አርሶአደር ባወጣው ያውጣው ብሎ እንደሰራው ጎስቌላ መሬት የተመሰቃቀለ ምስል የሚታይበት አይደለም ። ማሳው ሰልፍ ማሳመር እንደሚችሉት የሩቅ ምስራቅ ወታደሮች ህብርና ከቃላት በላይ መግለጫ የሚፈልግ ውበት ተሰናስሎ የሚታይበት ክቡር ኪናዊ መድረክ ነው ። ማሳው ጥልቀት ባላቸው የግጥም ሀሳቦችና ሸናጭ ዜማዎች ውህደት ምናብ ሰራቂ እንቅስቃሴዎች የሚታይበት መስክ ነው ።
አዝመራው በስልጡኑ ገበሬ ቴዲ ሲፈልግ ለሙዚቃ የሚሆን ገብስ ፣ ሲፈልግ ለመጽሀፍ መድብል የሚያገለግሉ ስንኞች ተዘርቶ የበቀለበት ነው ። ይህ አዝመራ እንደሌሎች የኪነት ገበሬዎች ገጣሚ ተፈልጎ ስንኝ እስኪመተርና የዜማ አድባር እስኪለመንበት ድረስ በአረም የሚሞላና በከብቶች ኮቴ የሚደፈር አይደለም ። ይህ አዝመራ እንደ ብዙዎቹ የሀገራችን ምስኪን የኪነት ገበሬዎች የሰማይን ዝናብ ጠብቆ በአመት አንዴ ብቻ የሚዘራበት አለመሆኑ ሌላኛው መገለጫው ነው ። የቴዲ አዝመራ ወቅታዊና አስቸኴይ ጉዳዮች ሲፈጠሩ በተሰጥኦ ቅመም የተሰራውን የምርጥ ግጥምና ዜማ እንክብል ውጦ የፌሽታ ፈንዲሻን እነሆ በረከት የሚል ነው ።
ሁሌም ባለመስመር ፣ ሁሌም በንፋስ ኮርኴሪነት ደፋ ቀና እያለ የሚያባብል ፣ ውርጭና ዶፍ  ቢያስቸግረው እንኴን እንደ ሱፍ አበባ ብርሃንና ፍቅርን የሚከተል ነው ።
ይህ ማሳ በመስመር እንደተዘራበት ሰብል ደስ ይላል የሚባልበት ብቻ አይደለም ። ማሳው ላይ የሰርከስ ኦርኬስትራ ልዩ ልዩ ብልሃቶችንና ጥበቦችን የሚያንጸባርቁበትም እንጂ ። ለቢራ የደረሰው የገብስ አዝመራ አስካሪነቱን ብቻ ሳይሆን አዝናኝነቱንም ለምግብነት ከበቀለው ገብስ ጋር ተወያይቶ የሚግባበት የፍቅርና የመቻቻል ገመድ አለው ። ለብዙ ጥቅም የሚውለው የስንዴ አዝመራ በልምድ አናሳ ግምት የተሰጠውን የጔያ ሰብል የሚያገልበት ወይም የባቄላውን አዝመራ « ፈሳም » እያለ የሚያሸማቅቅበት ምዕራፍ የለውም ።
ነጭ ጤፍን የሀብታም ወይም የባለግዜ ቦለቄውን የድሃ ወይም የተጨቌኝ ተወካይ በማለት እያላገጠ የሚያሽካካበት ግዜም ያጥረዋል ። የአዝመራው መስመር በነጠላ መስመር ብቻ ያልተዘረጋውም አንድም ከዚህ አኴያ ነው ። የሰብሎችን ህብርና ስብጥር በልዩ ልዩ ቅርጾች እየወከለ፣ እየገለጠ የሚታይ የኦርኬስትራው ወይም የሰርከሱ መሪ መድብል ነው ።
የቴዲ አዝመራ ደርሶ ሲበላ የመጨረሻ ግቡ በ « ጥጋብ » ደስታን መፍጠር አይደለም ። ፈጣን ምናብ ያለው ገና እህሉን እያላመጠ ፣ ቆይቶ የሚገባውደግሞ በስተመጨረሻም ቢሆን ይሄ ምግብ ከምን ተሰርቶ እንዴት ሊጣፍጥ ቻለ ? እንዴት አንጀትን ያርሳል ? እያለ እንዲያንሰላስልና ብዙ እንዲጠይቅ ማድረጉ ነው ። አዝመራው ፍቅርና ሰላምን ፣ መቻቻልና ብሄራዊ እርቅን ፣ የሃይማኖትና ፖለቲካ እኩልነትን ፣ ፍትሃዊነትንና ሰብዓዊነትን ፣ ቅንነትንና ጀግንነትን በጣም በተኴለና ወጣ ባለ መንገድ ለምናብ አድራሽ ነው ።
ስር በሰደደ ሙያዊ እውቀትና ፍቅር የተያዘው የቴዲ አዝመራ ከአመት አመት የሚሰጠው ምርት እያደገ የመምጣቱን ያህል አፈንጋጭነቱና ልዩ አተያዩ አለርጂ የፈጠረባቸው ግለሰቦችና ቡድኖች በሚገኘው ጠባብ የስህተትም ሆነ የመዘናጊያ ቀዳዳ ሾልኮ በመግባት አንካሴያቸውን ከመወርወር ተቆጥበው አያውቁም  ። እናም አሁንም ለብዙ ግዜኛ መሆኑ ነው ሰብሉ ላይ ልክ እንደ ነጭ ርግብ የተምች ፣ ነቀዝና ፌንጣ ሰራዊት አንገታቸው እየተሳሙ ተለቀዋል ።
በርግጥ መቼ ይሆን በፍቅር አረዳድ ራሳችንን የምንችለው ?
አዝመራው ግን ውርጭና ዶፍ ቢያስቸግረውም እንደ ሱፍ አበባ ብርሃንና ፍቅርን የሚከተል ነው ...


 

Thursday, January 9, 2014

« ግልጽነት የሚሻው ግልጽ ደብዳቤ »


አቶ ግርማ ካሳ ሰሞኑን በዘ ሀበሻ ድረ ገጽ ላይ  « ግልጽ ደብዳቤ ለፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም » የሚል ጦማር ጽፈው አንብበናል ። የደብዳቤው ዋና አላማ በ 2007 ዓ.ም ለሚደረገው ብሄራዊ ምርጫ አንድነት የተባለው ድርጅት በተለይም ከመድረክ ፣ መኢአድ ፣ አረና ፣ ኢዴፓና ሰማያዊ ፓርቲዎች ጋር ውህደት ፈጥሮ ስልጣን በቃኝ የማያውቀውን ድርጅት መታገልን ይመለከታል ።

በርግጥ ግልጹ ደብዳቤ ያስፈለገው የተቃዋሚዎችን ዳግማዊ የአንድነት ትንሳኤ አስረግጦ ለማሳየት ነው ወይስ ለምልጃነት የሚል ገራገር ጥያቄ በእግረ መንገድ ካነሳን ምላሹ የኃለኛው ሃሳብ ሆኖ እናገኘዋለን ። እዚህ ላይ ነው እንግዲህ « ግልጽነት የሚሻው ግልጽ ደብዳቤ » የሚል የመጻፊያ ርእስ ድንገት ብቅ የሚለው ። ፕሮፌሰር መስፍን በኢህአዴግ ዘንድ እጅግ የሚፈራውና የተገለለውን የይቅርታ መንፈስ በሀገሪቱ ዳመና ላይ ለማርበብ ወይም በፖለቲካው አጠራር የብሄራዊ እርቅን አጀንዳ ደጋግሞ ርእሰ ጉዳይ በማድረግ ወደ ተጨባጭ ምዕራፍ ለመለወጥ የተጉ ምሁር መሆናቸው ይታወቃል ። ይህንንም በሚያደርጉት ንግግር ብቻ ሳይሆን ያሳተሟቸውን በርካታ መጽሀፍት በማንበብም መረዳት ቀላል ነው ።

አጠያያቂው ጥያቄ ፣ አቶ ግርማም እንደነገሩን ፣ ፕሮፌሰር መስፍን ሰማያዊ ፓርቲን ከመሰረቱት አንደኛው በመሆናቸውና የመጀመሪያውም መሪ ስለነበሩ « ግልጹ ደብዳቤ » ሌላው ቢቀር ያለ ግልባጭ ቀጥታ ለእሳቸው የመጻፉ ነገር ነው ። በአሁኑ ወቅት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት መሆናቸው ይታወቃል ። ይህ ደብዳቤ መጻፍ የነበረበት ቀጥታ ለወቅታዊው የፓርቲው አመራር ወይስ ወደጎን ለቀድሞው ቁልፍ ሰው ?

ይህም ጥያቄ ሌላ ጥያቄ ይወልዳል ። አቶ ግርማ ፓርቲውን አነጋግረው ጥሩ ምላሽ አላገኙም ማለት ነው ? ከሆነ የጻፉት ግልጽ ደብዳቤ እስከሆነ ድረስ ለአንባቢው ይኀው የኃላ ታሪክ መገለጽ ነበረበት ። ርግጥ ነው አቶ ግርማ ውስጥ ያለውን ነገር ሊነግሩን ባይፈልጉም የግልጹ ደብዳቤ አንዳንድ ሀረጎች በራሳቸው ችግር መኖሩን እየጮሑ የሚያሳብቁ ናቸው ።

አቶ ግርማ ፈገግ ብለው አሉ ።

1 . « የሰማያዊውን ነገር በርስዎ ጥዬዋለሁ ። ያሳምኗቸውና ያግባቧቸው ዘንድ እጠይቃለሁ »

አቶ ግርማ ኮስተር ብለው አሉ ።

2 . « ምክርዎትን አልሰማ ብለው የተናጥል ጉዞ ከቀጠሉ ምርጫው የእነርሱ ይሆናል »  ጥርሳጨውን እያንቀጫቀጩና ሳይታወቃቸው ጠረጤዛ እየደለቁ ... « ጉዳዩ የፌዝና የቀልድ ወይንም የግለሰቦች ተክለሰውነት የመገንባት ሳይሆን የአገር ህልውናና ደህንነት ነው ... »  በማለት ቀጠሉ ።

ልብ በሉ አምስት ሳንቲም አላጋነንኩም ። ያደረኩት የአቶ ግርማ ቃላቶች ደምና ስጋ እንዲለብሱ ማድረግ ነው ወይም ቃላቶቹ የሚወክሉትን አካላዊ እንቅስቃሴ አስደግፎ ማቅረብ ብቻ ነው ። ታዲያ እንዴት ነው ጎበዝ ማነው እያፌዘና እየቀለደ ያለው ? እረ ማነው ፖለቲካን ለተክለ ሰውነት መገንቢያ ጥቅም እያዋለ የሚገኘው ? የሚሉ ጥያቄዎች ውስጣችን እየተንጫጫ እንዴት ነው ሆዳችንን የማይቆርጠን ... ለዚህም ነው ግልጹ ደብዳቤ ሊነግረን ያልፈለገው ወይም የደበቀን ነገር በመኖሩ የግልጽነቱን አላማ ስቷል የሚያስብለው ።

 አንባቢ « ነገርን ከስሩ ውሃን ከጥሩ » ብሎ ይመረምርና ይታዘብ ዘንድ በቂ የመረጃ ትጥቅ ሊኖረው ይገባል ። አቶ ግርማ እንዳሉት የማስታረቅና የመሸምገል ልምድ ያላቸው ፕሮፌሰር መስፍን በተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል ያለውን ጠባብም ሆነ ቦርቃቃ ልዩነት ከምን ተነስተው ምን ደረጃ ላይ አደረሱት ? የሚል ምናባዊ ቢጋር አዘጋጅቶ እንዲንቀሳቀስም ይረዳው ነበር - አንባቢው ። ግና ቢጋሩ እንዳይነደፍ ግልጹ ደብዳቤ ውስጥ unግልጽ የሆኑ እንክርዳዶች መንገድ ዘግተዋል ።

ነገር ሰነጠቅክ አትበሉኝ እንጂ ደብዳቤው ውስጥ የኢህአዴግን የመሰለ « ረጅም ሪሞት ኮንትሮል » የተመለከትኩ መስሎኛል ። በመጀመሪያ ለዚህ ጽሁፍ ዓላማ የተዘጋጀውን « ሪሞት ኮንትሮል » ብያኔ እንስጠው ።

ሀ . የተለየ ትርጉም ካልተሰጠው በስተቀር በዚህ ጽሁፍ ውስጥ « ሪሞት ኮንትሮል » ማለት ገባ ወጣ የማይል የህንድ ፊልም አክተር ማለት ነው ። የህንድ ዋና አክተር በገጀራ አንገቱ ቢከተከት ፣ በላውንቸር ጥይት ደረቱ ቢቦደስ ለግዜው ቢደማ ፣ ለግዜው ቢሰቃይ እንጂ በፍጹም አይሞትም ። የህንድ አክተር እንደ ፈጣሪ በሶስተኛው ቀን ባይሆንም እንደ እባብ ከሞተ በኃላ አፈር ልሶ በመነሳት ተመልካቹን ጉድ የማሰኘት አቅም አለው ።

የኢህአዴግ ህንዳዊ አክተር የሆነት አቶ መለስ ይኀው ሞተውም ቢሆን ሀገር እየገዙ ፣ ሰራዊት እያዘዙ ፣ ቦንዳዊ መልዕክታቸውን ከሚያማምሩ ጥቅሶች ጋር እያስተላለፉና « ሌጋሲ » የተባለ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማቸውን እያዘጋጁና እየተወኑ ናቸው ። በሪሞት ኮንትሮል ። ብዙ ግዜ ታዲያ የህንድ ፊልም ተመልካች የአክተሩን ልዩ ተግባር እያደነቀ መመሰጥና ማጨብጨብ እንጂ ለምንና እንዴት በሚሉ ገሪባ ጥያቄዎች መጨናነቅ አይፈልግም ። እናም ኢህአዴግ ማለት በአራት ጎሳዎች ውህደት የተሰራ ድርጅት ነው የሚለው ትምህርት እንዴት እንደተደለዘ ሳይታወቅ ኢህአዴግ ማለት መለስ መሆኑ ከተረጋገጠ ቆየ ።

ታዲያ በአቶ ግርማ ደብዳቤ ውስጥ የታየው ሪሞት ኮንትሮል ምንድነው ? ከተባለ ነገሩን ከኢዴፓ ለመጀመር ይቻላል ። ኢዴፓን ለረጅም ግዜ የመሩት አቶ ልደቱ አያሌው ፖለቲካ ርስት አይደለም በማለት ከሳርና ስፖንጅ የተሰራውን ወንበራቸውን ለምክትላቸው ለአቶ ሙሼ ሰሙ ማስተላለፋቸው ይታወሳል ። በሶስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ሳይሆን በሶስተኛ የፍልስፍና መንገድ የሚታወቁት አቶ ልደቱ ከፖለቲካ ርቀው በቅርቡ ወደ መዶለቻው ሰፈር /ፖለቲካ / መቀላቀላቸውን በዜና ሰምተናል ። አቶ ግርማ ለግልጽ ደብዳቤያቸው ማጠናከሪያ ይሆን ዘንድ « አቶ ልደቱ አያሌው ለአድማስ ጋዜጣ በሰጡት አስተያየት ኢዴፓ ከአንድነት ጋር አብሮ ለመሆን የመፈለግ አዝማሚያ ሳይኖረው እንደማይቀር አስባለሁ » ብለው ጽፈዋል ። ልብ አድርጉ ባለሙሉ ስልጣኑን አቶ ሙሼን አይደለም የገለጹት - ከጨዋታው የራቁ የመሰሉትን አምባሰደር ልደቱን እንጂ። እዚህ ሀሳብ ውስጥ የህንድ አክተርም በሉት ሪሞት ኮንትሮልን እንደ ቀጭኔ አንገቱን አስግጎ አልታያችሁም ?

ሁለተኛው ሪሞት ኮንትሮል ራሱ ሰማያዊ ፓርቲ አካባቢ የሚሸት ነው ። አቶ ግርማ « የርስዋ ድርጅት ሰማያዊ ፓርቲ ሀገር ቤት ጥሩ እንቅስቃሴ ከሚያደርጉ ድርጅቶች ከጥቂቶቹ መካከል አንዱ ሆኗል » በማለት ነበር ለፕሮፌሰሩ የሚገልጹት ።

ኃይለ ቃል ፣ የርስዎ ድርጅት

ምዕራፍ አንድ ፣ አሁን የአመራር አባል ላልሆነ ሰው እንዲህ እንዲገለጽ የቌንቌ / ሰዋሰው /  ስርዓታችን ይፈቅዳል ?

መካከለኛ ምዕራፍ ፣ የርስዎ ደርጅት የሚለው አነጋገር በጣም ለማጠጋጋት እንደሚያስቸግር ቁጥር ከመሃል ዝቅ ብሎ የወረደ ቢሆንም ድሮ የመሰረቱት ለማለት ተፈልጎ ነው ብለን ብናፏቅቀው ምን ያህል ያስኬደናል ?

መደምደሚያ ፣ የርስዋ ድርጅት ማለት ሳናጠጋጋው እረ እንደውም ከሩቅ በሪሞት ኮንትሮል ብንነካካው ትርጉሙ አሁንም ከጀርባ ሆነው የሚመሩት ማለት ይሆን ?


የገምጋሚው ማስታወሻ ፣ ግልጽነት ሳይቀድም ይቅር ለእግዚአብሄር መባባል ትርጉም ያጣል ። የግልጽነትን ድልድይ ሳይረግጡ ከአንድነት ቅጥር ግቢ መድረስ ያስቸግራል ። ደብዳቤውም ግልጽነት ያንሰዋል ። በደብዳቤው እንድንግባባ ተጨማሪ የማፍታታት ስራ እንዲሰሩ ይነገራቸው ። በቂ ነው ብለው ካሰቡ ግን ላጺስ ከኢህአዴግ ተውሰው ርዕሱን በአስቸኴይ ይደልዙት ። ለባለይዞታው ይመለስ ብለናል ።

Wednesday, December 18, 2013

ሊቨርፑል በገና ዋዜማ





ሰማዩ እጅግ ከፍቶታል ...

እንዲህ መሆን ከጀመረ ቆየ ።

አምቆ የያዘውን ጥቁር እባጭ የመሰለ ነገር ዘርግፎ ቢጨርሰው ሰላም ባገኘ ነበር ። ግና ቁጣ እንዳስበረገገው የአበሻ ህጻን ቆይቶ - ቆይቶ ነው ጠብ የሚያደርገው - ርግጥ ነው እንደ ህጻን ችክ ያለ ማላዘን አይታይበትም ።

ተጠሪነቱ ለደመናው ይሁን ለምድሪቱ ያልታወቀው ብርድ ግን የተሰጠውን ተልዕኮ በአግባቡ እየተወጣ ይገኛል ። አንዳንዴ በግልጽ እንደ ውሻ ይናከሳል ... አንዳንዴ እንደ ስለታማ ቢላ አካልን ይሰነጥቃል ። በግላጭ በሚያገኛቸው ጆሮ ፣ አፍንጫና የእጅ ጣቶች ላይ ደግሞ ጥቃቱ ለጉድ ነው ። እንደ ንብ ነድፎ - ነድፎ በረዶ ቤት የተቀመጡ ዕቃዎች ያደርጋቸዋል ።

ምድሪቱ ጉንጭ ላይ ስስ ፈገግታ ይታያል ...

ዓላማና ግቧ ግን ሙሉ ፊቷ ላይ ሳቅ እንደፈንዲሻ እንዲተራመስ ማስቻል ነው ። እናም ግብግብ ላይ ናት ። በረዶው ፣ ንፋሱ ፣ ብርዱ ፣ ዝናብና ጭጋጉ የቱንም ያህል ጥቃት ቢያደርስብን የገና በዓላችንን ከማድመቅ አይገድብንም የሚሉት ሊቨርፑዲያንስ ሙሉ ከተማውን ሞልተው ይሮጣሉ ። ሩጫቸውን ከንግድ ቤቶች የሚወጣው የገና ሙዚቃ ያግዛቸዋል ። ታላቅ ቅናሽ እያሉ በማይክራፎን የሚያላዝኑት ሱቆችም በረከቱ እንዳያመልጣቸው አጥብቀው ይወተውታሉ ። እዚህ እንደ እኛ ሀገር ዶሮና በግ ጥጋቸውን ይዘው አይጮሁም ። ሳርና ችቦ የሚቸረችሩ ወቅታዊ ነጋዴዎች ማየት አይቻልም ፤ አየሩ በተነጠረ ቅቤ ፣ በኮባና ኩበት ጢሳጢስ የተሞላ አይደለም ።

በርግጥም አየሩን የተቆጣጠሩት አብረቅራቂ መብራቶችና ሙዚቃዎች ናቸው ። መኖሪያ ቤቶች ፣ ህንጻዋችና « ሲቲ ሴንተር » የተባለው የገበያ ቦታ ለአይን በሚማርኩ የመብራት ውጤቶች ተንቆጥቁጧል ። ከሱቆቹ በተጨማሪ እዚህም እዚያም የተለያዩ የሙዚቃ ስራዋችን የሚያሳዩ ግለሰቦች እንደ አሸን ፈልተዋል ። ትላልቅ ሴቶች ሳይቀር አኮርዲዮን እጥፍ ዘርጋ እያደረጉ ሳንቲም ይሰበስባሉ ። ሁለት ሶስት ሆነው ቆርቆሮን እንደ ከበሮ በመጠቀም የመንግስት ማርሽ ባንድን የሚያስንቁ ሰዋችም ይታያሉ ። በአርሞኒካ ብቻ የብዙዋቹን ትዝታ የሚያማልል ፣ እንዲሁም ከውሻው ጋር ቁጭ ብሎ የሚመስጥ መሳሪያ የሚጫወት ሌላ ሰው በሌላ ክንፍ አይታጡም ።

በስነስርዓት ማይክራፎንና ኪቦርድ አዘጋጅቶ የፈረንጆቹን ሙዚቃ የሚጫወት አንድ አፍሪካዊ ግን ብዙ ግዜ የብዙዋችን ትኩረት ሲስብ ተመልክቼያለሁ ። ተመልካቹ ክብ ሰርቶ አፉን ከፍቶ ፣ አንገቱን ግራና ቀኝ እየናጠ ይመለከተዋል ። አንዳንዶቹ ደግሞ መሃል ገብተው ይወዛወዛሉ ። ይህን ሰው X – Factor አያውቀውም ወይስ X – Factor / የእንግሊዞች ታዋቂ አይዶል ሾው / አንጋሎ የተፋው ነው ? ድምጹ ብርዱንና ውሽንፍሩን በታትኖ ከጆሮ የሚደርሰው ሳይደናቀፍ ነው - አይጎረብጥም ። የዳጎሰ ልምድ ያለው መሆኑ ለተራ ሰውም ግልጽ ነው  - አንዳንዶች ሊወኒልን ሪቼ እያሉ ይጠሩታል ። በርግጥም የታዋቂውን አቀንቃኝ አንድ ሙዚቃ ሲያቀነቅን ነበር ፣

Good bye  ይለዋል ታዳሚውን እንደሚሰናበት ሁሉ  

I wanted you for life
You and me
In the wind
I never thought there come a time
That our story would end
It’s hard to understand
But I guess I’ll have to try
It’s not easy
To say good bye ... good bye ... good bye ..


ሙዚቃውን ሲጨርስ ታዲያ የሚሰሙት ጭብጨባ አንድ ትልቅ ቲያትር ቤት የታደሙ ያህል ነው ። ከዚያም ፊት ለፊት ባስቀመጠው ሻንጣ ውስጥ የእንግሊዝ ነጭና ቀይ ሳንቲሞች ሲንቦጫረቁ ይሰማል ።

አፍሪካዊው አቀንቃኝ

ሙዚቃ ወዳዱ የሊቨርፑል ነዋሪ ሲጋራውን እያቦነነ ፣ ሀምበርገሩን እየገመጠ ፣ የሚጠጣውንም እየተጎነጨ ያዳምጣል ። የዚህ ከተማ ሃምሳ የሚደርሱ አቀንቃኞች በምድረ እንግሊዝ ብቻ ሳይሆን በዓለማቀፍ ደረጃም ትልቅ ስም ያላቸው ናቸው ። ሙዚቃዋቹ ለጆሮ በደረሱበት ዘመን በሽያጭ ረገድ ቁጥር አንድ በመባላቸው ከተማዋ በጊነስ ቡክ ላይ የሙዚቀኞች ሀገር ለመባል አስችሏታል። በ1960 የተመሰረተውን The Beatles ብቻ ለአብነት ማንሳት ይቻላል ። አራቱ የቡድኑ አባላት ጆን ሊኖን ፣ ፓውል ማካትኒ ፣ ጆርጅ ሀሪሰን እና ሪጎን ስታር በ1962 « Love Me Do » የሚለውን አልበም እንደለቀቁ ነበር ታዋቂነትን የተጎናጸፉት ። ሮሊንግ ስቶን ሙዚቀኞቹን የምንግዜም ትልቅ አርቲስቶች ብሏቸዋል ። ታይም መጽሄት በበኩሉ የሃያኛው መቶ ክፍለዘመን መቶ ተጽዕኖ ፈጣሪ ብሎ ከዘረዘራቸው ግለሰቦች መካከል አስፍሯቸዋል ። የፈረደበት ጊነስ ቡክ ወርልድ የሙዚቀኞቹን « Yesterday » የተባለው ሙዚቃ ከሶስት ሺህ አርቲስቶች በላይ ከእንደገና ተጫውተውታል ይለናል ። አስደናቂው ነገር እንዲህ ተደጋግሞ የተዘፈነበት ሌላ ሙዚቃ አለመኖሩ ነው ።

በከተማው መሃል ለገና እየቀረበ ያለው ሌላው ስጦታ የግለሰቦች « ምትሃታዊ » ስራ ነው ። ለነገሩ አስማት ይባል ሌላ ጥበብ በድፍረት መናገር ቸግሮኛል ። እስኪ አንድ አጭር « ሾው » በጽሁፍ እንከታተል ፤

 አንድ ሰው ሻንጣ ይዞ መጣ ።
ከሻንጣው ውስጥ የሚያብረቀርቅ ልብስ አውጥቶ ለበሰ ።
 አናቱ ላይ  ቀንድ ያለው ማክስ አጠለቀ ።
ፊቱንም ልብሱን የመሰለ ነገር ተቀብቶታል ።
የልብሱን ቀለም የመሰለች ብትር አወጣ ።
ዙሪያ ገባውን ማትሮ በፈገግታ እጁን አወዛወዘ ።
በአካባቢው መንኮራኮር የለም እንጂ ወደ ላይ ለመምጠቅ የመጨረሻ ሰላምታ የሚሰጥ ነበር የሚመስለው ።
 መሬቱ ላይ ጥቁር ጨርቅ አነጠፈ ።

የፈራነው ደረሰ ?

እንዴ ? ... ዱላውን ተሞርኩዞ በአየር ላይ ቁጭ አለ ። በቃ ! ... ይወርዳል ብለን ብንጠብቅ - ብንጠብቅ ቁጭ እንዳለ ቀረ ። መቼም ይህ ሰው ሊንሳፈፍ የቻለው ጭንቅላቱን « ጨረቃ ላይ ነህ » ብሎ በማሳመኑ ሊሆን አይችልም ። ብዙዋቹ በጥበቡ በመገረም ሳይሆን በፍርሃትና በጥራጣሬ ነበር የሚመለከቱት ። እንዴት ሊሆን ቻለ ? ሰውነቱ ውስጥ የቀበረው ነገር ይኖር ይሆን ? በዜና ያልሰማነው ምን የሚያንሳፍፍ መሳሪያ ተገኘ ? መልስ አልነበረም ። ሳንቲም ወርወር ሲያደርጉለት ብቻ እጁን በአፉ እየሳመ ፈገግ ይላል ። ከዚያ ውጪ ኮስተር ስላለ ጥሩ ቀራጺ የሰራው ሃውልት ነው የሚመስለው ።

ተንሳፋፊው ሰው

 « ይገርማል » እያልኩ ሌላውን የገበያ አቅጣጫ መከተል ጀመርኩ ። የማስበው ስለ ምትሃት ነበር ። አስማት ጥበብ ነው ፣ ሳይንስ ነው ፣ ፈጣን የጭንቅላት ጨዋታ ነው ፣ በባዕድ አምልኮ ጋር የተገናኘ መንፈሳዊ ስራ ነው ... ብዙ ብዙ ይባላል ። ድንገት አባባ ተስፋዬ ሳህሉ በአእምሮዬ ጔዳ ብቅ አሉ ። በቴሌቪዥን መስኮት የምትሃት ጥበብ እያሉ ገመድ ሲቌጥሩና ሲፈቱ ፣ ጨርቅ ሲያሳዩና ሲሰውሩ  ብዙዎቻችን ተመልክተናቸዋል ። ምናልባትም ለአስማትና ምትሃት ያለን የእውቀት ጥግ ያንን ያህል በመሆኑ ሊሆን ይችላል አድናቆታችን አለቅጥ የሚረዝመው ።

ስለ አስማት የሚያውጠነጥነው አእምሮዬ ተጨማሪ ነገር የፈለገ ይመስል ከሌላ ምትሃተኛ ጋር ተገጣጠምኩ ። ይሄኛው ደግሞ በሙሉ ልብስ ዝንጥ ያለ ነው ። የያዛትን ዣንጥላ አንዴ ይደገፋታል ፣ ሌላ ግዜ ይዘረጋታል ። እየሰራ ያለውን ነገር በግልጽ እንድትረዱት ለማድረግ የግድ ስዕላዊ ገለጻ መጠቀም አለብኝ ። ለምሳሌ ያህል መደገፊያው ራቅ ያለ ምርጥ ሶፋ ላይ እግራችሁን አንፈራጣችሁ ቁጭ ብላችኃል እንበል ። ቀስ ተብሎ ሶፋው ከስራችሁ ሸርተት ቢደረግ ቁጭ እንዳላችሁ ትቀራላጭሁ ወይስ ሚዛን ስለማይኖራችሁ ትወድቃላችሁ ? መልሱ ግልጽ ነው ። እንግዲህ ይህ ምትሃተኛ አየር ላይ የተቀመጠው ሶፋው ከተነሳበት በኃላ መሆኑ ነው ። ሙሉ ሚዛኑን እየተቆጣጠረ ያለው በሁለት እግሩ ነው ። እስኪ ሞክሩት ።
ወገብዋ እንክትክት ቢል ግን የለሁበትም ።

አየርን ተደግፎ መቀመጥ

ከገበያው ግርግር ወጥቼ አስገራሚ ስነጥበብ ያረፈባቸውን ህንጻዋች ፣ ሙዚየሞችና የስዕል ጋለሪዋች እየተመለከትኩ ስጔዝ እግሬን አልበርት ወደብ አካባቢ አገኘሁት ። እየቸኮልኩ ነበር ። ምክንያቱም እዚህ ሀገር የሚጨልመው ከቀኑ አራት ሰዓት / በእኛ 10 /  ጀምሮ በመሆኑ ብርሃንን መሻመት አለብኝ ። ጠዋት አንድ ሰዓት ሆኖም ጨለማው እንደተዘፈዘፈ ነው ። ካላወቁ ጠዋት ቀጠሮ ይዘው እንኴ « እረ አልነጋም » ብለው ይተኛሉ ። አስራ ሁለት ሰዓት ሲሆን የምሽት ስንብትንና የመንጋት መምጣትን ወፎች በጨኀት አያበስሩም ። ለነገሩ የቤት ርግብ እንጂ ወፍ ይኑር አይኑር ርግጠኛ መሆን አልቻልኩም ። ውስን ወፎች ቢኖሩ እንኴ እንቅልፋሙን ሰው የመቀስቀስ ግዴታ የሌለባቸው ይሆናል ። ምክንያቱም ይህ ዴሞክራሲ የበዛበት እንግሊዝ ነውና ። ስለዚህ ጠዋት ስራ ገቢ ከሆኑ ሰዓት ሞልተው ጆሮዎ ስር አላርሙን በወፍ ዜማ ማስጮህ ይኖርቦታል ።

ይሄ የመምሸት ነገር ግን እንደሚመስለኝ ቀን ያለ ሰዓቱ ወደ ምድር የሚወረወረው ተፈጥሯዊ ሬንጅ በማግስቱም ከመሬት ለመላቀቅ የሚገጥመው ፍትጊያ ቀላል አይደለም ። እጅ ላይ የፈሰሰ የበረሃ ሙጫ በሉት ። « ወግድልኝ » ብትሉትም ሙጭጭ ብሎ እየተሳበ የሚልመጠመጥ ። እናም እስከ የካቲት ድረስ ጸሃይ ብቻ ሳትሆን ቀንም ራሱ ብርቅ ይሆናል ነው የሚባለው ።

በስመዓም ... አልበርት ወደብ በጣም ይጎበኛል ። ከጥንታዊነቱም ከዘርፈ ብዙ አገልግሎት ሰጪነቱ አኴያ ሊሆን ይችላል ። በ1846 ነው የተገነባው ። ይሁን እንጂ ቡና ቤቶች ፣ ሱቆች ፣ ሆቴሎች ፣ የባህር ትራንዚትና የአለማቀፍ ባርነት ሙዚየሞች እንዲሁም የ ዘ ቢትልሶችን ታሪክ አቅፎ ይዟል ። በግዜውም በያዘው ሰፊ ቦታና ተግባር ከዓለማችን ቁጥር አንድ ነበር ።

የከተማው አዛውንቶች ታዲያ ዉሻ እያስከተሉ ነው ወደቡን የሚጎበኙት - በልብስ ያጌጡ ውሾች ። ውሾቹ ግን የሌላ ሀገር ምርጥ ተሞክሮ እጥረት ያለባቸው ነው የሚመስሉት ። ምክንያቱም መናከስ፣ ማስደንገጥ ቢያንስ መጮህ የተባለውን የዘመዶቻቸውን ቌንቌ የት እንዳደረሱት አይታወቅም ። ማንም ቢያባብላቸውና ቢደባብሳቸው ግድ የላቸውም ። የሚታያቸው ቶሎ ብሎ የውስጥ ገላቸውን ፈርከስከስ አድርጎ ማቅረቡ ነው ። ዉሻ ካልጮኀ ደግሞ በግ ሊመስል ይችላል ። የሀገሬ ሰው ግድጔድ ቆፍሮ ቀብሮ ፣ ቢቻል ተርብ እያበላ አሳድጎ ዉሻው ጸጉረ ልውጥ ሰው ጅርባ ላይ ፊጥ ሲልማ መመልከት ይፈልጋል ። አለዚያማ እንደ አውደልዳይ ዉሻ መንገድ ላይ ይጣላል ። የዚህ ሀገር ዉሾች ውሎአቸው መኪናና ቡናቤት አዳራቸው ደግሞ ሳሎን ነው ። ውሻ የሚያሳድጉበት ዋና አላማም ሰውንም ሆነ ሌባ ማስደንገጥ አይመስልም ። ታዲያ ምንድነው ከተባለ የእንስሳት ፍቅር ወይም ሆቢ ብሎ ማለፍ ይቻላል ።

         እንዳልኴችሁ የሊቨርፑል ወደብ ከተማዋ እንድታድግ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጔል ። ይህን ወደብ ጨምሮ ስድስት የሚደርሱ አካባቢዋችም በዩኔስኮ የዓለም ቅርስ መዝገብ ውስጥ የሰፈሩ ናቸው ። ታዋቂው ብዕረኛ ቻርልስ ዲከንስም  ወደቡን « ሃብታሙና ማራኪው » በማለት ነበር የገለጸው ።

አልበርት ዶክ 

በነገራችን ላይ ዳንኤል ዴፎ ፣ ዋሽንግተን ኢርቪንግ ፣ ቻርልስ ዲከንስና ሌሎች ታዋቂ የጥበብ ሰዋች ሊቨርፑልን ጎብኝተዋል ። ደጋግሞ በመጎብኘት ምናልባትም አስራ ሁለት ግዜ ዲከንስን የሚያህል የለም ። ደራሲው ደጋግሞ የሚመጣው መጽሀፎቹን ለመጻፍ ይረዳው ዘንድ አንዳንድ ነገሮችን ለመመርመር ፣ መድረክ ላይ ተጋብዞ ለመናገርና የራሱን ስራዎች ለማንበብ ነው ። እንደሚታወቀው ሃያ የሚደርሱ መጽሀፍትን ለአንባቢያንን አበርክቶ ነው ያለፈው ። ስነጽሁፍ በኮሌጅ የተማረም Great expectation , Oliver twist , A tale of two cities , Hard times እና The pick wick papers የተባሉ ስራዎቹን አይረሳም ። እኔ በወቅቱ ዲክንስ ከአደፍርሱ ደራሲ ዳኛቸው ወርቁ ጋር ይመሳሰልብኝ ነበር ። ሁለቱም ቃላትን አጥብቀው የሚወዱ ፣ በቃላት መራቀቅ የሚፈልጉ « Wordy » የሚባሉ አይነቶች ናቸው ። ጹሁፉን በአግባቡ ተረድተን የቤት ስራችንን ለመስራት በጣም እንቸገር ነበር ። አደፍርስንስ ስንት ግዜ ነው እየጀመርኩ የተውኩት ? የቁጠኛውን ዳኛቸውን ባላውቅም ዲክነስ ፍጹም የመድረክ ተናጋሪና ተከራካሪ እንደነበር መዛግብት ያስረዳሉ ። ዲክነስ እንደ ንግግሩ ሁሉ ጹሁፎቹ ለጥቅስ የሚበቁ ናቸው ። ለዛሬ ግን የሚከተለውን ላስታውስለት ፣

« No one is useless in this world who lightens the burden of another . »

ከአልበርት ወደብ አካባቢ ሆኖ ጀምስ መንገድ ላይ የሚገኘው የአልቢዎን ሀውስ ይታያል ። ይህ ህንጻ ሲነሳ ደግሞ ሊቨርፑልና ታይታኒክ የተባለችው ታሪካዊ መርከብ የነበራቸውን ጥብቅ ቁርኝት መረዳት ያስችላል ። እንደሚታወቀው ከመርከቧ የፈት ገጽ ላይ ታይታኒክ ከሚለው ጽሁፍ በታች Liver Pool የሚል ጽሁፍ ይታያል ። ይህ የሆነው የካምፓኒው ጽ/ቤት / አልቢዎን  ሀውስ / እዚህ በመገኘቱ መርከቧ የተመዘገበችው በከተማው ስም ስለሆነ ነው ።

የታይታኒክ ማዋለጃ ቤት

ታይታኒክ የተጸነሰችውም ሆነ የመጨረሻውን ዲዛይን የያዘችው በሊቨርፑል ይሁን እንጂ ነፍስ ዘርታ መንቀሳቀስ በጀመረችበት ወቅት ሊቨርፑልን ማየት አልቻለችም ። ሌላው ቁርኝት ከመርከቧ ሰራተኞች 90 ያህሉ በተለይም ታይታኒክ ከበረዶ ጋር ስትጋጭ የተመለከቱትን ሁለት ሰዋች ጨምሮ የተቀጠሩት ከሊቨርፑል መሆኑ ነው ። ፊልሙን ባየነው መሰረት የሰውየው አጯጯህ  እንዴት ነበር ? « የበረዶ ቌጥኝ ይታየኛል ! ... የበረዶ ቌጥኝ ይታየኛል ! ... » ምን ዋጋ አለው አንዳንዶች ዘግይቶ ሪፖርት አድርጔል በማለት ከርፋፋ ሲሉት ሌሎች ደግሞ ስራውን በአግባቡ የተወጣ ጀግና ያደርጉታል ። መርከቧ ስትሰምጥ ምንም ሳያቌርጡ ሲዘፍኑ የነበሩ ሙዚቀኞችን እንዲሳፈሩ ያደረጋቸው ወኪል የሚገኘውም በሊቨርፑል ነው ። ባይሆን የሙዚቀኞቹ ነገር እጅግ ይገርማል ። ሰው ህይወቱን ለማትረፍ ላይ ታች ሲራኮት የእነሱ ነፍስ ግን በሙዚቃው ሃይል ውስጥ ተውጦ ነበር ። ሊቨርፑልና የሙዚቃ ፍቅርን በማያያዝ እነዚህ ሰዎች ሊቨርፑዲያን ነበሩ ማለት አይቻል ይሆን ? አላውቅም ። የመርከቧ የሞተር ክፍል / Engine / የተሰራውም ሊቨርፑል በሚገኝ ድርጅት ነው ። ለታይታኒክ ሞተር ክፍል ሰራተኞች መታሰቢያ ይሆን ዘንድ በዋተር ፍሮንት ሃውልት ቆሟል ።

ይህ ታሪካዊ ህንጻ በአሁኑ ወቅት ምን እየተሰራበት እንደሆነ ባላውቅም / ምናልባትም ለሽያጭ ቀርቦ ይሆናል / እንደ ታሪካዊነቱ በአግባቡ የተያዘ አይመስልም ። ሶስቱ በግማሽ ጨረቃ ቅርጽ የተሰሩት የፊት ለፊት በሮቹ ተዘግተዋል ። በጎን በኩል የሚገኘውም እንደዚሁ የታሸገ ነው - የዚህኛው ልዩነቱ ከበሩ ጀርባ የቆሻሻ ክምር መታየቱ ነው ። ምናልባትም የታይታኒክ ቅርጽ ይኖረው ይሆን በሚል ጥርጣሬ ራቅ ብዬ አጠናሁት ። ባለ ሶስቱ ፎቅ ህንጻ በምንም ተዓምር መርከቢቷን አይመስልም ። እረ ታይታኒክ ቅንጡ ህንጻ ነበረች ። ለነገሩ ለግንባታዋ የፈሰሰው ዶላር ቀላል አይደለም -  7.5 ሚሊየን ። 3547 ሰዎችን አሳፍራ በኩራት ነበር ባህሩን የምትሰነጥቀው ። አጠቃላይ ቁመቷም ቢሆን 11 ፎቅ ርዝመት ካለው ህንጻ ጋር የሚተካከል ነው ። ውስጧስ ቢሆን ዘመናዊ ሆስፒታልን ጨምሮ ምን የሌላት ነገር አለ ?

ህንጻውን እየራቅኩት ስሄድ በሆነ ነገር ላመሳስለው እየፈለኩ ነበር ። በል ቻዎ ስለው የታይታኒክ ማጀቢያ የሆነው የሴሊንዲዮን my heart will go on የሚለው ዜማ ከየት አባቱ እንደመጣ አላውቅም ። ውስጤ ለአፍታ ያህል የተንጫጫ መሰለኝ ፣

Every night in my dream
I see you , I feel you
That is how I know you go on
Far across the distance
And spaces between us
You have come to show you go on
Near , far , wherever you are
I belive that the heart does go on
Once more you open the door
And you’re here in my heart
And my heart will go on and on


እቺ ከአየርላንዱ ደብሊን እና ከጀርመኗ ኮሎኝ መሃል የምትገኝ መካከለኛ ከተማ የፊልም አምራች ድርጅቶችንም ቀልብ መግዛት የቻለች ናት ። captain America , In the name of the father , Sherlock holmes , Fast and furious 6 , Harry potter and the dealthy hallows የተባሉ ትላልቅ ስራዋችን ጨምሮ በብዙ መቶ የሚቆጠሩ ፊልሞች ተቀርጾባታል ።

ዛሬ እነዚህ ታሪካዊ ቦታዋች በሙሉ ዋና ትኩረታቸው የፊልም ኢንዱስትሪውንና ጊነስ ቡክን መሳብ ሳይሆን በቅርቡ የሚከበረውን የገና በዓል ደማቅ ማድረግ ይመስላል ። Remember , if Christmas isn’t found in your heart , you won’t find it under a tree . የሚለው አባባልም ለበዓሉ የሚሰጠውን ግዙፍ ክብር አመልካች ነው ። ለማንኛውም መልካም ገና ይሁንላቸው ማለት ይገባል ።

ግልባጭ ፣
ጥቂት ቆይቶ ብቅ ለሚለው አትዮጽያዊው ገና ።