Thursday, November 22, 2012

የአምባገነኖች ቀልድ



ለተለያዩ ስራዎች የተለያዩ መረጃዎችን ሳገላብጥ ካሰባሰብኳቸው አምባገነናዊ ቀልዶች የተወሰኑትን እነሆ ብያለሁ ፡፡ ካዝናኗችሁ ዘና በሉባቸው ፡፡

ሂትለር በገነት

አዶልፍ ሂትለር  እንደሞተ ራሱን ከሲኦል በር ጋ አገኘው ፡፡ ሲያንኳኳ በሩን ከፍቶ የወጣው ሰይጣን ‹‹ ስምህ ማነው ? ›› ሲል ጠየቀው
‹‹ አዶልፍ ሂትለር ››
 ሰይጣን በጣም እየተገረመ  ‹‹ በምድር ላይ ምን እንደሰራህ አውቃለሁ ፤ ወደ ውስጥ እንዳላስገባህ ቦታ የለም ፡፡ በርግጥ ሲኦል ቢሆንም ለሁሉም ነገር ወሰን አለው፡፡ ለምን ወደ ገነት አትሄድም  ?››
‹‹ አላውቀውም ! ››
‹‹ ይህን መንገድ ተከተል ፡፡ በስተቀኝ በኩል ትልቅ በር ታገኛለህ ፡፡ አታጣውም ››
ሂትለር ባልጠበቀው ጥሩ እድል እየተደሰተ ወደ ገነት ተጓዘ ፡፡ በቀጣዩ ቀን የሲኦል በር ተንኳክቶ ሰይጣን በሩን ሲከፍት እየሱስን ቆሞ ተመለከተ
‹‹ እየሱስ ! እዚህ ምን ታደርጋለህ ?! ›› በግርምት ጠየቀው
‹‹ ከካምፕ ጠፍቼ ነው የመጣሁት ! አመጣጤም የፖለቲካ ጥገኝነት ለመጠየቅ ነው ›› ሲል እየሱስም መለሰ

የስታሊን ግርፍ

            ከጆርጂያ የመጡ የልዑካን ቡድን አባላት ለረጅም ሰዓታት ከስታሊን ጋር ስለ ልማትና እርዳታ ከተወያዩ በኃላ በሚደረግላቸው ትብብር  በመርካት ቢሮውን ለቀው ወጡ ፡፡ ስታሊን ሲጋራ የሚያጨስበትን ትቦ መሳይ ነገር በማጣቱ  ወዲያው አንድ ስራውን ጠንቅቆ የሚያውቅ ደህንነት  ሰው ጋ ደውሎ ሲጋራ ማጨሻውን ነጥቆ እንዲያመጣ ያዘዋል ፡፡ ነገር ግን  ከ30 ደቂቃ በኃላ ዕቃውን ጠረጼዛ ስር በማግኘቱ የላከው ሰው ጋ በመደወል ትዕዛዙን ትቶ እንዲመጣ ይነግረዋል ፡፡
‹‹ አዝናለሁ ጓድ ስታሊን ! ››
‹‹ምን ተፈጠረ ?! ››
‹‹ ከልዑካን ቡድኑ ግማሽ ያህሉ እኮ ዕቃውን መውሰዳቸውን አምነዋል ፡፡ የተቀሩት ደግሞ ጥያቄው  በሚከናወንበት ወቅት አልፈዋል ›› በማለት ምላሹን በስልክ አሰማ

የመሪዎች ፉክክር

           ንግስት ኤልሳቤጥ፣ ቢል ክሊንተንና ሮበርቱ ሙጋቤ እንደሞቱ ቀጥታ ወደ ሲኦል አመሩ ፡፡ ወዲያው ንግስት ኤልሳቤጥ ‹‹ እንግሊዝ በጣም ናፍቃኛለች፣ መደወል እፈልጋለሁ፡፡ ሁሉም ሰው ምን እያደረገ መሆኑን ማወቅ እፈልጋለሁ ›› በማለት ለ 5 ደቂቃ ያህል አወራች፡፡ ከዚያም ‹‹ ሰይጣን ስንት ነው የምከፍለው ? ›› ስትል ጠየቀች
‹‹ አምስት ሚሊዮን ዶላር ›› አላት ፡፡ ቼክ ጽፋ ሰጠቸውና ወደ ቦታዋ ተመለሰች፡፡ ክሊንተን በኤልሳቤጥ ተግባር በመቅናቱ ‹‹ እኔም ወደ አሜሪካ መደወል እፈልጋለሁ ›› አለ፡፡ ለሁለት ደቂቃም አውርቶ ሂሳብ ሲጠይቅ 10 ሚሊዮን ዶላር ተጠየቀ፡፡ እሱም ቼክ ጽፎ ሰጠ፡፡
ሮበርቱ ሙጋቤም ከማን አንሳለሁ በሚል ስሜት ተነሳስቶ ‹‹ እኔም ወደ ዙምባብዌ መደወል እፈልጋለሁ ፣ ከቤተሰቤና ሚንስትሮቼ ጋር ማውራት እፈልጋለሁ ›› አለ ፡፡ ሙጋቤ ወሬውን ማቋረጥ ባለመቻሉ ለ10 ሰዓታት ያህል አወራ፡፡ ኤልሳቤጥና ክሊንተን ከየት አባቱ አምጥቶ ሊከፍል ነው በማለት መጨረሻውን ለማየት ቋመጡ ፡፡ ሙጋቤ እንደጨረሰ ሂሳብ ሲጠይቅ
‹‹ አንድ ዶላር ! ›› ሲል ሰይጣን መለሰለት
‹‹ ሂሳብ አትችልም እንዴ ?  ይህን ሁሉ አውርቼ  አንድ ዶላር ትለኛለህ ?! ››
‹‹ ባክህ እችላለሁ ! ሂሳቡ ይሔው ስለሆነ ወዲህ በል ! ››
‹‹አዝናለሁ አትችልም ! ››
‹‹ ሰውዬ ምን ነካህ ! ከሲኦል ወደ ሲኦል  እኮ ነው የደወልከው ! ይህ ደግሞ የሀገር ውስጥ ጥሪ ነው ! ›› ሲል አምባረቀበት

የቴይለር ርህራሄ

ቻርልስ ቴይለር እና ሾፌራቸው በመኪና ወደ ዋና መንገድ ሲያመሩ አንድ አሳማ ገጩ ፡፡ አሳውም ወዲያው ሞተ ፡፡ ቴይለርም ለሾፌራቸው ‹‹ እዛ ወዲያ ወዳለው የእርሻ ቦታ ሂድና አሳማው ምን እንዳጋጠመው አስረዳ›› አሉት
ከአንድ ሰዓት በኃላ ሾፌራቸው ከእርሻው ቦታ ከሴቶች ጋር ሲመለስ ተመለከቱ ፡፡ በአንድ እጁ የወይን ጠርሙስ ፣ በሌላ እጁ ሲጋራ ጨብጧል
‹‹ ምን ሆንክ አንተ ;! ››
‹‹ ገበሬው ጠርሙስ ወይን፣ ሚስቱን፣ ሲጋራና ከእኔ ጋር ፍቅር የያዛትን የ 19 ዓመት ልጁን ሰጠኝ ››
‹‹ እንዴት ? ምን ብለህ ነግረሃቸው ነው ? ›› ቴይለር አፈጠጡ
‹‹ እንደምን አመሻቸሁ ! እኔ የቴይለር ሾፌር ነኝ ፣ እናም አንድ አሳማ ገድያለሁ ! ››

የፑቲን ስጋ

የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን መጥፎ ህልም በሌሊት ቀሰቀሳቸውና እየተጨናበሱ ወደ ፍሪጅ አመሩ፡፡ ልክ ፍሪጁን እንደከፈቱ በመልክ በመልክ ተደርድረው የተቀመጡ ስጋዎች መንቀጥቀጥ ጀመሩ፡፡ በድርጊታቸው በመናደዳቸውም እንደሚከተለው ገሰጽዋቸው
‹‹ አትንቦቅቦቁ !! እኔ የመጣሁት ቢራ ለመጠጣት ብቻ ነው !! ››


የመለስ የጾታ ፍቃድ

አንድ ዝነኛ አርቲስት ክስ ተመስርቶበት ከታሰረ ትንሽ ቆየት ብሎ ነበር ። በዚህን ወቅት አንድ ታዋቂ አትሌት በውጭ ሀገር አስደናቂ ድል ተቀዳጅቶ ወደ አገሩ ሲገባ ጠ/ሚኒስትር መለስ አድናቆታቸውን ለመግለጽ ኤርፖርት ድረስ ሄደው ይቀበሉታል ። አትሌቱም አጋጣሚውን በመጠቀም አንድ አንገብጋቢ ጥያቄ እንዳለው ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ይናገራል ።
« ምን ችግር አለ ጠይቃ » አሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቀለል አድርገው
« ቴዲ አፍሮ የተባለው አርቲስት ካልተፈታ በመጣሁበት አውሮፕላን እመለሳለሁ »
« ወዴት ? »
« ወደ ሌላ ሀገር ፣ ጥያቄዬ ምላሽ ካላገኘ ዜግነቴንም ለመቀየር እገደዳለሁ »
« ወንድም ፣ እንኴን ዜግነትህንም ጾታህንም መቀየር ትችላለህ » አሉት ቆምጨጭ ብለው

የሙሻራፍ ፈተና

ፔርፔዝ ሙሻራፍ ወደ ደልሂ ለስብሰባ ሲያመራ ከህንዱ ጠቅላይ ሚንስትር ቫጅፔይ ጋር አጭር ቆይታ አደረገ ፡፡ ቫጅፔይ ‹‹ ስለ ካቢኔ አባላትህ እውቀት ምን እንደምታስብ አላውቅም፡፡ የኔ ሰዎች ግን በእጅጉ ጎበዞች ናቸው ›› ይለዋል
‹‹ እንዴት አወቅክ ? ›› ሙሻራፍ ይጠይቃል
‹‹ ቀላል ነው፡፡ ሁሉም ሚንስትር ከመሆናቸው በፊት ልዩ ፈተናዎችን ይወሰዳሉ ፡፡ ቆይ አንድ ግዜ ›› ይልና አድቫኒ የተባለውን ሚኒስትር ጠርቶ ይጠይቀዋል
‹‹  ያንተ ወንድም አይደለም፣ ያንተ እህት አይደለችም ፣ የአባትህ ልጅና  የእናትህ ልጅ ማነው ? ››
‹‹ ይህማ ቀላል ነው፡፡ እኔ ነኛ ! ›› ሲል አድቫኒ ይመልሳል
‹‹ ጎበዝ አድቫኒ ! ›› ቫደፓዬና ሙሻራፍ ተገረሙ
ሙሻራፍ ወደ ኢስላማባድ ሲመለስ ስለ ሚንስትሮቹ አዋቂነት በጣም እየተገረመ ነበር ፡፡ በመጀመሪያ ስብሰባውም በጣም የሚወደውን የካቢኔ አባል ጠርቶ ‹‹ የአባትህ ልጅና የእናትህ ልጅ ማነው ? ያንተ ወንድም አይደለም ፣ ያንተ እህት አይደለችም.፣ እሱ ማነው ? ›› ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ሰውየው ቢያስብ መልሱ ለመጣለት አልቻለም፡፡
‹‹ ትንሽ አስቤ ነገ መልሱን ባመጣስ ? ›› ሲል ያስፈቅዳል
‹‹ እንዴታ ! 24 የማሰቢያ ሰዓታት ተሰጥቶሃል ! ›› ሙሻራፍ መለሰ
ባለስልጣኑ ሚኒስትሮች፣ የካቢኔ ጸሃፊዎችና ትላልቅ ሰዎች ጋ እየደወለ ቢጠይቅ መልሱን ማግኘት አልቻለም ፡፡ ባለቀ ሰዓት ቤናዚር ቡቶ ብልህ ስለሆነች ታውቃለች በሚል ስልኩን መታና ‹‹ የአባትሽና የእናትሽ ልጅ የሆነ፤ ወንድምሽና እህትሽ ያልሆነ ማነው ?›› ሲል ጠየቃት
‹‹ በጣም ቀላል እኮ ነው ፡፡ እኔ ነኛ !! ›› ስትል መለሰችለት ፡፡ የካቢኔው አባል ደስ ብሎት ወደ ሙሻራፍ ደወለ ፡፡
‹‹ ጌታዬ መልሱን አግኝቼዋለሁ ፤ ቤናዘር ቡቶ ናት ›› አለ
‹‹ አንተ ደደብ ! አይደለም ›› አሉ ሙሻራፍ በቁጣ ‹‹ መልሱ አድቫኒ ነው !! ››
አይ ሙሻራፍ ???

የአህመዲንጃድ ቆምጫጫ ምላሽ

የኢራኑ ፕሬዝዳንት መሀመድ አህመዲንጃድ በኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ ተጋብዘው ስለ ሀገራቸው ወቅታዊ ሁኔታ ንግግር አድርገው ነበር፡፡ ከንግግራቸው በኃላ የተለያዩ ጥያቄዎችን ማስተናገድ ጀመሩ ፡፡
‹‹ የሰብዓዊ መብት አያያዝ ላይ ችግር እንዳለባችሁ ምእራባዊያን ይናገራሉ፡፡ እውነት ነው ; ››
‹‹ ወረኛ በላቸው ! ዛሬ የተሻለ መብትም ሆነ ዴሞክራሲ ያለው ኢራን ውስጥ ነው ››
‹‹ እሺ እዛጋ ጆሮህን እንደ ሴት የተበሳሐው ! ›› ፕሬዝዳንቱ ለሌላ ጠያቂ ዕድል ሰጡ
‹‹ አመሰግናለሁ ፡፡ በሀገራችሁ ምን ያህል ግብረ ሶዶማዊያን ይገኛሉ ; ››
‹‹ በታላቋ አራን ይህን የሚፈጽሙ ሰዎች የሉም ! ››
‹‹ መረጃዎች የሚጠቁሙት ግን በግብረሶዶማዊያን ላይ ኢ- ሰብዓዊ ድርጊት እንደምትፈጽሙ ነው ›› ሌላ ጠያቂ
‹‹ ወንድሜ ጥያቄ መደጋገም ለምን ያስፈልጋል! በሀገራችን የሉም አልኩህ እኮ ! ምክንያቱም ሁሉንም ጨርሰናቸዋል ! ››

የአሳድ ትዕዛዝ

በሀገሪቱ ከተደረገ አጠቃላይ ምርጫ በኃላ አንድ ሚንስትር እየተቻኮለ ወደ ሶርያው ፕሬዝዳንት ሃፌስ አሳድ ቢሮ ይገባል
‹‹ እሺ ! ›› አለ አሳድ ካቀረቀረበት ቀና ሳይል
‹‹ የተከበሩ ፕሬዝዳንት! እጅግ በጣም ደስ የሚል ዜና ይዤ መጥቻለሁ ፡፡ በምርጫው 98.6 ከመቶ አሸንፈዋል፡፡ እርስዎን ያልመረጡት ከ 2 በመቶ በታች የሚያንሱ ሰዎች ናቸው ፤ ከዚህ በላይ ምንም የሚፈልጉ አይመስለኝም ጌታዬ ;! ››
‹‹ እፈልጋለሁ ! እፈልጋለሁ እንጂ አንተ !! ›› አለ አሳድ ካቀረቀረበት ቀና ብሎ እያፈጠጠ ‹‹ በአስቸኳይ ያልመረጡኝን ሰዎች ስም ዝርዝር ለቅመህ አምጣ !!! ››

የማኦ ፈስ

አንድ ቀን የቻይናው ሊቀ መንበር ማኦ የግል ሀኪማቸውን ዶ/ር ዣንግን ጠርተው የሚከተለውን አዘዙት
‹‹ ሆዴን በሚገባ መርምር! ካለፉት ጥቂት ሳምንታት ጀምሮ በጣም እንግዳ ነገር እየገጠመኝ ነው ፡፡ በተደጋጋሚ ያስፈሳኛል ፤ ማለትም በየአምስት ደቂቃው ልዩነት… ይህ ከይሲ ነገር ሊቆም አልቻለም፡፡ እንግዳው ነገር ደግሞ ፈሱ ድምጽ የሌለው እንዲሁም ሽታው የማይታወቅ መሆኑ ነው ››
ማኦ ንግግራቸውን ከጨረሱም በኃላ ፈሱ ፡፡ ዶ/ር ዣንግን ከመድሃኒት ማስቀመጫ ሳጥናቸው ውስጥ የሆነች ጠርሙስ አወጡና
‹‹ ሊቀመንበር ማኦ ይህን መድሃኒት ለአምስት ቀናት በየአራት ሰዓቱ ልዩነት አንድ- አንድ በመውሰድ ተጠቀሙ ›› ብሎ ተሰናብቶ ወጣ
ከአምስት ቀናት በኃላ ማኦ ዶክተሩን አስጠርተው ይጮሁበት ጀመር ፡፡
‹‹አንተ የተረገምክ !! ምን ዓይነት መድሃኒት ነው የሰጠኀኝ ? አሁን ደግሞ በጣም ነው የባሰብኝ ፡፡ ትናንት በወጣቶች ስብሰባ ላይ ንግግር ሳደርግ ያለማቋረጥ እየፈሳሁ ነበር ፡፡ ድምጹ በጣም የሚጮህ ስለነበር አሳፍሮኛል ! ››
‹‹ ሊቀመንበር ማኦ አሁን የመስማትዎ ችግር ተቀረፈ ማለት ነው ›› አለ ዶክተሩ ኮስተር ብሎ ‹‹ አሁን የሚቀረኝ እንደምንም ብዬ የአፍንጫዎን ችግር ማስተካከል ይሆናል !! ››

No comments:

Post a Comment