Thursday, June 8, 2017

በስም እንደራጅ


መንግሥት ሰማንያ ሚሊየኑ ሕዝብ በተበታተነና በተበጣጠሰ መልኩ ለሚያነሳው ችግርና ጥያቄ እልባት ለመስጠት አይቻለኝም ብሏል መብትን ለማስከበር ፣ ብጣቂ  የምታህለውን ብድር ለማግኘት ሥራ ለመስራት ቦታ ለማግኘት ብቻ ለሁሉም ነገር መደራጀት ግድ ብሏል

ግዴታውን ለመወጣት ሕዝቡ በጾታ ተደራጅቷል፤የሴት ሊግ የሴቶች ማኅበር እያለ ። በሙያ ተደራጅቷል - የመምህራን የሕግ የፋርማሲ የስታቲክስ ወዘተ እያለ በዕድሜ ተደራጅቷል - የወጣቶች የአዛውንቶች እያለ በቋንቋ ተደራጅቷልአማራ ትግሬ ኦሮሞ እያለ በብሔር ተደራጅቷል-ትግሬ ወርጂ፣ ወለኔ ጠምባሮ ደንጣ  ዱባሞ  ከችንችላ እያለ  በአምራችነት ተደራጅቷል - የጨው፣ የአሳ፣ የቡና፣ የማር፣ የኦፓል ወዘተ እያለ በጉዳት ተደራጅተል - አካል ጉዳተኛ ማየት የተሳነው መስማት የተሳነው እያለ በቀለብ ተደራጅተል ስኳር ጨው ዘይት፣ ጤፍ ሸማች እያለ በንብረቱ ተደራጅቷል - የታክሲ የአውቶብስ፣ የገልባጭ የቦቲ  እያለ በኪነጥበብ ተደራጅቷል-ሙዘቀኛ፣ ሠዓሊ ፣ ደራሲ ፣ ፊልም ሰሪ ፣ ቀራጺ፣ ቴአትረኛ እያለ ።  አንበሳ አጋዘን ጎሽ ሳላ ለማስገደል ተደራጅቷል - አሳዳኝ እያለ   ሌላው ቢቀር አንድ ለአምስት ብሎ በቁጥር ተደራጅቷል በዚህም ምክንያት የመደራጃ ርእስ ተሟጦ አልቋል።

እናም አንድ ቀን እስካሁን ክፍት በሆነው በተመሳሳይ ስም ተደራጁ መባሉ አይቀርም ያኔ ሎዳሞ  ከሎዳሞዎች ቶሎሳ ከቶሎሳዎች ደም መላሽ ከደመላሾች ጀርባ ይሰለፋሉ በርግጥ የስማችን ድግግሞሽ በርካታ በመሆኑ ሰልፉን በሥርዓት ለመምራት አስቸጋሪ መሆኑ አይጠረጠርም መቼም ሰልፉን ነገር እንደማይገባው ፓርላማ መበተን የዋህነት ስለሚሆን በስም ብቻ ሳይሆን እስከነአባታቸው ተመሳሳይ የሆኑት ተሰባስበው መላ የሚፈልጉበት ዘዴ ይፈጠራል  ። ርግጥ ነው አሁንም ክፍተቱ ሊደፈን አይችልም ተመሳሳይ ወፎች እንጂ ተመሳሳይ ስሞች አንድ ላይ ላይበሩ ይችላሉ አንደኛው በቀለ ጎሰኝነትን እንዋጋ ሲል ሌላኛው በቀለ የሙሰኛ አመራር ጉዳይ እንቅልፍ ይነሳው ይሆናል ለአንደኛዋ ትዕግስት የደረጃ እድገትና ሹመት ላይ የሚሰራ ግፍ የሚያንገበግባት ሲሆን ሌላኛዋ ትዕግስት የዲግሪና ዲፕሎማዎች ሳጥኗ ውስጥ መሻገት ነው የሚያስጨንቃት ።

ምናልባት ስምና ፍላጎትን ማቆራኘት የተሻለ ሊሆን ይችላል የእናንተን አላውቅም ፣ እኔ ግን ከሞክሼዎቼ ጋር መደራጀት የሚያስችለኝ የማርያም መንገድ ይታየኛል ለአብነት፣
አለማየሁ ገላጋይ
አለማየሁ ታዬ
አለማየሁ /ህይወት
አለማየሁ ማሞ
አለማየሁ ዲባባ
አለማየሁ ታደሰ
የሚባሉ ኪነጥበብ የጠራቻቸው ሰዎችን አውቃለሁ ሌሎችም በሂደት ይቀላቀላሉ የክበቡ ወይም የማህበሩ ወይም የሊጉ አላማ ምን ይሆናል? ይሄ የምልአተ ጉባኤው የቤት ሥራ ቢሆንም ብዙ መነሻ ሀሳቦችን መደርደር ይቻላል በትርጉም የሚቀራረቡ ስሞችን ለምሳሌ ያህል ውባየሁ ፣ ድንቃየሁ እጅጋየሁ ወዘተ በማሰባሰብ በተለጣፊነት ሳይሆን አጋር ማኅበራት የሚሆኑበትን ስልት ይነድፋል በሂደት በፌዴሬሽንም ሆነ ኮንፌዴሬሽን ውህደቱ እውን እንዲሆን በትጋት ይሠራል በሌላ በኩል ብዙአየሁ ስንታየሁ የመሳሰሉ መጠሪያዎች ያዩት ነገር ደስታ ይሁን ሀዘን ግልጽ ስላልሆነ እግረ መንገድ መልስ የሚሰጥ ኮሚቴ ተቋቁሞ ሥራውን ያቀላጥፋልይህም በኋላ ሊመጣ የሚችለውን የአባልነት ጥያቄ ከወዲሁ ግልጽ ለማድረግ ያስችላል።

በብዙ አካባቢዎች አለማየሁ የሚለው መጠሪያ የወንድ ነው አልፎ አልፎ ግን አለማየሁ የሚባሉ ሴቶችም እንዳሉ ተደርሶበታል ሴቶች ይህን ስም ለምን ሊጠቀሙበት ፈለጉ? ማኅበሩ የውህዳኑን መብት እንዴት ሊያስተናግደው ይችላል? የሚሉ ጥያቄዎችንም ማጥናት የኮሚቴው ሌላኛው ተግባር ይሆናል

አለማየሁ በሚል መጠሪያ የግጥም የአጭር ልቦለድ የወግና የስላቅ ወድድር በማዘጋጀት አለማየዎች እንዲወዳደሩ ይደረጋል። አለማየሁ የተባሉ ባለሃብቶችን ገንዘብ በመለመን አሸናፊዎች ዓለሙን አይቶ የተዳከመ መኪና ይሸለማሉ ባገለገለው መኪና ዓለምን ባይሆንም የክልል ከተሞችን ይጎበኙበታል ዞሮ ዞሮ አሸናፊው በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ዓለሙን እንዲቀጭ እናደርገዋለን።

ከእንግሊዝ ኤምባሲ ጋር ቅርበት በመፍጠር የልዑል አለማየሁን መካነ መቃብር ለመጎብኘት ጥረት ይደረጋል የሀሳቡ መነሻ ጉብኝት ይሁን እንጂ ዋነኛው ተግባር ብዙ ስላልተባለለት ተጠባባቂ ንጉሥ ብዙ አጥንቶ ዳጎስ ያለ መጽሐፍ ማሳተም ነው ይህ  መጽሐፍ ሀገራዊ ቅርስ ነው ተብሎ ቢታመንም መንግሥት ለምንጠይቀው የማሳተሚያ ገንዘብ ጥያቄ በጎ ምላሽ ይሰጣል ተብሎ አይጠበቅም በመሆኑም በአለማየሁ እሸቴ የሚመራ ለስላሳ ጥዑም ዜማ በአንድ መድረክ በአለማየሁ ፈንታ የሚመራ የሽለላና ፉከራ ጥበብ በሌላ መድረክ ተዘጋጅቶ ገቢ ለማሰባሰብ ጥረት ይደረጋል  

በሂደት የሬዲዮ አየር ሰዓት በመግዛት የአለማየሁ ድምጽ የሚል ፕሮግራም ይጀመራል ፕሮግራሙ ከማዝናናት በተጨማሪ አለማየዎች እንዲነቃቁ በየክልሉ ተሰባስበው እንዲደራጁ ያበረታታል አለማየሁ ምንድነው ? እንደምንስ ተፈጠረ ? አለም ያየው ባለስሙ ነው ወይስ ልጅ ፈጣሪው? በስሙና በሰውየው መካከል ያለው ዝምድና ምንድነው? ዝምድና ከሌለ ደስታ አየሁ፣ ፍቅር አየሁ፣ በጎነት አየሁ የሚለውን ትርጉም እውነት ለማድረግ የሚያስችል አማራጭ አለ? ምን ያህሉ ነው ስሙን የሚታዘበው? ስሙ ከብዶት የቀየረ ወይም አለምና አሌክስ በማለት ስጋቸውን የቀነሰ አለ? በእነዚህና በመሳሰሉ ጉዳዮች ላይ ክርክር ወይም ምርምር ሊያደርግ ይችላል

አለምነሽ እና አለሚቱ ከመሳሰሉ ተቀራራቢ ሴት አቻ ማኅበራት ጋር ግንኙነት በመፍጠርዓለምበተሰኘው የጋራ ነጥብ ላይ ሃሳባቸው እንዲፋጭና እንዲጋጭ ይደረጋል ብልጭታው ፍቅርና ትዳርን ሊመሠርት ይችላል ብልጭታው አለም የተሰኘ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት እንዲፈጠር  ምክንያት ሊሆን ይችላል ብልጭታው አለም የተሰኘ የፖለቲካ ድርጅት ወይም አክስዮን እንዲወለድ መንገድ ይከፍት ይሆናል ብልጭታው ምን የማይፈጥረው ነገር አለ ? …

መደራጀት እንግዲህ ጥቅሙ ብዙ ነው አለምበቃኝ መዉረድም እንደተጠበቀ ሆኖ

Thursday, May 4, 2017

የቴዲ አፍሮ ትሪያንግል


አዲሱን የቴዲ አፍሮ አልበም አጣጣምኩት ። ከላይ ወደታች ፣ ከታች ወደላይ ተመላላሰኩበት ። ከአንዱ ጫፍ ወደ ሌላው ስዘል ውበቱን ፣ ስልቱን ፣ ስሜቱንና መልእክቱን ለመለካት እየሞከርኩ ነበር ። በዚህ የወዲህ - ወዲያ ቅኝቴ የፈጠርኩት ስእል ትሪያንግል ሆነ ።

እኩል ሶስት ማእዘን ባለው ቅርጽ ላይ ሶሰት ሙዚቃዎች ከፍ ብለው ተመለከትኩ ። በአንደኛው ጫፍ ‹ ኢትዮጽያ › ፣ በሁለቱ ጎኖች ደግሞ አጼ ቴዎድሮስ እና ማር እስከ ጧፍ ። የእነዚህ ሶስት ሙዚቃዎች ተምሳሌትነት ከፍ ያለ ነው ። የሶስቱም ዘፈኖች ግጥማዊ ክህሎት ምጡቅ ነው ። ትሪያንግሉ በራሱ ለመቆም ምሉዕ ቢሆንም አንዳንዴ ሀገር ከሚያምሰው የነገርና ምቀኝነት ሱናሜ ለመትረፍ የሚያስችልም ስንቅ አንግቧል ። ኢትዮጵያ ውስጥ / ሀገር/ ፣ አጼ ቴዎድሮስ  ውስጥ / ጀግንነት /  ማር እስከ ፍ ውስጥ ደግሞ / ፍቅር / ተወከሎ ይገኛልና ።
                                                                                                       ኢትዮጽያ
                  አጼ ቴዎድሮስ                                                                               ማር እስከ ጧፍ              

        
‹ ኢትዮጵያ › ቀደም ብሎ የተለቀቀ ነጠላ ዜማ ቢሆንም ከሙሉ አልበሙ ጋር ሳየውም መጠሪያ መሆኑ አያንስበትም ። ሙዚቃው የትልቅ አጀንዳ ባለቤት ነው ። የሞት- ሽረት ጠርዝ ላይ የሚገኘውን ኢትዮጵያነት ይሞግታል ። ኢትዮጵያነት ከዘጠና ሚሊየን ህዝቦች ውህደት በላይ መሆኑን ለማሳየት ባንዲራው ያለውን ክብርና ጸጋ ይዘክራል ።

              « እንኳን ሰማይ ላይ ባንዲራሽን አይቶ
                ኢትዮጵያ ሲባል ማን ዝም ይላል ሰምቶ »

ቴዲ የፖለቲካ ኩርፊያና በደል ማንነትን ለመካድ መሰረት ሊሆን አይችልም ባይ ነው  « ቢጎል እንጀራው ከመሶቡ ላይ ፣ እናት በሌላ ይቀየራል ወይ » በርግጥም ዓለም የሉሲ ልጆች ፣ የነጻነት ምሳሌዎች እያለ የሚጠራቸው አበሾች በየአደባባዩ በርካታ ትናንሽ ባንዲራዎች ተሸክመው ሲያያቸው ያዝናል ። በትልቁ ባንዲራችን ፍቅር ወድቀው የራሳቸውን ለመቅረጽ መነሻ ያደረጉ አፍሪካዊያንም ከንፈራቸውን መምጠጥ ከጀመሩ ቆይተዋል ። እናም የሰንደቅ እና ሀገር ጉዳይ ውሃ ቢወቅጡት እንቦጭ እንደሆነ ቀጥሏል ።

  « ተዉኝ ይውጣልኝ ልጥራት ደጋግሜ
    ኢትዮጵያ ማለት ለኔ አይደል ወይ ስሜ » ያስብላል

ይህ ሙዚቃ ብቻውን የተለቀቀ ሰሞን እንካሰላንቲያ ያማዘዘውም የትሪያንግሉ አንደኛው ማእዘን ሰለሆነ ነው ። ኢትዮጵያነት ግን ያው የነብር ቆዳነት ነው ። ብዙ ሂትለሮች በለስ ቀንቷቸው ኢትዮጵያዊያንን ማጥፋት ቢችሉ እንኳ ኢትዮጵያ የተሰራችበትን ታሪካዊ ፣ ሃይማኖታዊ እና ሳይንሳዊ አሻራዎች መደለዝ አይችሉም ።

በርግጥ አንዳንዶችም ሙዚቃውን አሰታከው የዋህ አስተያየት ሲሰጡ ተሰምተዋል ። አንደኛውና ዋነኛው ወቅትን እየጠበቁ እንዲሁም ሰዎችና ክስተቶች ላይ መዝፈን የጥበብ ሰው ባህሪ አይደለም የሚል ነው ። ይህ አባባል የጥበብ ምንነትን ካለማወቅ ይነሳል ። የጥበብ ግብ የገሃዱን ዓለም ጥሬ እውነት ጥበባዊ በሆነ ኩታ አስውቦ መገኘት ነው ። ስለዚህ ሰዎች እና ክስተቶች ከብዙ በጥቂት የሚቀዱ ምንጮች ናቸው ማለት ነው ።

ሌላው የቴዲ አፍሮን የጥበብ መንገድና ስልት አለመገንዘብ ነው ። ይህ ድምጻዊ በአጭር ግዜ ውስጥ የማይታመን ተቀባይነት ያገኘው  ለምንድነው ? የሚለውን ጥያቄ ስንመልስ  መስመሩን እናገኛለን ። ቴዲ የድፍረት ፣ የፈጣንና ሰፊ ምናብ ባለቤት ነው ። ማንም አቀንቃኝ የሚፈራውን የአንድነትና የመገንጠል ጉዳይ ሲፈልግ አስውቦ ያዜማል ። በፈጣን ምናቡ ወቅታዊና ትኩስ እውነቶችን የውበትና ተዝናኖት ክንፍ ሰርቶላቸው አድማጩ ቤት ድረስ እንዲያንዣብቡ ያደርጋቸዋል ። 

ፖለቲካ ያስፈራራቸውን ወይም ሀገር የረሳቸውን ጀግኖች በፈጠራ ሃውልት ያንጻቸዋል ። እነዚህ ሃውልቶች እንደምናውቃችው አይነቶች የተመረቁ እለት ብቻ የሚነገርላቸው አይደሉም ። ሃውልቶቹን በፍቅር ይተክላቸዋል ፤ እኔና እናንተ ደግሞ ደምና ስጋ ሞልተን ስለነፍሳቸው ዘወትር እናዜማቸዋለን ። በግጥም ዘርፍ « የጸጋዬ ቤት » እንደምንለው ሁሉ ይህን የዜማ አተያይም « የቴዲ አፍሮ ስልት » ማለት ይቻላል ። ታዲያ ይህን በእሱ ፍቃድ ብቻ የሚገኝ ሃያል ስልት እንዳይቀጥል የሚፈልግ ጅላጅል ተደራሲ ማነው ?

የትሪያንግሉ ሁለተኛው ማእዘን « አጼ ቴዎድሮስ » ነው ። በዚህ ዜማ የጀግንነት ከፍታ ታይቶበታል ። የታሪኩ ባለቤት አጼ ቴዎድሮስ ለሀገራቸው ክብር በመቅደላ ተራራ ያደረጉት ተጋድሎ ተዘርዝሯል ። ቴዎድሮስ የተከፋፈለችውን ኢትዮጽያ አንድ ለማድረግ በተደረገው ትግል የአንድነት ምልክት ናቸው ። ለዛም ነው ድምጻዊው
 « ጎንደር ጎንደር የቴዎድሮስ ሀገር
   የአንዲት ኢትዮጽያ ዋልታና ማገር » የሚለው

ቴዎድሮስ በኢትዮጽያ የመሪዎች ታሪክ ልዩ ቦታ ያገኙትም የተከፋፈለች ወይም የተሸነፈች ሀገርን ላለማየት መስዋዐት በመሆናቸው ነው ። ከራስ በላይ ንፋስ የሚል መሪ በችግር ግዜ እጁን ይሰጣል ወይም ይሰደዳል እንጂ ራሱን አያጠፋም ። ድምጻዊው ይህን መስዋእትነት ያስተሳሰረው ከሰንደቅ ዓላማ እና ከቀጣይ መልዕክት ጋር ነው ።
   « ጨክኖ ካሳ ጋተና ኮሶ
     ሞተ ለአንድ ሀገር ባንዲራ ለብሶ »           
      
ቀጣዩ መልዕክትም የተላለፈው በባንዲራው ድልድይነት ነው ። ይህን ባንዲራ ማንሳት ብቻ ሳይሆን የተዳፈነውንም ጀግንነት በብዙሃኑ ላይ እንዲጋባ ይፈለጋል ። ሀገር ለመስራት ጀግኖች ያስፈልጋሉ ። የግኖችን ራእይ ተግባራዊ ለማድረግ የወራሾች ሚና ወሳኝ ይሆናል ። ወራሾች የሞተውን ጀግና በማሰብ ከማለቃቀስ ይልቅ የአሟሟቱን ሚና በመረዳት ላይ እንዲተጉ ይጠበቃል ። ይህን ግን እውን ለማድረግ ቀላል አይደለም ።
 « ግመሌን ላጠጣት ቀይ ባህር ተጉዤ

    አንድ ገመድ አጣው ልመልሳት ይዤ » የሚለው ስንኝ የአንድን ጠንካራ ወራሽ ስጋትና ተስፋ መቁረጥ በምሳሌ የሚያሳይ ነው ። የአጼ ቴዎድሮስን ህልም እውን ለማድረግ ወቅታዊው የፖለቲካ ምህዳር ጠባብ ቢሆንም መልእክት አደራሹ ከያኒ ግን የጋመ ፍላጎቱን ጾታ ሳይለይ ለማስተላለፍ ‹ ሹሩባ › የሚለው ቃል የተመቸው ይመስለኛል ።
  « አንጡ ቆርጣችሁ ከሹሩባው ላይ
    ኪታብ እንሰር እንዳንለያይ »

የትሪያንግሉ ሶስተኛው ማእዘን « ማር እስከ » ይሰኛል ። ሙዚቃው የተመሰረተው የፍቅር እስከ መቃብር ድርሰት ላይ ነው ። ይህ መጽሀፍ በእንግሊዘኛ የመተርጎም እድል ቢያጋጥመው ኖሮ ዓለም ‹ የድርሰት ሉሲ › በኢትዮጵያ ተገኘ ማለቱ ባልቀረ ነበር ።
ቴዲ ይህን ትልቅ መጽሀፍ እንደገዘፈ ለማቅረብ ሞክሯል ። ገጸባህሪያቱን አሳይቶናል ። በተለይ ተፈቃሪዋ ሰብለ ወንጌል መልከ ብዙ ሆና ተስላለች - ብራና ፣ ንብ እና ማር ። ብራና ሆና የፍቅር መወድስ እናነብባታለን ። ንብ ሆና በአንድ በኩል ትጋትዋን በሌላ በኩል የጥቂት አመታት እድሜዋን እንዲሁም ማር ሆና ጣፋጭነትዋን በተለዋጭ ዘይቤ እንመለከታለን ። ይህን ውብ ቋንቋ ቅኔያዊ በሆነ መስተጋብር እያስተሳሰረ አቅርቦታል ።

 « ላሳደገኝ ደብር የስለት ልጅ ሆኜ
   ካህን እንዴት ይፍታኝ ያንቺ እስረኛ ሆኜ
   ማር ጧፍ ሆኖ ገባ - ከመቅደስ
   ነዶ ለኔ ጸሎት ሊያደርስ  »

ቢጫ ለብሳ ገዳም የገባችውን ሴት መንጥቆ ለማውጣት የሚደረገው  ትግል ጠንካራ ነው ። ሆኖም የቱንም ያህል አዋቂ ቢኮን ፍቅር አንበርካኪ መሆኑን እንረዳለን ።

  « ለካ ሰው አይድንም በደገመው መጽሀፍ
    እንደ ሰም አቅልጦ ፍቅር ካደረገው ፍ »         
የቴዲን ትሪያንግል እንደ ጋሪ ለመግፋት ብንፈልግ አራት ጎማዎች ያስፈልጉናል ። ሰምበሬ ፣ አና ንያቱ ፣ ያምራል እና ኦላን ይዞ በአቀራረብ ስልታቸውና ሳቢነታቸው የእኔ ምርጫዎች ናቸው ።           
 ኦላን ይዤ አላፍርም ይህን አውቃለሁ
 ወደ ፍቅር ልሂድ ምን እጠብቃለሁ
 ወደ ፍቅር ጉዞ ተያይዞ
 ቂምን ከሆድ ሽሮ
 ኦላን ይዞ …                                                                  

Sunday, February 26, 2017

አድዋ - ባለ ሺህ ገጽ ምርጥ መጽሀፍ



‹‹ ዳዊት እጁን ወደ ኮሮጆው አግብቶ አንድ ድንጋይ ወሰደ ፤ ወነጨፈውም ፡፡ ድንጋዩ በግዙፉ ጎልያድ ግንባር ተቀረቀረ፡፡ በወንጭፍና በድንጋይ አሸነፈው ›› 

ይህ ጥቅስ የአድዋ ድል መግለጫ ወይም Synopsis ሊሆን ይችላል ። በርግጥም ለእኔ የኢትዮጽያና የኢጣሊያ ጦርነት የዚህ ጥቅስ ሃሳብ እኩያ ነው ፡፡ ጦር ፣ ጎራዴና ውስን ቆመህ ጠብቀኝን የያዘ ህዝብ በውትድርና ጥበብ ከላቀ ፣ በትላልቅ መድፎች በታጠረ   በአጠቃላይ ዘመናዊነትን ከታጠቀ አስገባሪ ጦር ጋር ተናንቆ ድል ጨበጠ ፡፡ ጎልያድ ዳዊትን በትር ይዘህ የምትመጣብኝ እኔ ውሻ ነኝ ? ወደ እኔ ና ስጋህንም ለሰማይ ወፎችና ለምድር አራዊት እሰጣለሁ ብሎት ነበር ። የኢጣሊያ ወታደሮችም ቆመህ ጠብቀኝና ጉራዴ ታጥቀው የሚያቅራሩትን ጀግኖች በንቀት እያዩ በሳቅ ይዝናኑባቸው እንደነበር ግልጽ ነው ። የተናቀ ያስረግዛል እንዲሉ የማይታመን ፣ ብዙዋችን የሚያስደምም ፣ ከአንጸባራቂ ማዕድናት የላቀ ዋጋ ያለው ክስተት በአድዋ ተራራ ተገኘ፡፡
በአድዋ ተራራ ላይ አያሌ ዳዊቶች ተፈጠሩ ።

ቅድመ ታሪክ

· 
                                   አዋጅ አዋጅ የደበሎ ቅዳጅ
የሰማህ ላልሰማ አሰማ….. 
በሚል ነጋሪት የሚኒሊክ ታማኞች ለህዝቡ ቀጭን ጥሪ ማስተላለፍ ጀመሩ ፡፡ ኢትዮጽያና ጣሊያን ውጫሌ ላይ የተፈራረሙት ስምምነት በተለይም አንቀጽ 17 ሁለት ትርጉም በመያዙ ሀገሮቹ ትታዘዘኛለህ - አልታዘዝህም በሚል ወደለየለት ግጭት ለመግባት ተገደዱ ፡፡ ንጉሱም ‹‹ ጉልበት ያለህ በጉልበት እርዳኝ ፣ ጉልበት የሌለህ ለልጅህ ፣ ለምሽትህ ፣ ለሃይማኖትህ ስትል በጸሎት እርዳኝ ወስልተህ የቀረህ ግን ኋላ ትጣላኛለህ ፡፡ አልተውህም …. ዘመቻዬ በጥቅምት ነውና የሸዋ ሰው እሰከ ጥቅምት እኩሌታ ድረስ ወረይሉ ከተህ ላግኝህ ›› ሲሉ አዘዙ ፡፡
·                 
ወደ አድዋ የተመመው የአጼ ሚኒሊክ ጦር በ10 የጦር መሪዋች የተከፈለ ሲሆን ቁጥሩም ከ73 ሺህ በላይ ነበር ፡፡ እቴጌ ጣይቱ ፣ ራስ መኮንን ፣ ራስ መንገሻ ፣ ራስ ሚካኤል ፣ ራስ ወሌ ፣ ራስ ወ/ጊዮርጊስ ፣ አዛዥ ወ/ጻዲቅና ደጃች ተሰማ ናደው ዋናዋቹ ነበሩ ፡፡ በጣሊያን በኩል በአራት ጄኔራሎች ተዋቅሮ ቁጥሩ 22ሺህ የሚደርስ ነበር ፡፡ ባራቲየሪ ፣ አልቤርቶኒ ፣ ባልዲሴራና ዳቦርሜዳ አዛዦቹ ነበሩ ፡፡ በኢትዮጽያ በኩል የነበረው አቅም 22ሺህ ፈረሰኛ እዚህ ግባ ከማይባል የጦር መሳሪያ ፣ ጋሻና ጦር ጋር ሲሆን ጣሊያን 20ሺህ ዘመናዊ ጠመንጃዋች ከ66 መድፎች ጋር አሰልፋ ነበር፡፡

የአድዋ ጦርነት የካቲት 23 ቀን 1888 ዓም በዕለተ እሁድ በጠዋቱ ተጀመረ ፡፡ በብዙ መስዋዕትነትም ምሽት ላይ በኢትዮጽያ አሸናፊነት ተደመደመ ፡፡ ድራማው አሰቃቂ ነበር ፡፡ ፊታውራሪ ገበየሁ ጉራዴ መዘው ሲገቡ በጥይት ተመቱ ፡፡ ይሄኔ የኢትየጽያ ጦር መደናገጥና መረበሽ ታየበት ፡፡ የጄኔራል አልበርቶኒ በቅሎ በጥይት ሲመታ ጄኔራሉ ወደቀ ፡፡ ወዲያው በኢትዮጽያ አርበኞች ቁጥጥር ስር ዋለ ፡፡

አሁን ደግሞ የጣሊያን ጦር ተፈታ ፡፡ እረ ጎራውና የፍየል ወጠጤው በአንድ በኩል ሲሰማ የቁስለኛው የድረሱልኝ ጩሀት በሌላ በኩል አካባቢውን ገሃነም አደረገው ፡፡ በኢትዮጽያ በኩል 4ሺህ ሰው ሲሞት 6ሺው ቆሰለ ፡፡ በጣሊያን በኩል 5179 ሲሞት 1429 ያህሉ ቆሰለ ፡፡ 1865 ያህሉ ተማረከ ፡፡ በኢትዮጽያ በኩል የደስታ ፈንጠዝያ ሲከበር ጣሊያኖች ሮምን በተቃውሞ ሰልፍ ደበላለቁት ፡፡ አጼ ሚኒልክ በሀገር በቀል ሻምፓኝ ሲታጠቡ ጠ/ሚ/ር ክሪስፒ ሽምቅቅ እንዳለ ስራውን ለቀቀ ፡፡

የድህረ ታሪክ ሽፋን

ጄኒራል ባራቲየሪ ለሮም ህዝብ ‹‹ በቅርብ ቀን ሚኒልክን በቀፎ ውስጥ አስሬ ሮማ አመጣዋለሁ !! ›› በማለት ፎክሮ ነበር ፡፡ በወቅቱ ከነበረው የሁለቱ ሀገራት ልዩነት አንጻር ለዚህ ንግግር ድጋፉን መቶ መቶ የማይሰጥ ማነው ? ጸሃይ በምስራቅ አቅጣጫ መውጣት ታቆማለች የሚል ቋሚ እውነት ለመሻር የሚከጅል እብድ ከየት ማግኝት ይቻላል ?

ግና ዕድሜ ልክ ልናከብራቸው በሚገባን የቀድሞ ትውልዶች ልዩ መስዋትነት የማይታመን ድል ተገኘ ፡፡ ይህ እንዴት ይሆናል ? ዓለም በተገቢና በጦርነት መስፈሪያ ሂደቱን ለክቶ ውጤቱን አስልቷል ፡፡ የኢትዮጽያን ሩጫ በፎርፌ ከመሸነፍ ይልቅ ተሳትፎን ለማጠናከር የሚረዳ ያህል ነበር የታመነበት ፡፡ ታዲያ ፍጥጥ ያለው ውጤት እንዴት ተቀየረ ? ዳኛው ምን ነካው ? ለድሃ ፣ ጉቦ ለማይሰጥ ፣ ዘመድ ወዳጅ ለሌለው ተከሳሽ አይደለም ትናንት ዛሬስ ቢሆን ፈርዶ ያውቃል እንዴ ? ይሄ ተጠራጣሪነትን / skepticism / የሚያጠናክር ፍልስፍና ነው ? ይሄ ልክ እንደ አሰምፕቶት / asymptote /  መስመር ላይ ለመተኛት የማይችል አልጄብራ ነው ? ይሄ በነሌኒንም ሆነ በነ ጆህን ሎኬ የፓለቲካ አስተምህሮ ውስጥ ምዕራፍ ያላገኝ አጀንዳ ነው፡፡

ለዚህም ነው ብዙ ጸሀፍት የአድዋን ድል የሚገልጹበት ቋንቋ አስገራሚ የሚሆነው ፡፡ በአፍሪካ ውስጥ ታላቅ የተወላጅ ሃይል መነሳቱ ታወቀ ያለው በርክሊይ አበሾች አደገኛ ህዝቦች መሆናቸው ከኦሪት ዘፍጥረት ጀምሮ ተጽፎላቸዋል በማለት የተዘነጋ እውነት እንዲዋጥ የገፋፋው ፡፡ ማርገሪ ፐርሃምም አድዋ ኢትዮጽያን የዓለም ካርታ ውስጥ አስገባት በማለት መሳጭ አስተያየት ሰጥቷል ፡፡
ይህን ታሪክ ለምን ማኮሰስ አስፈለገ ?
እስካሁን ይህን አንጸባራቂ ድል ስናከብር ያላጓደልነው ዓመታቱን መቁጠር ላይ ነው ፡፡ እያከበርን የምንገኝው አድዋ አደባባይ በመገኘት የማርሽ ባንድ ማሰማት ፣ የአርበኞችን ቀረርቶ መከታተል ፣ የአስተዳደሩ ተወካይ ያበባ ጉንጉን ሲያስቀምጡ መታዘብ ፣ ግንኙነቱ የራቀ ንግግር ማዳመጥ ነው ፡፡ የቀጣዩም ዓመት መርሃ ግብር ከዚህ አይርቅም ፡፡ እውነት ይህን ታሪክ እንዴት እያነው ነው ? እንደምን እየተረጎምነው ነው ? በምን አይነት መልኩስ እያከበርነው እንገኛለን ?

እንደ ድሉ ታላቅነት ለምን አድዋ ተራራዋች ስር አላከብርንም  ? የአባቶቻችንን ክብር የሚያጎላና የመጪውን ትውልድ መንፈስ የሚያጠናክሩ ልዩ ልዩ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶቸን ማቅረብ እየተቻለ አልተደረገም  ፡፡ እንደ ካፓርት የሚሞቁ ታሪክ ቀመስ ጥናቶችን ማስተላለፍ እየተቻለ አልተፈለገም ፡፡ የውጪ ቱሪስቶች እንደ ጥምቀትና መስቀል እንዲጎርፉ የሚያደርግ ቋሚ ስራዋችን መስራት ቢፈለግ የሚከብድ ባልሆነ ነበር ፡፡ የአድዋን ሜዳዋች በሙዚየምና በመዝናኛ አገልግሎቶች ፣ የታሪካዊ ተራራዋቹን ግርማ ሞገስ ደግሞ እንደ ገና ዛፍ ማብረቅረቅ ወገቤን የሚያሰኝ አይደለም - ቢያንስ ለአንድ ሁለት ተሃድሶ የሚወጣውን ወጪ ቆንጠጥ አድርጎ መያዝን ነው የሚጠይቀው ፡፡ እንደ ቻይና ግንብ መወጣጫ ሰርቶም መዳረሻው ላይ የፈለገ እንደ ጀግኖቹ ዘራፍ እያለ እንዲያቅራራ ፣ ያልፈለገ ደግሞ የአባቶቻችንን የከበረ መስዋዕትነት ከልቡ ተመስጦ እንዲያስብ ማድረግ ፍጹም የሚያስደስት ነው ።

ሞኝ አሞራ ያባቱን ዋሻ ይጠየፋል አሉ ። አሞራው ዋሻው የቀፈፈው በተራ ጅልነቱ ነው ። እኛ የቀድሞ ማንነታችንን ጥቂት እንደቀረው ደናችን እየጨፈጨፍን ነገ የሚያጠፋንን በረሃ ለመፍጠር የምንተጋው ባለማወቅ ሳይሆን በተራ ጥላቻና ትዕቢተኝነት በወለደው የዘቀጠ አስተሳሰብ ነው ።

ግዜ የሰጠው ቅል ድንጋይ ይሰብራል እንዲሉ ከታላቁ የአድዋ ድል ጀርባ ታላቁ አጼ ሚኒሊክ አሉ በሚል የተጃጃለ ሃሳብ የህዝቡን መብትና ጥያቄም እየጨፈለቅን ነው ። በርግጥም አፍሪካዊ ድሉን አስተባብረው ኩራት እንዲፈጠር የአንበሳውን ድርሻ የወሰዱት አጼ ሚኒሊክ ናቸው ። ታላቅን ጀግና እንደታላቅነቱ ማክበር እንጂ በሀገር ውስጥ ጦርነት ... ቆርጧል ፣ ... ተርትሯል  እያሉ በታሪክ ውስጥ እንዳላለፈ ሁሉ ስሙን ለመደምሰስ የሚደረግ ሩጫ የትም አያደርስም ። ምክንያቱም ሰቅጣጭ የጦርነት ታሪክ ባላት ኢትዮጽያ ግዜ ሰጥቶት የነገሰው መሪ ሁሉ የራሱን ስርዓት ለማስጠበቅ ንጹሃንን ገድሏል ፣ ጨፍጭፏል … እስኪ ይህን አላደረኩም የሚል የፖለቲካ ስርዓት / ሌላው ቀርቶ ጠመንጃ የታጠቀ አማጺ ድርጅት / እጁን ያውጣ - በፍጹም አይገኝም ።
ይህ እንዲሆን ባይፈለግም ሆኗል ። ካለፈ ስህተት ተምሮ ማለፍ ይሻላል ወይስ ታሪካዊ ድሉን በመጨፍለቅ የማጣጣት ስራ መስራት ? ሚኒሊክ ሰዎችን ስለገደሉ ሃውልታቸው ይፍረስ ? የአድዋ ድል ትቢያ ይልበስ ? ጀግንነታቸውን ከርቸሌ አስረን ስማቸውን በየሚዲያውና በየስብሰባው እናጥፋ ?

ይህን ሁሉ በማድረግ በህዝቡ ውስጥ ያላቸውን ሚዛን ደፊ ፍቅርና ክብር መቀነስ አይቻልም ። ምናልባት ይበልጥ በጣም እየገነኑ ይሄዳሉ እንጂ ። ስለዚህ አስተዳደራዊ ችግራቸውን እንደመማማሪያ እያነሳን ዓለም የተቀበለውን ድልም በተገቢው መልኩ ማስተናገዱ ይበጃል ። ለፖለቲካ ፍጆታም ሆነ ከታሪክ ተጠያቂነት ለመዳን የተሻለው መንገድ ይኀው ነውና ።

የድህረ ታሪኩ አስኴል
የአድዋ ድል ውጤቱ ብዙ ነው ፡፡ ባህልን ለመውረር የተደረገ ስልትን ያኮላሸ ድርጊት ነው….. ትልቅ ስብዕናና ድፍረት ያላቸውን ህዝቦችንና የጦር መሪዋችን ለአለም አስተዋውቋል….. በጭቆና ስር ለነበሩ ጥቁር ህዝቦች በሙሉ ተስፋና መነቃቃትን ፈጥሯል….. የአውሮፓ ተስፋፊዎች በሰው ልጆች ላይ ሲፈጽሙት የነበሩትን ኢ- ሰብአዊና ኢ- ፍትሃዊ ስርዓት ቆም ብለው እንዲመረምሩ ያሰገደደ ነው ፡፡ ይህ ድል ክብርና ነጻነታቸውን የተገፈፉ የዓለም ህዝቦች በሙሉ ከጭቆና ቀንበር እንዴት መውጣት እንደሚችሉ የሚያስተምር ባለ ሺህ ገጽ ምርጥ መጽሀፍ ነው፡፡