Tuesday, July 16, 2013

ጥርስ የሚፍቁ መስሪያ ቤቶች



1 . ‹‹ እንደ ተቋም ጥፋት ስላጠፋን ይቅርታ እንጠይቃለን ›› የሚለው መግለጫ የሚጠበቅ ስለነበር የሚያስገርም አልሆነም ፡፡ አስገራሚ የሆነው የሚጠበቀው መፍትሄ ሊፈታ ያልቻለ እንቆቅልሽ መሆኑ ነው ፡፡ የተጎዳውን ህዝባዊ ስሜት ለመጠበቅ ከሞራልና ህግ አንጻርም ሊሰራበት ያልተቻለን ስልጣንን ለሚሰራ አካል ማስረከብ ግድ ነውና አመራሩ ለራሱ ቀይ ካርድ እንደሚያሳይ ተጠብቋል ፡፡
ግን አልሆነም ፡፡

‹‹ ሁለት ቢጫ ማየት በምንያህል ተሾመ ይብቃ ! ›› ሲል የአቋም መግለጫውን አሰማ ፡፡ ይህ መግለጫ ደረቅ አይሆን ዘንድም ጥቂት የእግር ኳሱና የአመራሩ አባላት በጥፋተኝነት ቅባት እንዲዋዙ ተደረገ ፡፡ የፌዴሬሽኑ አመራር አካላት በህዝብ ለቀረበላቸው የልቀቁ ጥያቄ ‹‹ በክረምት ቤት አይገኝም ! ›› በሚል ሰበብ ለራሳቸው የወራት እድሜን ጨምረዋል ፡፡ በውስጣቸው  ግን  ‹ ይህ ስልጣን በመልቀቅ ሀብታም የሆነው የአውሮፓ ፌዴሬሽን አይደለም ! › ማለታቸው ይገመታል ፡፡

መቼም ይህ ፌዴሬሽን እንደ ሁላችንም ጨዋታ ተመልካች እንጂ መንገድ አመላካች አልሆነም ፡፡ ምንም ስራ እንደሌለበት ፊውዳል ክቡር ትሪቡን ላይ ቁጭ ብሎ ጥርሱን እየፋቀ ይባስ ብሎ ግራና ቀኝ ሰው መኖሩን በመዘንጋት የቆሸሸ ምራቁን ጢቅጢቅ .. በማድረጉ ስንቱን የዋህ ህዝብ ለማዲያትና ለጨጓራ በሽታ ዳረገ ?

2 . አንድ ሰሞን ከነዳጅ መውጣትና መውረድ ጋር ተያይዞ የትራንስፖርት ታሪፍን ለህዝቡ ይገልጽ ነበር ፡፡ ከቅርብ ግዜ ወዲህ ግን ድሃዋ አዲስ አበባ በሚያስገርም ሁኔታ ሀብታም ፎቆችን ሳይቀር ማፈራረስ ይዛለችእግረ ጠባቦቹም ሆኑ ሰፋፊዎቹ መንገዶቿ አዲሱን ሰርገኛ ለማስተናገድ በመፈራረስ ሽርጉድ አብዝተዋል ፡፡

ይህ ያልተጠበቀ ግርግር የአዲስ አበባ መንገድና ትራንስፖርት ቢሮን ያደናገረው ይመስላል ፡፡ አምስትና አስር ሳንቲም መጨመር የሚቻለው በእኔ እውቅና ነው ይል የነበረው ይኀው ተቋም ዛሬ ታክሲዎች 1 . 35 መንገድን 2 . 70 2 .70 መንገድን 3 . 70 በገዛ ፍቃዳቸው ሲያስገቡ ስልጣኑን ማስጠበቅ አልቻለም ፡፡ ለአብነት ያህል ከጦር ኃይሎች /ፍርድ ቤት በልደታ አድርጎ ሜክሲኮ በመድረሱ ብቻ ዋጋው መቶ ፐርሰንት መድረሱ በእጅጉ የሚያስገርም ሆኗል ፡፡

በዚህ ሁሉ የህግ ጥሰትና ዘረፋ መካከል ቢሮው ጋቢ ደርቦ ቁጭ ብሏል ፡፡ ከሶማሌ ባስመጣው ረጅም መፋቂያ ጥርሱን ደጋግሞ እየፈተገ ከራሱ ጋር እሰጥ አገባ ይዟል  ‹‹ ምን ይደረግ ታዲያ ! የልማት ጉዳይ ነው ፡፡ መንገድ በሌለበትስ ታሪፍን እንዴት ከፍና ዝቅ ማድረግ እችላለሁ ? ››
ከደረበው ጋቢ ይሁን ከግድየለሽነቱ ከመብራት ኃይል ቀጥሎ የላቀ የቸልተኝነት ኃይል እያመነጨ ይገኛል ፡፡ ይኀው ቸልታው ግን  ‹ እንኳን እናቴ ሞታ ድሮም አልቅስ አልቅስ ይለኛልየሚለውን የከተማ ነዋሪ ለጉዳት እየዳረገው ነው ፡፡ አዲሱ ሰርገኛ የሚመጣው ከሁለትና ሶስት ዓመታት በኃላ በመሆኑ ይህ ቢሮም እስከዛ ድረስ የአፉን መደገፊያ ላይጥል ነው ማለት ነው :: እስከዛ ድረስ ለሚደርሰው ብዝበዛ ማን እንደሚጠየቅ ለጸረ ሙስና ወይም ለእንባ ጠባቂ ግልባጭ ማድረግ ሳያስፈልግ አይቀርም ፡፡

3 .ገንዘብ በመቆጠባችሁ ብቻ እሸልማለሁ ማለት ከጀመረ አመታት አሳለፈ ፡፡ ስልቱም የልማት አጋር ብቻ ሳይሆን የአዲስ አሰራር መንገድ መሆኑን
ነግሮናል ፡፡

ኬር ! ብለናል ፡፡

አዲስና ዘመናዊ መንገድ ብሎ ካስተዋወቀን አሰራር ውስጥ ኤቲኤም ይገኝበታል ፡፡ ይህ ካርድ የተሰጠን ግዜ ላላፊው አግዳሚው ብቻ ሳይሆን ለራሳችንም አስር ግዜ ከኪሳችን መዥለጥ እያደረግን አስኮምኩመነው ነበር ፡፡

መሰለፍ ድሮ ቀረ ብለናል ፡፡
ብር እንደ አበሻ ጎመን ከቅርባችን ሊቀነጠስ ነው ብለናል ፡፡

ይሁን እንጂ እነዚህ ማሽኖች በአጭር ግዜ ውስጥ በበሽታ ማስነጠስ ጀመሩ ፡፡ ቀስ በቀስም የሚከበሩ ዋንጫዎች ሳይሆኑ ባዶ ቆርቆሮ መሆናቸውን አስመሰከሩ ፡፡ እንደ ወንድማቸው የመንገድ ስልክ የነሱንም ወገብ በፍልጥ የሚነርት በዛ ፡፡ የአራዳ ልጆች አናታቸውን ከፈት አድርገው ቆሻሻ ይጥሉበት ነበር ፡፡ ይህ ከመሆን ለጥቂት የተረፈው ቆርቆሮዎቹ የቆሙት ጥበቃ ያለበት አካባቢ መሆኑ ነው ፡፡ አልፎ አልፎ የሚሰሩት ደግሞ ሰው ብር በሚፈልግበት ቅዳሜና እሁድ ለጥቂቶች አገልግለው ጎተራቸው ባዶ መሆኑን ያውጃሉ ፡፡
የታመመውን ዘመናዊነት መታደግ የደከመው የኢትዮጽያ ንግድ ባንክ ነው እንግዲህ በአናቱ ላይ ስለ ቁጠባ ሳያሰልስ የሚጨቀጭቀን ፡፡ አንዳንዶች ዘወትር ለስራ የሚጠቀሙትን አንዳንዶች ወር ጠብቀው የሚያገኙትን ደመወዝ ለመቀበል ሲሄዱ ‹‹ እንኳን ደህና መጣችሁ ! ›› የሚለው ትሁት ቃል አይጠብቃቸውም ፡፡ ደንበኛን የማያስቀይመው ንግድ ባንክ ግን ተመሳሳይ ቃል አመንጭንቷል ፡፡

‹‹ ኮንኬሽን የለም ! ›› የሚል
‹‹ ዛሬም ?! ››
‹‹ ምን እናድርግ ? ቴሌ እኮ ነው ?! እጀ ሰባራ አደረገን ! ››
‹‹ ታዲያ ሌላ አማራጭ የለም ? ››
‹‹ ምን ይምጣ ? የለም ! ››
‹‹ ወይ ጌታዬ ምን ይሻል ይሆን ? ››
‹‹ ሌላ ቀን ብቅ ማለት ወይ እስኪመጣ መጠበቅ ነዋ ! ››
‹‹ መቼ ይመጣ ይሆን ? ››
‹‹ እንጃ ! ቴሌም አያውቀው ! ››

ስለ ዘመናዊነት የሚያወራው ባንክ ስራውን ከቴሌ ጋር በጋራ ተስማምቶና ተነጋግሮ እንደጀመረ ይገመታል ፡፡ ግን ጉልቤው በየቀኑ ሲቆነጥጠውና ሲያሸው ሊታገለው ሊቃወመው ሊገስጸው አልደፈረም ፡፡ ስለዚህ ብር አስቀማጩ ባንክ አስር አለቃ የአየሩ አክሮባቲክስ ቴሌ ኮሎኔል መሆናቸውን ለመገመት እንገደዳለን ፡፡ ጂኔራሎቹን ያው መገመት ይቻላል ፡፡
በዚህም ምክንያት አዳራሽ የሞሉት ባለከራባት ሰራተኞች ወንበር ላይ ተለጥጠው ጣራ የነካ ብር ተደግፈው ጥርሳቸውን መፋቅ ይጀምራሉ ፡፡ ትዕግስተኛው ህዝባችን ደግሞ ከመስታውቱ ጀርባ እጅብ ብሎ አፋፋቃቸውን በጥብቅ ይመለከታል ፡፡

‹‹ አለ መፋቂያ ! መፋቂያ  ! … የክትክታየቀረሮየዋንዛ
  የሚያሳምር  … የሚያወዛ ››

የሚል ድምጽ ስማ ስማ አለው ጆሮዬን ::

Monday, July 15, 2013

‎መቼ ነው የሀገራችን መንጃ ፍቃድ የሞት ፍቃድ የማይሆነው ?‎



ሞጆ ---- ሰኔ 2005 . ፡፡

የምሽት ጉዞ ክልከላን የናቀ ወይም ያልተቀበለ ሾፌር እንደሚግ እየተወረወረ መንገድ ላይ ከቆመ ትልቅ መኪና ጋር ተላተመ ፡፡ በተአምርና በተለየ ብልጠት ካልሆነ በስተቀር አንድ ሚዳቆ ዝሆንን ገፍታ ከቦታው ታርቃለች ማለት ይከብዳል ፡፡

የሆነው ግን ይኀው ነው ፡፡

ከዝዋይ ወደ አዲስ አበባ የሚፈተለከው ዶልፊን ሚኒባስ ተበላሽቶ የቆመውን ትልቁን ማርቼድስ ከነበረበት 50 ሜትር ርቀት አፈናጠረው ፡፡ ወደ ገደላማ ቦታም ሰደደው ፡፡ ሀገር ሰላም ብለው መኪና ውስጥ የተኙ ሰዎች ከለሊቱ አስር ሰዓት መኪናው ሲንቀሳቀስ በእንቅልፍ ልባቸው ወደ አንድ ጋራዥ እየተጓዙ ቢመስላቸው አያስገርምም ፡፡ ነቅተው ያሉበትን ሲረዱ ግን በታላቅ ድንጋጤና ሽብር ተርበተበቱ ፡፡ ከአደጋው መትረፋቸውን ሲያረጋግጡም ስሜታቸው ተዘበራረቀ - ደስታና ፍርሃት ፡፡

ወዲህ  22 ሰዎችን የጫነው ሚኒባስ አንድ ከዝሆን የተሰራ ሰው እንደ 4 ጨምድዶ ወደ ቅርጫት የወረወረው ወረቀት መስሏል ፡፡ ጭምድዱ በቁርጥራጭ የሰው ልጆች ስጋና አጥንት የተሞላ ቢሆንም መጠኑን አላሳደገውም ፡፡ ያለቅጥ ተደራርበው ከተጫኑት 22 ተሳፋሪዎች መካከል ሹፌሩን ጨምሮ 16 ንጹሃን ነፍስ በምሽቱ ተቀጠፈ ፡፡ የሀገራችን መኪና አደጋ ከዚህም በላይ ቁጥር በማስመዝገብ የሚታወቅ ቢሆንም የአሟሟቱ ሰቅጣጭነት ግን ከእስከዛሬው ሁሉ ይጎፈንናል ፡፡ የሰው ልጅ አንገት እዚህና እዚያ እንደ ጎልፍ ኳስ በሯል ፡፡ አካል ከዶሮ በቀጠነ መልኩ በግድ ተበልቷል ብቻ ሳይሆን ለመልቀም በሚያስቸግር መልኩ ተጨፈላልቋል ፡፡ ‹‹ የዉሃ ያለህ ! ›› በሚባልበት ሀገር ደም ያለ ቆጣሪ ፈሷል ፡፡

አለልቱ --- 1999 ፡፡

ከወደ ላይ የጣለው ዝናብ ጎርፍ ወልዶ የመኪና መንገድ ላይ ይደነፋል ፡፡ አንድ የቀይ መስቀል አምቡላንስ ለስራ ተጣድፎ ሳይሆን አይቀርም ጎርፉን ገፍቶ ለማለፍ ሲሞክር ወደ ወንዙ ይወድቃል ፡፡ ይህ ሲሆን በርካታ ሰዎችን የጫነ የህዝብ ማመላለሻ አውቶብስ ከኃላ ይመለከታል ፡፡ ሞተሩን በደንብ ኮርኩሮ ወደፊት ተንቀሳቀሰ ፡፡ ‹‹ እባክህ አትዳፈር ! ጥቂት ትዕግስት ይኑርህ ! ›› የሚሉ ድምጾችን ለማስተናገድ ፈቃደኛ አልሆነም ፡፡ ጎርፉን በጭንቅላቱ ሳይሆን በመኪናው ትልቅነት የመዘነው ሾፌር በማታውቁት ጥልቅ አትበሉ / በሆዱ ነው / በሚል እሳቤ ከባላጋራው ጋር ግብግብ ገጠመ ፡፡ ጥሶት ሊወጣ ተንፈራገጠበንዴት ጓጎረጎርፉ ግን እያስጮኀውም እያሳሳቀውም ገለበጠው ፡፡ የበርካታ ንጽሀን ነፍስም ለሰሚ በሚከብድ መልኩ በጎርፉ ተቀረጠፈ ፡፡

በጣም ትዝ ይለኛል ትራፊክ ፖሊስ ‹‹ ቸልተኛና ሃላፊነት የማይሰማው ! ›› በማለት ነበር ሾፌሩን ያወገዘው ፡፡ ይህ አይነቱ ወቀሳና ስያሜ በሀገራችን ዕድሜ ጠገብ ቢሆንም ዛሬም ሰንሰለቱ መጠናከሩን እንጂ ያለመበጠሱን የሞጆና አለልቱ ታሪኮች ያመላክታሉ ፡፡ የሞጆው አደጋ በተከሰተ በሶስተኛው ቀን በሱሉልታ ሚኒባስ 13 ሰዎችን ጨርሷል ፡፡ ጊዮርጊስ ከሀዋሳ ከነማ ለነበረበት ጨዋታ ወደ ሀዋሳ ሲጓዙ መቂ ከተማ ላይ መኪናው በመገልበጡ ሁለት ደጋፊዎች ሲሞቱ ሁለቱ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸዋል ፡፡ በአዲስ አበባ በየቀኑ የትራፊክ አደጋ ከነሞቱ ፣ጉዳቱ እና የንብረት ውድመቱ ተመዝግቦ ለጆሮአችን እንደ ቁርስ ይቀርባል ፡፡ በቅርቡ ወደ ጎንደር ሁመራ ቋራና ጅጅጋ ለስራ አቅንቼ ነበር ፡፡ በሁሉም መስመሮች በጣም በተቀራረበ ርቀት በሚያሳዝንና በሚሰቀጥጥ መልኩ ከቤት መኪና እስከ ተሳቢዎች በየመንገዱ ተጨማደውና እግራቸውን ሽቅብ ሰቅለው በየገደሉ ‹ ዳይቭ › ጠልቀው ተመልክቼያለሁ ፡፡ ብዙዎቹ ሞተዋል፣ ለአካል ጉዳት ተዳርገዋል ሀብት ወድሟል ፡፡

ያስደነግጣል ፡፡

ወዴት እየሄድን እንደሆነ በቅጡ አልተፈተሸም ፡፡ ከጠጡ አይንዱ ፣ ከነዱ አይጠጡ የሚለው የዘወትር ምክር ከመልዕክቱ ይልቅ ጥቅስነቱ ያሸበረቀ መስሏል ፡፡ አደጋውን የሚያስገነዝቡ የነሞገስ ተካና መሰል ድምጻዊያን ዘፈን ከእንጉርጉሮነት ለምን አላለፉም ? ከፕሮግራም ማዳመቂያነት ወይም የአየር ሰዓት መሙያነት ለምን አልተሻገረም ? … በጫት ምርቃና ፣ እጅን ከመሪና ማርሽ ይልቅ ለሞባይል በማዋል ፣ በአጉል ጀብደኝነት ፣ ያለ በቂ ችሎታ በማሽከርከር ፣ አይን የመንገድ እንቅስቃሴን ከመቆጣጠር ይልቅ የሴት ዳሌ ላይ እንዲያሸልብ በመፍቀድ ፣ ከፍጥነት በላይ በመሮጥ ፣ ተሸከርካሪን መንጃ ፍቃድ ለሌለው ሰው አሳልፎ በመስጠት ወዘተ … የሚሉ ምክንያቶች የሞታችን መንስኤ ከመሆን መቼ ያቆማሉ ?

እኛና ወዘተ የተባለው ነገር የተጋመድንበት ሰንሰለት ያስገርማል ፡፡

ማለት ፈረንጅ ሲባል ሁልግዜ መኪና ይፈበርካል ፤ አበሻ ሲሆን ሁልግዜ በመኪና ሰውና እንስሳትን ይገድላል ሊሆን ነው ፡፡ ለነገሩ ወደ ሀገራችን  ብቅ የሚለው የውጭ ዜጋ ልክ እንደ ቪዛው ‹‹ ኢትዮጽያ  ውስጥ አትንዳ ! የግድ ሲሆን እንጂ ከመሳፈር ይልቅ እግርህን እመን ! መስቀለኛ መንገድ ላይ ስትሻገር እንኳ የቆሙ መኪናዎችን ተገላመጥ ! ›› የሚል የቃል ይለፍ መቀበሉም ይረጋገጣል ይባላል ፡፡ ይህን ምጸት ተራ የሀገሬ ሰውም ገና ድሮ ‹‹ መንጃ ፍቃድ የሞት ፍቃድ ! ›› በማለት አጠናክሮት እንደነበር አይዘነጋም ፡፡ የተማረውና ምርምር አድርጌበታለሁ የሚለው ከረቫት ለባሽ ደግሞ ‹‹ በተሸከርካሪ አደጋ ሶስተኛ ደረጃ ላይ እንገኛለን ›› በማለት በየስብሰባው ከጣፋጭ ኩኪስ ጋር እንድናወራርደው ያደርጋል ፡፡

እነዚህ ሁሉ ምጸቶች ምን ያሳዩናል ? የሚከተሉትን ምርጫዎች በጥሞና በማንበብ ትክክለኛውን ምላሽ ለአፍታ ያንሰላስሉ ?

ሀ . ትላልቅ መኪናዎች ትላልቅ እቃዎች ለማጓጓዝ በእጅጉ ጠቃሚ የመሆናቸውን ያህል ትላልቅ በሬዎችንና ግመሎችን መጨፍለቃቸው የሚጠበቅ ነው ፡፡
ለ . ትንሽ በማይባሉ ትራፊክ ፖሊሶች ባሉበት ሀገር በጠራራ ጸሃይ ህጻናትን እንደ ሰርዲን አጭቀው የሚሮጡ ታክሲዎች ሲፈልጉ እንዲሞቱ ይፈርዱባቸዋል ፡፡
ሐ . ሾፌሮች ፍሬን አልታዘዝ ሲላቸው  ከስልክ እንጨት ፣ ከድንጋይ አጥር ወዘተ ጋር ከማጋጨት ይልቅ ቤት ደርምሰው የሚገቡት ‹‹ ዞሮ ዞሮ ከቤት ኖሮ ኖሮ ከመሬት ›› ለሚለው ጥቅስ ከፍተኛ አክብሮት ስላላቸው ነው ፡፡
መ . ቶራ ቦራ ተራራን የሚወደው አልቃይዳ እና አይሱዙዎች የሚያመሳስላቸው ራሳቸውንም ሌሎችንም ለማጥፋት ወደ ኃላ የማይሉ በመሆናቸው ነው ፡፡

ምርጫዎቹ በመኪናዎቹ አይነቶች ላይ ያነጣጠሩ ይምሰል እንጂ በውስጡ ተአምረኛው ወይም ምንተስኖት ሊባል የሚችለው ‹‹ አበሻ ›› መኖሩ ይታወቃል ፡፡ ‹‹ ምንተስኖት ›› በሞት ፍቃዱ አሰጣጥ ላይ ሳይታወቀው ድጋፍ የሚሰጥበት ሁኔታም ይታያል ፡፡

አይሱዙን እናንሳ ፡፡

የእነዚህን መኪናዎች ስያሜ ‹‹ አልቃይዳ ›› በማለት ዳቦ ቆርሷል ፡፡ መኪናዎቹ ለመገልበጥ ሾፌሮቹ ደግሞ ለመጋጨት ቅርብና ዝግጁ በመሆናቸው ነው ስያሜውን ያወጣው ፡፡ ህብረተሰቡ ሌላው ቢቀር መንጃ ፍቃድና የእቁብ ገንዘብ ለመጠየቅ ወደ ኃላ የማይለው ትራፊክ ፖሊስ እውቅና የሰጠውን ይህን ስያሜ እነሱም በደስታ መቀበላቸው ማስገረሙ አይቀርም ፡፡ የማይቃወመው ፣ የሚያጨበጭበውና አንዳንዴም የሚያሸልበው  የሀገራችን ፓርላማ  ‹‹ አሸባሪ ›› ብሎ ስማቸውን በአዋጅ ካሰፈረው ድርጅቶች መካከል ‹‹ አልቃይዳ ›› አንዱ መሆኑን ቢሰሙ እንኳ ደንታ የላቸውም ፡፡

 
ዛሬም በከተማም ሆነ በገጠር  እንደ ጄት ሲሮጡ ፖሊሱ ፣ መንገደኛውም ሆነ መኪናው ዳር ይዞ ያሳልፋቸዋል ፡፡ እኛ ለእኩይ ተግባራቸው የእውቅና ዲፕሎማ መስጠታችን እነሱ ደግሞ ይሄንኑ ሆይ ሆይታና ሳያገናዝቡ በአስፈሪ ተግባራቸው መቀጠላቸውን ቆም ብሎ ለመረመረ ገረሜታን ሳይጭር አይቀርም ፡፡ ለመሆኑ በሀገራችን መኪና የሚነዳው ለምን ዓላማ ነው ? አሽከርካሪና ተሸከርካሪ ማለትስ ? … ልብ ብላችሁ ካሰባችሁ መኪናው ያለተግባሩ የ ‹‹ ጥይት ›› ን ቦታ ተክቶ እየሰራ ነው ፡፡ አሽከርካሪው ደግሞ ቃታ ሳቢ ወታደር … እና ነገሩ እንደዚህ የሚታሰብ ከሆነ ሰላማዊ ሰዎች ከተባራሪ ወይም ደግሞ ከአባራሪ ጥይት ራሳቸውን ለማዳን በየትኛው መንገድ ይሂዱ ? ..

ለነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ትልቁን ድርሻ የሚወስደው መንግስት መሆኑ አያጠያይቅም ፡፡ መንግስት አደጋውን ለመቀነስ ለሾፌሮች ሰፊ የቀለምና የተግባር ትምህርት እሰጣለሁ በማለት አሰራሩን ከዘረጋ ቆየ ፡፡ አሰራሩ ስልጡን መሆኑን ለመግለጽ ‹‹ ሁለተኛ መንጃ ፍቃድ ያለው ስልጠናውን እስከወሰደ ድረስ በአንድ ዝላይ ባለአምስተኛ ከመሆን የሚያግደው የለም ! ›› በማለት በመግለጫ ተቀናጣ ፡፡ ይህ አሰራር ግን በየቦታው በስፋት እየታጨደ ያለውን ሞት ለማስቆምና ለህይወት ሁነኛ ዋስትና ለመስጠት ቃል አልገባም ፡፡ ይህ አሰራር እንደምንጠብቀው ምጡቅ ሾፌሮችን ለማምረቱ ልበ ሙሉ መስካሪዎች አላደረገንም ፡፡ ይህ አሰራር ዛሬም መንጃ ፍቃድ ቤት ድረስ በአፋጣኝ መልዕክት ከመድረሱ እንዲቆጠብ ዘብ አልቆመም ፡፡ በዚህ ሳይንሳዊ አሰራር መሰረት የኢትዮጽያ በመኪና የመሞት ሰቆቃ ቢያንስ እንደ እግር ኳሱ ጥቂት ደረጃዎችን ማሻሻል አልቻለም ፡፡ 
ምናልባትም ብሶበታል ፡፡

ታዲያ ምንድነው ዲስኩሩ ?
 ምንድነው ጥሩንባው ?
በየመንገዱ የሚወድቀውን ንጽሃን ቅበሩ ነው ?
መቼስ ነው የሀገራችን መንጃ ፍቃድ የሞት ፍቃድ ላለመሆኑ የተኛው ፓርላማ በነጋሪት ላይ የሚነግረን ?
‹‹ የአመለካከት ችግር ሲቀየር ነው  ›› --- እኮ የማ ?



Tuesday, June 11, 2013

No Dam , No Victory !‎




‹‹ No Money , No Funny ! ››  ሲሉ ነበር ፈረንጆቹን የምናውቃቸው ፡፡ የሙርሲ ሀገር ሰዎች ደግሞ ‹‹ No Nile , No Egypt ! ›› የሚል መዝሙር  ማቀንቀን  ጀምረዋል ፡፡ ይህን ፈሊጣዊ አባባል በጓድ መንግስቱ ዘመን ብንቃኘው ‹‹ እናት ሀገር ወይም ሞት ! ›› ወይም ‹‹ ሁሉም ነገር ወደ ጦር ግንባር ! ›› የሚል አቻ ምንዛሪ እናገኝበታለን ፡፡

በውስጥ ችግሮች የተጠላለፉት የግብጹ መሪ መሀመድ ሙርሲ በሙሉ አፋቸው ‹‹ አንዲት ጠብታ ውሃ እንኳ አንፈቅድላቸውም ! ›› ብለዋል ፡፡ በጣም የሚገርመው የማይፈቀድልን ውሃ የራሳችን ንብረት መሆኑ ነው ፡፡ ነው ‹ አንዲት ጠብታ አፈር እንኳን ወደ ዉጭ እንዲወጣ አልፈቅድም › በማለት ጫማ አስወልቀው ያስጠረጉ የሀገራችንን መሪ ታሪክ ለመድገም አስበው ነው ? ይህ የተደረገው ደግሞ በሰው ሳይሆን በራስ ኀብት ነው ፡፡ የቀድሞው ጠ/ሚ/ር መለስ ዜናዊም በአንድ ወቅት ‹‹ የአባይ ግንባታ ለአንዲትም ደቂቃ ቢሆን አይቋረጥም ! ›› ብለው ነበር ፡፡

አንዲት ጠብታ !
አንዲት ደቂቃ !

ግብግቡን አያችሁት - ማለቴ የውጥረቱን ስስነት ፡፡ መቼም በ ‹ አንፈቅድላቸውም ! › እና በ ‹ አይቋረጥም ! › መካከል እንደ አባይ ወንዝ የረዘመ የእልህ ክፍተት አለ ፡፡ እነዚህ የተንቦረቀቁ ሀሳቦች እንደምን ሊቀራረቡ እንደሚችሉ ማሰብ ለግዜው ግርታ ይፈጥራል ፡፡ እውነቱ ግን የተራራቀው አባባሉና መፈክሩ እንጂ መሬት ላይ ሊለካ የሚችለው ተጨባጭ ተግባሩ አይመስለኝም ፡፡ ምክንያቱም እንደ ግብጾች ቁጣ ከሆነ እኛ ‹ የሬሳ ማጠቢያ የሆነውን ውሃ ለለመነ አይከለከልም › የምንለውን ቅዱስ ብሂል ባለመረዳት አንዲት ኩባያ እንኳ ለጥማታችን ሊሰጡን አልፈቀዱም ፡፡ እንደ ስነ ጽሁፍ ተማሪነት ሰሙን ወደ ጎን ትተን ወርቁን የምንፈልግ ከሆነ ግን የሚሊኒየሙ ግድብ 21 ከመቶ ያህል ተከናውኗል … ተደፈርን በሚል ስሜት ደማቸውን ያንተከተከው የቅልበሳ ስራም ተከናውኗል ፡፡ አንድ አምስተኛ የተከናወነው ስራ ቀስ በቀስ አንድ አራተኛ … አንድ ሶስተኛ … የሚባለውን ስሌት ተከትሎ የግድቡ ገላ እየፈረጠመ መሄዱ አይቀርም ፡፡

ይህም ሲሆን ፉከራው ፣ ቀረርቶው ፣ ዛቻውና ውጥረቱ እየጮኀ - በዝምታ / contradictory / ይቀጥላል ባይ ነኝ ፡፡ ምክንያቱም የሚጮህ ውሻ ሁሉ ፈሪ ቢሮጥለት እንጂ እንደማይናከስ ከልምድ ይታወቃልና ፡፡ በርግጥ የግብጽ ጋዜጦች ‹ ዉሾቹ ይጮሃሉ ፣ ግመሎቹ ጉዟቸውን ቀጥለዋል › የሚል አናዳጅና ነገር አቀጣጣይ ዘገባዎችን ማፋፋማቸው ይጠበቃል ፡፡

‹ እውን ደርግ አለ ? › የሚለውን ታሪካዊና ወጥ አባባል እያስታወስን ‹ እውን ግብጾች አይናከሱም ? › የሚል በአሽሙር የተንጋደደ ጥያቄ ወርወር እናድርግ ፡፡ ርግጥ ነው ድንገት ከኃላ ተደብቆ እግር ስር የሚጮህ ዉሻ እንኳ ቀልብ ይገፋል ፡፡ በዚህም ምክንያት ከቆመ ስልክ እንጨት ጋር ሊያጋጭ ወይም በኮብልስቶን ካልተቀየረ ሹል የወንዝ ድንጋይ ላይ በደረት ሊደፋ ይችላል ፡፡ በተቃራኒው ግብጽ በቀጣይ ልታደርሰው የምትችለው ጉዳት እንደ ሶርያ ከተማ ያፈራርሰናል ብሎ ማሰብ ግን አጓጉል ስጋት ነው የሚሆነው ፡፡

እኮ ለምን ?
ከ 500 በላይ የሚደርሱት ተዋጊ አውሮፕላኖቻቸው በሶ ጨብጠዋል ?
ከ 1 ሺህ በላይ የሚቆጠሩት ተወንጫፊ ሚሳይሎቻቸው በቀፎን ተጨባብጠዋል ?
እነ ኤፍ 16 ፣ ሚግ 17 ፣ ሚግ 21 ፣ አልፋ ጄት ፣ ሚራዥ ፣  የኬሚካል ጦር መሳሪያዎቻቸው ምን ይጠብቃሉ ? መባሉ ግድ ነው ፡፡ እኮ ታዲያስ ?

1 . ለነገርም ሆነ ለአውሮፕላን መንደርደሪያነት እጠቀምባታለሁ የምትላት ሱዳን ግድቡ ጠቃሚ መሆኑን በመረዳት ለሀገራችን ድጋፏን ሰጥታለች ፡፡ ይህ ማለት ደግሞ አንዴ በሞሉት ነዳጅ ከ 1 እስከ 3 ሺህ ኪ.ሜ የሚጓዙት ተዋጊ ጀቶች ግድቡ ጋ መድረስ ቢችሉ እንኳን ሀገራቸው ለመመለስ አይችሉም ፡፡ ርግጥ ነው እንደ አልቃይዳ እዛው እየፈነዳን እናልቃለን ካሉ ምርጫቸው ነው ፡፡ ይህን ምርጫ ለመጠቀም ካሰቡ የኛ የቤት ስራ ገና ድንበራችን እንዳለፉ በመቃወሚያ መልቀም ነው ፡፡ የጋሽ አልበሽር ሀሳብ ነገ ሊቀየር ከቻለስ ? የሚል ስጋት ሚዛን ከደፋም መፍትሄ አይጠፋም ፡፡ ሰውየው በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት በወንጀል ስለሚፈለጉ አንጠልጥለን እንደምንሰጣቸው አስረግጠን ማስረዳት ነው ፡፡

2 . የግብጽ መንግስት ስር ነቀል ለውጥ የሚፈልገውን ህዝብና ወግ አጥባቂዎችን አስተባብሮ ለጥፋት ዓላማ ለመሰማራት ይከብደዋል ፡፡ ምንም እንኳ ህዝቡ አንድ ሆኖ በአባይ ጉዳይ እንዲያተኩር እየቀሰቀሰ ቢሆንም ፡፡

3 . ግብጽ የራሷን የችግር ቁልል ወይም ተሰርቶ የማያልቅ የቤት ስራ ገና አጽድታ አልጨረሰችም ፡፡ ግድቡን አፈራርሳለሁ የሚለው የግብጽ መንግስት በህዝባዊ ተቃውሞ ወይም ባደፈጠው ጦር ሰራዊት ሊፈራርስ አይችልም ማለት አያዋጣም ፡፡

4 . ግድቡ የግብጽንና ሱዳንን ጥቅሞች በከፋ መልኩ የማይጎዳ መሆኑን ሀገራቱን ያካተተውና የገለልተኞች ስብስብ የሆነው አጥኚ ቡድን አረጋግጧል ፡፡ ይህ ውሳኔ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ እንደ ቋሚ ህግ ወይም መመሪያ ሊያገለግል የሚችል ነው ፡፡ ህግን ጥሶ ወደ ጦርነት መግባት ደግሞ ዓለማቀፍ ውግዘትን እንጂ ድጋፍን አያስገኝም ፡፡

5 . ቢያዋጡንም ባያዋጡንም እነ ቻይና ፣ እስራኤልና አሜሪካ የኛ አጋር እንደሆኑ የመገመት ወይም የመፈረጅ አባዜ በምድረ ግብጽ እየተስፋፋ ነው ፡፡ ይህ ጉዳይ ለእኛ መልካም አጋጣሚ ለሚያስፈራሩት ደግሞ ስጋት ይፈጥራል ፡፡ በዚህ ግዜ የሚገኘውን ‹ ቲፕ › መቀበል ይጠቅማል ፡፡

6 . በታሪክ አይን ኢትዮጽያን መተናኮስ ወይም በሃይል ማስገበር ብዙ መስዋዕትነት ሊያስከፍል እንደሚችል ይታወቃል ፡፡ ስለዚህ ግብጾች ክተት ከማወጃቸው አስቀድሞ የጦርነቱን የመጨረሻ ውጤት ከወዲሁ አስልተው መነሳት ይኖርባቸዋል ፡፡

7 . በአፍሪካ ህብረት የላቀ ክብር ያገኘውን የኢትዮጽያ ጦር ሰራዊት ፣ በተመድ ዶላር ብቻ ሳይሆን ኒሻን የተከፈለውን ጦር ሰራዊት አቅም አሳንሶ ማየት የሚቻልበት አግባብ የለም ፡፡ ግዜውም አይፈቅድም ፡፡


እነዚህን የመሳሰሉ ተጨማሪ ምክንያቶችን መዘርዘር ይቻላል ፡፡ ይሁን እንጂ ግብጽ ውክልናንም ሆነ ሰላማዊ የክርክር መድረክን በመጠቀም ልትናከስ የምትችልባቸው አግባቦች አይኖሩም ማለት አይቻልም ፡፡ አንደኛው ራሳቸው እንደተናገሩት በራሳቸውም ሆነ በሌሎች የውጭ ሃይሎች የሽብር ተግባር መፈጸም ነው ፡፡ እንደውም አስፈሪውና ለእውነት የቀረበው ይኀኛው መንገድ ነው 

፡፡ ሁለተኛው ኢትዮጽያ ከአበዳሪ ድርጅቶች ጋር በቂ ገንዘብ እንዳታገኝ የማግባባትና የማሳመን ስራ ማከናወን ይሆናል ፡፡ ይህም በጣም ሊተገበር ይችላል ፡፡ እንዴት ከተባለ ሀገሪቱ ከፍተኛ የሆነ የዲፕሎማሲና የነገር ልምድ አካብታለች ፡፡ በሌላ አነጋገር ያደፈ ቢሆንም እጇ ረጅም ነው ፡፡ ግድቡ ጉዳት የለውም የሚለው የኛ መፈክርና እንዴት እንደፈራለን የሚለው የእነሱ ‹ ባላባታዊ ቁጣ › ደግሞ በቀላሉ እንዳንግባባ ያደርገናል ፡፡ ተከብሮ የኖረውን የሳዳትና የናስር መርህ እናስጠብቃለን ሲሉ እኛ ደግሞ የአጼ ቴዎድሮስንና የሚኒልክን ሀገራዊ ተጋድሎና ዝና እንደግማለን እንላለን ፡፡ ይህ ክፍተት በራሱ ለጋሽ ሀገሮችና አበዳሪ ድርጅቶች ወደ አንዱ ወገን እንዳያጋድሉ ያስፈራቸዋል ፡፡ ጭቅጭቁ የሰላም ማረጋገጫ ወይም ዋስትና አልሰጠንም እንዲሉ በር ይከፍትላቸዋል ፡፡ በሌላ አነጋገር ለኛ የተቆለፈው እጃቸው ነገም እንደተከረቸመ ይቀጥላል ማለት ነው ፡፡

አሁን ‹ No Money , No Funny › ወይም ‹ No Money , No Dam ›  የእውነት በኛ ላይ እንዳይሰራ ወይም በብሂሉ ተጠልፈን እንዳንቆም መስጋት አግባብ ይሆናል ፡፡ በርግጥ መሃንዲሱም እኛ ፣ የገንዘብ ምንጩም እኛ መሆናችን ቀደም ብሎ የተገለጸ ነው ፡፡ የግብጾች ትንኮሳ ፣ እብሪትና ማን አለብኝነትም የህዝቡን ቁጭት ለማቀጣጠል የሚያስችል ክብሪት እንደሚፈጥርም ይገመታል ፡፡ መንግስት አሪፍ ከሆነ አጀንዳውን ለሀገራዊ መግባባት ሊጠቀምበት ይችላል ፡፡

እንደዛም ሆኖ ግን ‹ ተራራው የግድብ ብር ›  ላይ ለመድረስ ምስኪኗ የወር ደመወዛችንና የአንዳንድ ባለሃብቶች ለቀቅ ያለ ልግስና ብቻ የትም አያደርሰንም ፡፡ በመሆኑም ያልታዩ አዳዲስ ስልቶች ያስፈልጉናል ፡፡ ለዚህም ስልት መሳካት ቆራጥ ርምጃዎችና ‹ እናት ሀገር ወይም ሞት ! › የሚሉ አመራሮች ያስፈልጋሉ ፡፡

እኮ ለምን ? ምን ሊያደርጉ ?

ብዙ ብዙ ነገሮችን ለማድረግ መጠበብ ያስፈልጋል ፡፡ ቢያንስ ሁለት ክፉ ምሳሌዎችን እንደ ማሳያ ልወርውር ፡፡

. አንደኛ ትንሽ ትልቁ በሙስና እየበላ የሚገኘውን ገንዘብ ጠንክሮ በማስመለስ ለግድቡ እንዲውል ማድረግ ፡፡ ሁለት መቶ ደርሷል የተባለውን ተጠርጣሪ እንደ ትራንስፎርሜሽኑ የተለጠጠ ዕቅድ በመቶ እጥፍ በማሳደግ ካቴና የሚያጠልቀውን የሌባ ቁጥር ከፍ ማድረግ ፡፡

. ሃብታም ባለስልጣናት ለፖለቲካው ልዕልና ሲባል ዘብጥያ የማይወርዱ ከሆነ እንኳ ቢያንስ በአንድ ነገር መደራደር ፡፡ ሰርቀው ካጠራቀሙት በርካታ ገንዘብ በርካታ እጁን እንዲያዋጡ ማድረግ ፡፡ ይህ ጥያቄ ጋሼ ትልቁና እትዬ ትልቋንም ይመለከታል ፡፡ እነሱም ከኛ እኩል የወር ደመወዛችንን ለገስን ሲሉ ‹ Shame › አይዛቸውም እንዴ ?  Really , It is not a joke !

No Dam , No Joke !
No Dam , No Justice !
No Dam , No Victory !
One  Nile  , More Togetherness !